ቀጥታ, ፕሬዝዳንት ትራምፕ ወሳኙን የኢራን የነዳጅ ማስተላለፊያ ደሴትን በቅርቡ እንደሚቆጣጠሩ አስታወቁ

የኢራን እና የአሜሪካ ግጭት ከዕለት ወደ ዕለት እየተባባሰ ባለበት በአሁኑ ወቅት ፕሬዝዳንት ትራምፕ ዛሬም በድጋሚ በኢራን ላይ ከባድ ጥቃት እንደሚፈጸም እና በቅርቡም አሜሪካ የኻርግ ደሴትን እንደምትቆጣጠር አስታወቁ።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ለዓለም ዋንጫ አሜሪካ እንዳይገባ የተከለከለው ሶማሊያዊው ዳኛ የአውሮፓ ጨዋታን እንዲመራ ተመረጠ

    አሜሪካ እንዳይገባ ተከልክሎ በዓለም ዋንጫ ላይ የመዳኘት ዕድልን የተነፈገው ሶማሊያዊ የእግር ኳስ ዳኛ ኦማር አርታን የአውሮፓ ሱፐር ካፕ ጨዋታን እንዲዳኝ ተመረጠ።

    ሶማሊያዊው ዳኛ በዓለም ዋንጫ ላይ እንዳያጫውት መደረጉ ከበርካቶች ዘንድ ተቃመሞን ያስከተለ ሲሆን፣ የአውሮፓ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ግን ሌላ ጨዋታ እንዲዳኝ መርጦታል።

    የ34 ዓመቱ አርታን በነሐሴ ወር በፈረንሳዩ ፓሪስ ሳን ዠርሜን እና በእንግሊዙ አስቶንቪላ መካከል ኦስትሪያ ሳልዝበርግ ውስጥ የሚካሄደውን ግጥሚያ እንዲመራ መመረጡን ፌዴሬሽኑ አረጋግጧል።

    ሶማሊያዊው ዳኛ ከአውሮፓውያኑ 2018 ጀምሮ በዳኝነት በፊፋ የተመዘገበ ሲሆን፣ ባለፈው የአውሮፓውያን ዓመት ደግሞ የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን የዓመቱ ዳኛ ብሎ መርጦታል። በተጨማሪም የዚህ ዓመቱን የዓለም ዋንጫ ከሚዳኙ ዳኞች መካከል አንዱ ነበር።

    አሜሪካ ዳኛውን ወደ ግዛቷ እንዳይገባ በመከልከሏ በዓለም ዋንጫ የማጫወት ዕድሉ የተጨናገፈበነት አርታን ወደ አገሩ ሲመለስ ደማቅ አቀባበል በተደረገለት ጊዜ በቀጣዩ የዓለም ዋንጫ በዳኝነት እንደሚሳተፍ ተስፋውን ገልጿል።

  2. ፕሬዝዳንት ትራምፕ ወሳኙን የኢራን የነዳጅ ማስተላለፊያ ደሴትን በቅርቡ እንደሚቆጣጠሩ አስታወቁ

    የኢራን እና የአሜሪካ ግጭት ከዕለት ወደ ዕለት እየተባባሰ ባለበት በአሁኑ ወቅት ፕሬዝዳንት ትራምፕ ዛሬም በድጋሚ በኢራን ላይ ከባድ ጥቃት እንደሚፈጸም እና በቅርቡም አሜሪካ የኻርግ ደሴትን እንደምትቆጣጠር አስታወቁ።

    ፕሬዝዳንቱ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ እንዳሰፈሩ “ባሕር ኃይሏ፣ የአየር ኃይሏ፣ የአየር መከላከያ ሥርዓቷ እና ሁሉም የጥቃት አቅሟ” ወድሟል ያሏት ኢራንን ዳግም ዛሬ “ሌሊት በኃይለኛው ትመታለች” ብለዋል።

