በመቀለ ከተማ ሁለት የተለያዩ ቦታዎች የድሮን ጥቃት መፈጸሙ ተነገረ

ታትሟል
የንባብ ጊዜ: 3 ደቂቃ

በትግራይ ክልል ዋና ከተማ መቀለ ውስጥ የድሮን ጥቃት መፈጸሙን እና በሰዎች ላይ ጉዳት መድረሱን የክልሉ ባለሥልጣናት አስታወቁ።

ጥቃቱ ስለመፈጸሙ የክልሉ ኮሚዩኒኬሽን ቢሮ መግለጫ ያወጣ ሲሆን፣ የክልሉ ከፍተኛ ባለሥልጣንም ለኤኤፍፒ ዜና ወኪል አረጋግጠዋል።

የክልሉ ምክትል ፕሬዝዳንት እና የህወሓት ምክትል ሊቀመንበር አቶ አማኑኤል አሰፋ ለፈረንሳይ ዜና ወኪል ኤኤፍፒ እንደተናገሩት በመቀለ ከተማ ውስጥ ዛሬ ጠዋት የድሮን ጥቃት ተፈጽሟል።

"የመኖሪያ አካባቢን ዒላማ በማድረግ በከተማዋ ውስጥ የድሮን ጥቃት ተፈጽሟል" ያሉት አቶ አማኑኤል በጥቃቱ ስለደረሰው ጉዳት ግን ዝርዝር መረጃ እንደሌላቸው ገልጸዋል።

የክልሉ ኮሚዩኒኬሽን ቢሮ ዛሬ ሐሙስ ነሐሴ 14/2018 ዓ.ም. ዕኩለ ቀን ላይ ባወጣው መግለጫ በመቀለ ከተማ የተለያዩ አካባቢዎች በተፈጸመ ድሮን ጥቃት ከ13 ሰዎች በላይ ጉዳት እንደደረሰባቸው ገልጾ፣ ለጥቃቱ የፌደራል መንግሥቱን ተጠያቂ አድርጓል።

የፌደራል መንግሥቱም ሆነ ከመከላከያ ሠራዊቱ በክልሉ ተፈጸመ ስለተበላው የድሮን ጥቃት እስካሁን ድረስ ያሉት ነገር የለም።

ቢቢሲ ተፈጸመ ስለተባለው ጥቃት ከገለልተኛ ወገን ማጣራት አልቻለም።

የትግራይ ክልል ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ሐሙስ ነሐሴ 14/2018 ዓ.ም. የተፈጸመው አንደኛው ጥቃት በሐወልቲ ክፍለ ከተማ፣ ሞሞና ጣቢያ፣ ቀጠና 27፣ እዳማርያም አካባቢ በሚገኙ መኖሪያ ቤቶች ላይ መሆኑን አስታውቋል።

መግለጫው አክሎም በጥቃቱ 13 ሰዎች ከባድና ቀላል ጉዳት ደርሶባቸው ለሕክምና ወደ ሆስፒታል መወሰዳቸውን ገልጿል።

ሁለተኛው ጥቃት ደግሞ በኩሓ አካባቢ መፈጸሙን ገልጾ በዚህ ጥቃት ምክንያት የደረሰ ጉዳት እንደሌለ ተናግሯል።

መግለጫው የከተማዋ ነዋሪዎች ተጨማሪ ጥቃቶች ሊፈጸሙ ስለሚችሉ ጥንቃቄ እንዲያደርጉ መልዕክት አስተላልፏል።

በክልሉ የሚተዳደረው የትግራይ ቴሌቪዥን ዳእሮ በተባለው አካባቢ የተፈጸመው የድሮን ጥቃት በአቅራቢያው የነበሩ እናት እና ልጅ ላይ ጉዳት ማድረሱን ዘግቧል።

የድሮን ጥቃቱ በመኖሪያ ቤት ላይ ያደረሰው ጉዳት እና ሰላማዊ ሰዎች ሕክምና ሲደረግላቸው የሚያሳይ ምሥል አጋርቷል።

በህወሓት እና በፌደራል መንግሥቱ መካከል የሰላም ስምምነት በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ ከተፈረመ በኋላ በመቀለ የድሮን ጥቃት ሲፈጸም ይህ የመጀመሪያው ነው።

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በክልሉ የተለያዩ አካባቢዎች የተፈጸሙ የድሮን ጥቃቶች በህወሓት እና በፌደራል መንግሥቱ መካከል የተፈጠረው ውጥረት እየተባባሰ መምጣቱን ያሳያሉ።

