በዋይት ሐውስ የጋዜጠኞች የእራት ግብዣ ላይ ተኩስ ቢከፈትም ትራምፕ ጉዳት እንዳልደረሰባቸው ተገለጸ

የፎቶው ባለመብት, Reuters
ቅዳሜ ምሽት ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ እና በርካታ የአሜሪካ ከፍተኛ ባለሥልጣናት በተገኙበት የዋይት ሐውስ ዘጋቢዎች የእራት ግብዣ አዳራሽ ላይ ጥቃት ለማድረስ የጦር መሣሪያ እና ቢላዋ ይዞ የገባ ግለሰብ በአገሪቱ የጸጥታ እና ደህንነት ባልደረቦች በቁጥጥር ስር ዋለ።
ፕሬዝዳንቱ ምንም ጉዳት ሳይደርስባቸው በፍጥነት ከአዳራሹ መውጣታቸው ታውቋል።
እንግዶች ጠረጴዛዎች ስር የተሸገጉ ሲሆን አንዳንዶቹ ዝግጅቱ ከተካሄደበት የዋሽንግተን ሂልተን ውጭ የተኩስ ድምጽ እንደሰሙ ተናግረዋል።
አንድ የፖሊስ ኃላፊ ግለሰቡ ተኩስ እንደከፈተ መናገራቸውን ኤፒ ዘግቧል። አንድ የፖሊስ አባል የጥይት መከላከያው ላይ ቢመታም በጥሩ ሁኔታ እንደሚገኝ ተገልጿል።
ትራምፕ "የታመመ ሰው" ሲሉ የገለጹት ተጠርጣሪ የ31 ዓመቱ ኮል ቶማስ አለን ሲሆን የቶረንስ፣ ካሊፎርኒያ ነዋሪ እንደሆነ ሁለት የሕግ አስከባሪ ባለሥልጣናት ለኤፒ ተናግረዋል።
"ተፅዕኖ ስታሳድር ይከታተሉሃል። ተፅዕኖ በማትፈጥርበት ጊዜ ደግሞ ይረሱሃል" ሲሉ ትራምፕ ከጥቃቱ ከሁለት ሰዓታት በኋላ በዋይት ሐውስ ተናግረዋል።
ግለሰቡ ጥቃቱን ብቻውን መፈጸሙን እና ሌላ ሰው አብሮት አለ ብሎ ለማመን "ምንም ምክንያት የለም" ሲሉ የዋሽንግተን ከንቲባ ሙሪየል ቦውሰር ገልጸዋል።
ትራምፕ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ በለጠፉት ቪዲዮ ተጠርጣሪው የደህንነት መከላከያዎችን አልፎ ሲሮጥ እና የደህንነትአባላት ሲከተሉት ያሳያል።
"ለሕዝቡ ምንም ዓይነት ተጨማሪ አደጋ ያለ አይመስልም" በማለት ቦውሰር በሌላ ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ተናግረዋል።
እራቱ ግብዣ ላይ ትራምፕ፣ ምክትል ፕሬዝዳንት ጄዲ ቫንስ፣ የመከላከያ ሚኒስትር ፒት ሄግሴት፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማርኮ ሩቢዮ እና ሌሎች በርካታ የትራምፕ አስተዳደር ባለሥልጣናት ተገኝተዋል። በአገሪቱ የደህንነት አባላት ጥበቃ የሚደረግላቸው ሁሉም ባለሥልጣናት ከቦታው እንዲወጡ ተደርገዋል።
እአአ ከ2024 ወዲህ ፕሬዝዳንቱ በአቅራቢያቸው ጥቃት ሲፈጸም ይህ ለሦስተኛ ጊዜ ሲሆን ባትለር፣ ፔንስልቬንያ በተደረገባቸው የመግደል ሙከራ ጉዳት የደረሰባቸው ሲሆን በስፍራው የነበር የእሳት አደጋ መከላከል ሠራተኛ መገደሉ የሚታወስ ነው።