    "ቬንዙዌላ ላይ እንዳደረግነው ብዙም ሳይቆይ የኻርግ ደሴትን እና ሌሎች የነዳጅ መሠረተ ልማቶችን እንይዛለን፤ በዚህም የኢራንን የነዳጅ እና የጋዝ ገበያን ሙሉ ለሙሉ እንቆጣጠራለን” ሲሉ ዕቅዳቸውን አሳውቀዋል።

    ከኢራን ጋር የሚደረገው ጦርነት ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ ፕሬዝዳንት ትራምፕ የኢራን ዋነኛው የነዳጅ ማስተላለፊያ የሆነውን ኻርግ ደሴትን እንደሚቆጣጠሩ በተደጋጋሚ ሲናገሩ ነበር።

    በሰሜናዊ የባሕረ ሰላጤው አካባቢ የሚገኘው ኻርግ ደሴት ኢራን ወደ 90 በመቶ የሚሆነውን የነዳጅ ምርቷን ለቀሪው ዓለም የምታቀርብበትት ዋና መተላለፊያ ነው።

    ደሴቱ ከኢራን የባሕር ዳርቻ አቅራቢያ የሚገኝ ሲሆን፣ ወደ ሁለት ሚሊዮን በርሜል መጫን የሚችሉ ግዙፍ ድፍድፍ ነዳጅ ጫኝ መርከቦች ላይ ነዳጅ ለመሙላት የሚያስችል ጥልቅ የውሃ ክፍል አለው።

  3. የኢራን ጥቃት በባሕረ ሰላጤው አገራት ላይ ጉዳት አደረሰ

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ አሜሪካ በደቡባዊ ኢራን ውስጥ ለፈጸመችው ጥቃት በባህሬን፣ በኩዌት እና በዮርዳኖስ በሚገኙ የጦር ሰፈሮቿ ላይ ጥቃት መፈጸሙን አረጋግጧል።

    የባህሬን መገናኛ ብዙኃን እንደዘገቡት ዛሬ ሐሙስ ጠዋት በተፈጸመው የኢራን የድሮን ጥቃት አንዲት የ11 ዓመት ታዳጊ ጉዳት ደርሶባታል።

    የአሜሪካ ባሕር ኃይል ሰፈር በሚገኝባት ባህሬን ላይ ኢራን በፈጸመችው ጥቃት ቤቶች እና መኪኖች መውደማቸውን የአገሪቱ ባለሥልጣናት አስታውቀዋል።

    ዮርዳኖስ ከኢራን የተተኮሱ 20 ሚሳዔሎችን መትታ መጣሏን ስትገልጽ፣ የኩዌት ጦር ኃይል ደግሞ ከኢራን የተወነጨፉ መሳሪያዎችን አየር ላይ ማስቀረቱን አስታውቋል።

