የተባበሩት መንግሥታት እና የተለያዩ አገራት በኢራን እና አሜሪካ መካከል የተደረሰውን ስምምነት አደነቁ

የፎቶው ባለመብት, Bloomberg via Getty Images
የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉታሬዝ ቃል አቀባይ “ዩናይትድ ስቴትስ እና ኢራን የሰላም ስምምነቱ ላይ መድረሳቸውን ይፋ በማድረጋቸው” ደስተኛ መሆናቸውን ተናገሩ።
ቃል አቀባዩ አክለውም “ይህ ግጭቱን በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት ወሳኝ እርምጃ” መሆኑን ገልጸዋል።
የጃፓን ጠቅላይ ሚኒስትር ሳናኤ ታካኢቺ በበኩላቸው የሰላም ስምምነቱን ካደነቁ የዓለም መሪዎች መካከል ናቸው።
ጠቅላይ ሚኒስትሯ ጃፓን “በሆርሙዝ ወሽመጥ ነጻ እና ደኅንነቱ የተጠበቀ እንቅስቃሴ በተግባር እንደሚረጋገጥ በብርቱ ተስፋ ታደርጋለች” ካሉ በኋላ “በኢራን የኒውክሌር እና ሌሎች ጉዳዮች ላይ የመጨረሻው ስምምነት በቅርቡ ይደረሳል” ብለው እንደሚጠብቁም ተናግረዋል።
የአውስትራሊያ ጠቅላይ ሚኒሲትር አንቶኒ አልባኔዝ ስምምነቱ “ቋሚ እና ዘላቂ ሰላም” ያመራል ብለው ተስፋ እንደሚያደርጉ ተናግረዋል።
“ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ ለማድረግ ጊዜ ቢወስድም ይህንን ወሳኝ የንግድ መተላለፊያ መልሶ መክፈት በኢነርጂ ዋጋ እና ምጣኔ ሀብት ላይ የሚያደርሰውን ጫና ይቃለላል” ብለዋል።
የኒው ዚላንድ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዊንስተን ፒተርስ “ወሳኝ እና ገንቢ ስምምነት” እንዲሁም “ውጥረትን ለመቀነስ እንዲሁም መረካካትን ለዓለም ምጣኔ ሀብት ደኅንነት ወሳኝ በሆነው ቀጣናው ለማምጣት” ቁልፍ እርምጃ መሆኑን ተናግረዋል።
ዩናይትድ ኪንግደም፣ ፈረንሳይ፣ ጀርመን እና ጣሊያን ከስምምነቱ በኋላ በጋራ ባወጡት መግለጫ አሜሪካን እና ኢራንም እንዲሁ በድርድሩ ውስጥ የተሳተፉትን በሙሉ እንኳን ደስ አላችሁ ብለዋል።
“ይህ ቀጣናዊ መረጋጋት ለማምጣት እና ዓለም ምጣኔ ሀብትን ለማረጋጋት ጥሩ ዕድል ነው” ብለዋል።
ስምምነቱ በፍጥነት እና በተሟላ መልኩ ተግባራዊ አንዲሆን ጥሪ ያቀረቡት አገራቱ የሆርሙዝ ወሽመጥ “ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እና ያለገደብ” እንዲከፈት ጠይቀዋል።