የትግራይ ክልል ባለሥልጣናት የፌደራል መንግሥቱ በተደጋጋሚ የሚፈጸማቸውን የድሮን ጥቃቶች አውግዘዋል።

ማክሰኞ ነሐሴ 12/2018 ዓ.ም. ከመቀለ 15 ኪሎ ሜትር ርቃ በምትገኘው ዳንዴራ አቅራቢያ የድሮን ጥቃት ተፈጽሞ አንድ ሰው መግደሉን እና አንድ ሰው ላይ ደግሞ ጉዳት መድረሱን የክልሉ ባለሥልጣናት አስታውቀዋል።

የክልሉ ኮሙኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ ዶ/ር አብርሃም ሐጐስ ረቡዕ ዕለት በሰጡት መግለጫ ማክሰኞ ነሐሴ 12/2018 ዓ.ም. በእንደርታ ወረዳ በቀዳማይ ወያነ ቀበሌ ዳንዴራ በሚባል ቦታ "በንፁሃን ዜጐች ላይ የድሮን ጥቃትና የአንቶኖቭ ድብደባ ተፈፅሟል"ብለዋል።

በደቡብ ትግራይ ነሐሴ 4/2018 ዓ.ም. በራያ አላማጣ መረዋ በተባለ አካባቢ በተፈጸመ ሌላ ጥቃት ደግሞ አንድ ሰው መገደሉ እና ሦስት ሰዎች መጎዳታቸው ተገልጿል።

በወቅረቱ ቢቢሲ ያነጋገራቸው ምንጮች የድሮን ጥቃቱ ከአላማጣ ከተማ 50 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በሚገኝ ስፍራ ሦስት ጊዜ መፈጸሙን ተናግረዋል።

የፌደራል መንግሥቱ በተደጋጋሚ ተፈጽመዋል ስለተባሉ ጥቃቶች እስካሁን ድረስ በይፋ ያለው ነገር የለም።

በፌደራል መንግሥቱ የተሰየመውን የክልሉን ጊዜያዊ አስተዳደር የህወሓት መሪዎች ከተቆጣጠሩ በኋላ ባለፉት ወራት በሁለቱም ወገኖች መካከል የጦርነት ዝግጅት እየተደረገ መሆኑ ሲነገር ቆይቷል።

ያለው ውጥረትም እየተባባሰ ወደ ግጭት ሊያመራ ይችላል የሚል ስጋት ሲገለጽ የነበረ ሲሆን፣ በአንዳንድ ቦታዎች ላይ ግጭቶች እና የድሮን ጥቃቶች መፈጸማቸው ተዘግቧል።

ሐምሌ 25 ቀን የፌደራል መንግሥት እና የትግራይ ኃይሎች "ሸረሪና" በተባለ የሱዳን አዋሳኝ ሥፍራ ግጭት ውስጥ ገብተው ነበር።

የፈረንሳዩ የዜና ወኪል ኤኤፍፒ ግጭቱ በከባድ መሣሪያ እና ድሮን የታገዘ እንደነበር እንዲሁም ፍንዳታዎችን፣ የከባድ መሣሪያ ተኩስ እና የአውሮፕላኖችን ድምጽ መሰማቱን ዘግቧል።

በወቅቱ በህወሓት ሊቀ መንበር ዶ/ር ደብረፅዮን ገብረሚካኤል የሚመራው የክልሉ አስተዳደር በዕለቱ ባወጣው መግለጫ፣ ፌደራል መንግሥት "ግልፅ ጦርነት ከፍቷል" ሲል ከስሷል።

የፌደራል መንግሥት ስለ ክስተቱ ይፋዊ አስተያየት ባይሰትም የመስኖ እና ቆላማ አካባቢ ሚኒስትር እንዲሁም የገዢው ብልጽግና ፓርቲ ሥራ አስፈጻሚ አባል የሆኑት ዶ/ር አብርሃም በላይ ግን የህወሓት ኃይሎች "ጦርነት እንደከፈቱ" በመግለጽ ከስሰዋል።

የህወሓት መሪዎች ባለፉት ሳምንታት በክልሉ ውስጥ ባካሄዷቸው ስብሰባዎች ገዢውን ብልጽግና ፓርቲን ለማስወገድ ሲዝቱ ከመሰማታቸው በተጨማሪ፣ በክልሉ መገናኛ ብዙኃን ላይ ተመሳሳይ ዘገባዎች እየቀረቡ ነው።

እንዲሁም የፌደራል መንግሥቱ በትግራይ ክልል ውስጥ ስለተከሰቱ ጥቃቶች አስካሁን በይፋ ያለው ነገር ባይኖርም በሚቆጣጠራቸው መገናኛ ብዙኃን በኩል የህወሓት መሪዎች ለጦርነት እየተዘጋጁ ነው የሚል ዘገባ እየቀረበ ነው።