  4. አሜሪካ በኦማን ባሕረ ሰላጤ የኢራን መርከብ ላይ ጥቃት መፈፀሟ ተነገረ

    አሜሪካ ወሳኝ እቃዎችን የጫነች መርከብ ላይ ዛሬ ጠዋት ጥቃት መፈፀሟን ሪፖርት አመለከተ።

    በኢራን መንግሥታዊ የዜና ወኪል መህር ኒውስ የጠቀሳቸው የሲሪክ አስተዳዳሪ ጥቃቱ በኦማን ባሕረ ሰላጤ መፈፀሙን ተናግረዋል።

    ከቅጽበታዊው ጥቃት አምስት መርከበኞችን መታደግ ተችሏልም ብለዋል።

    መርከቧ ጥቃት የተፈፀመባት ከኦማን ኻሳብ ከተማ ወደ ኢራን ከተማ - ሲሪክ ለመጓዝ ከተነሳች በኋላ ነበር።

    ጥቃቱን በተመለከተ አሜሪካ እስካሁን ያለችው ነገር የለም።

  5. ካናዳ ታዳጊዎች ማኅበራዊ ሚዲያ እንዳይጠቀሙ እገዳ ልትጥል ነው

    ካናዳ ከ16 ዓመት በታች ለሆኑ ታዳጊዎች የማኅበራዊ ሚዲያን ለማገድ የሚያስችል ሕግ አቀረበች።

    ሕጉ ባለፈው ዓመት በአውስትራሊያ ከጸደቀው ጋር ተመሳሳይ ነው ተብሏል።

    ነገር ግን ከአውስትራሊያው ሕግ በተለየ የቴክኖሎጂ ኩባንያዎች ታዳጊዎቹን ለመከላከል የሚያስችል ፖሊሲዎች ካሏቸው ግዴታ ውስጥ አይገቡም።

    ሕጉ የሰው ሠራሽ ቻትቦቶች እንዲሁም በኦንላየን “ያሉጎጂ ይዘቶችን” ለመከላከል ሰፊ እርምጃዎችን ይወስዳል ተብሏል።

    ተቆጣጣሪዎች የቴክኖሎጂ ኩባንያዎች ሕጉን ማክበራቸውን እንዲከተተሉ ያደርጋል።

    አንዳንድ የመናገር ነጻነት አቀንቃኞች ሳንሱርን ያስፋፋል ሲሉ ስጋታቸውን ገልጸዋል።

    ሕጉ ለምክር ቤት የቀረበው በሚቀጥለው ሳምንት በፈረንሳይ ከሚካሄደው የቡድን ሰባት አገራት ስብሰባ በፊት ነው።

    ይህ ደህንነቱ የተጠበቀ የማኅበራዊ ሚዲያ ረቂቅ ሕግ ረቡዕ ዕለት በባህል ሚኒስትር ማርክ ሚለር ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀርቦ ነበር።

    በሳምንቱ መጀመሪያ ላይ ሚለር እንዳሉት “ልጆች እየሞቱ በመሆኑ” በኦንላየን የሚደርሱ ጉዳቶችን የሚመለከት ሕግ ማውጣትን የካናዳ መንግሥት ቅድሚያ የሚሰጠው ጉዳይ ነው።

    “ልጆች በዚህች አገር ደህንነታቸው የተጠበቀ መሆኑን ለማረጋገጥ ሁሉንም ተገቢ እርምጃዎች እንወስዳለን ማለት በቂ ነው” ሲሉ ለጋዜጠኞች ተናግረዋል።

  6. ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥን ሙሉ ለሙሉ ስትዘጋ የነዳጅ ዋጋ ጭማሪ አሳየ

    አሜሪካ ለሦስተኛ ቀን በኢራን ላይ ጥቃት መፈጸሟን ተከትሎ የኢራን ጦር ኃይል ማዕከላዊ ዕዝ የሆርሙዝ ወሽመጥ ነዳጅ ጫኝ እና የንግድ መርከቦች ጨምሮ ለሁሉም የባሕር ላይ እንቅስቃሴ ዝግ መሆኑን አስታወቀ።

    ባለፉት ቀናት አሜሪካ እና ኢራን ጥቃት ሲፈጽሙ የቆዩ ሲሆን፣ አሜሪካ በኢራን ውስጥ የሚገኙ ዒላማዎችን ስትመታ ኢራን በአጸፋው በፋርስ ባሕረ ሰላጤ አገራት ውስጥ በሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሰፈሮች እና በእስራኤል ላይ ጥቃት ፈጽማለች።

    ረቡዕ ሌሊት በአሜሪካ የተፈጸመውን ጥቃት ተከትሎ ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥን ከዘጋች በኋላ አብዮታዊ ዘቡ በሕገወጥ መንገድ ለማለፍ ሞክረዋል ያላቸውን ሁለት መርከቦችን መምታቱን አስታውቋል።