ፕሬዝዳንቱ "ዛሬ ማንም ሰው ከዚህ በፊት አይቶት የማያውቀው ጥበቃ ያስፈልገናል። ማንም ሰው ማኅበረሰባችንን እንዲቆጣጠር አንፈቅድም" ብለዋል።
ተጠባባቂ ጠቅላይ አቃቤ ሕግ ቶድ ብላንቼ ቅዳሜ ምሽት ከተፈጸመው ጥቃት ጋር የተያያዙ ክሶች በቅርቡ እንደሚጀመሩ እና የእራት ግብዣው ላይ ከተከሰተው ጋር የተያያዙ ክሶች ግልጽ እንደሚሆኑ ተናግረዋል። "ምርመራው መጀመሩን" አጽንኦት ሰጥተውታል።
የኤፍቢአይ ዳይሬክተር ካሽ ፓቴል በበኩላቸው ከቦታው የተገኘ ረዥም የጦር መሣሪያ እና ጥይት እየተመረመረ መሆኑን እንዲሁም በእራት ግብዣው ላይ የነበሩ ሰዎችን ምስክርነት እየተቀበሉ መሆኑን ተናግረዋል። መረጃ ያለው ማንኛውም ሰው እንዲተባበርም ጠይቀዋል።
እንግዶች እየተመገቡ በነበረበት ወቅት ሁካታ መፈጠሩን እና መጀመሪያ ላይ መመገቢያ ሰሃን የወደቀ እንደመሰላቸው ትራምፕ ቢገልጹም አንዳንድ ጋዜጠኞች ከአምስት እስከ ስምንት የተኩስ ድምጽ እንደሰሙ ገልጸዋል።
እንግዶች በጠረጴዛዎች ስር ለመደበቅ ሲገደዱ የጸጥታ እና ደህንነት አባላት ቦታውን በፍጥነት ተቆጣጥረውታል።
በኋላም የእራት ግብዣው እንዲቀጥል ለማድረግ ቢሞከርም ተሰርዞ በሌላ ቀን እንዲደረግ ተወስኗል።

የፎቶው ባለመብት, Donald Trump/Truth Social
"[ግብዣውን] እንደገና እናሰናዳለን" ሲሉ የዋይት ሐውስ ዘጋቢዎች ማህበር ፕሬዝዳንት ዌይጂያ ጂያንግ ተናግረዋል።
በዝግጅቱ ላይ የተገኙት አፈ ጉባዔ ማይክ ጆንሰን ባለቤታቸው ኬሊ "ዛሬ ማታ ለአገራችን እየጸለይን ነው" ብለዋል።
የምክር ቤቱ የዴሞክራቲክ ፓርቲ መሪ የኒውዮርኩ ሐኪም ጄፍሪስ በበኩላቸው "በአሜሪካ የተከሰተው ዓመፅና ትርምስ ማብቃት አለበት" ሲሉ ተናግረዋል።
የትራምፕን ንግግር ሲጠባበቁ የቆዩት በመቶዎች የሚቆጠሩ ታዋቂ ጋዜጠኞች፣ ታዋቂ ሰዎች እና የአገር መሪዎች ከአዳራሹ በፍጥነት እንዲወጡ ተደርጓል።
የብሔራዊ ጥበቃ አባላት ሰዎች እንዲወጡ ቢፈቀድላቸውም ወዲያውኑ ተመልሰው እንዲገቡ አላደረጉም። ከውጭ ያለው ደህንነትም እጅግ ጥብቅ እንዲሆን ተደርጓል።
በእራት ግብዣው ላይ እንግዳ የነበሩት የኒውዮርክ ሪፐብሊካን ተወካይ ማይክ ላውለር የሚፈነዳ ድምጽ እንደሰሙ እና "ምን እንደሆነ አላውቅንም ነበር። ከዚያም ሁሉም ሲጮሁ ሰማችሁ" ብለዋል።
ለዓመታት የእራት ግብዣው የተካሄደበት የሂልተን ሆቴል በግብዣው ሰዓት ለመደበኛ እንግዶች ክፍት ሆኖ ቆይቷል።
የእራት ግብዣው የተካሄደበት አዳራሽ ግን ከፍተኛ ጥበቃ ቢደረግበትም ወደ እራት ግብዣው የማይገቡ ሰዎች ላይ ብዙም ፍተሻ አልተደረገም። ይህ አይነቱ ሁኔታ ባለፉት ዓመታት በመግቢያ አዳራሽ እና በሌሎች የህዝብ መሰብሰቢያ ቦታዎች የተቃውሞ ሰልፎች እና ረብሻዎች እንዲፈጠሩ ምክንያት ሆኗል።