    የኢራን ወታደራዊ ማዘዣ የሆነው ኻታም አል-አምቢያ እንዳስታወቀው “በቀጣናው ባለው አለመረጋጋት ምክንያት የሆርሙዝ ወሽመጥ ለሁሉም መርከቦች ተዘግቷል” በማለት ለማለፍ የሚሞከሩ መርከቦች ላይ እርምጃ እንደሚወሰድ አስታውቋል።

    የወሳኙ የባሕር መተላለፊያ መዘጋት ለወራት ጋብ ብሎ የነበረው የአሜሪካ እና ኢራን ጦርነት እየተባባሰ መሆኑን የሚያመለክት ነው። ከፍተኛ መጠን ያለው የዓለም የነዳጅ ፍጆታ የሚተላለፍበት ወሽመጥ በመዘጋቱ የነዳጅ ዋጋ ላይ ጭማሪ ተከስቷል።

    ጦርነቱ በየካቲት ወር መጨረሻ ገደማ ከተቀሰቀሰ በኋላ ኢራን ሆርሙዝን ሙሉ ለሙሉ ከመዝጋት ይልቅ በመርከቦች እንቅስቃሴ ላይ ገደቦች ጥላ ቁጥጥር ስታደርግ ነበር። በተጨማሪም የባሕር መተላለፊያውን የሚመለከት አዲስ ሕግ እና አሠራር በማውጣት ሆርሙዝን በቁጥጥሯ ስር ለማስገባት ስትሠራ ቆይታለች።

    ይህ የኢራን ውሳኔ የተሰማው ኢራን የአሜሪካ የጦር ሄሊኮፕተርን መትታ ከጣለች በኋላ ከአሜሪካ ተደጋጋሚ ጥቃት ስለተፈጸመባት ነው።

    ሆርሙዝ ወሽመጥ ዓለም ለፍጆታው ከሚያስፈልገው 20 በመቶው ነዳጅ ዘይት እና ጋዝ ከባሕረ ሰላጤው አገራት በመነሳት በየቀኑ የሚተላለፍበት ወሳኝ የባሕር መስመር ነው።

  7. እስራኤል በደቡባዊ ሊባኖስ በፈፀመችው ጥቃት በርካቶች መገደላቸው ተዘገበ

    እስራኤል ትናንት በደቡባዊ ሊባኖስ በፈፀመችው ጥቃት ቢያንስ 17 ሰዎች መገደላቸውን የሊባኖስ መገናኛ ብዙኃን ዘገበ።

    ኤንኤንኤ እንደዘገበው ዘጠኙ ሰዎች የተገደሉት ታይር ደባ በተባለው ከተማ ውስጥ ነው።

    በዲየር ቃኖን ኤል ናህር መንደር አቅራቢያ እስራኤል በፈፀመችው ሁለት የአየር ድብደባዎች ሌሎች ሦስት ሰዎች የተገደሉ ሲሆን ሁለት ሰዎች ደግሞ በደቡባዊ ምሥራቅ ታይር በምትገኘው ሴዲቂን ተገድለዋል።

    በኋላ ላይም በሲደን ከተማ እና ማሳክን አል ሻቢያ አካባቢ በተፈፀሙ ጥቃቶች ሦስት ሰዎች መገደላቸው ተገልጿል።

    በኢራን የሚደገፈው ታጣቂ ቡድን ሄዝቦላህ በበኩሉ በእስራኤል ወታደሮች ላይ ተጨማሪ ጥቃቶችን መፈፀሙን እና የአገሪቷን ደቡባዊ ክፍል መቆጣጠሩን ገልጿል።

    ማክሰኞ ዕለትም በእስራኤል ጥቃት 15 ሰዎች መገደላቸው የተገለጸ ሲሆን እስራኤል በሄዝቦላህ ላይ የምታደርገውን ዘመቻ መቀጠል እንድታቆም ከኢራን የተሰጣትን ማስጠንቀቂያ ውድቅ አድርጋለች።

    የኢራን መሪዎች ጦርነቱን ለማቆም ከአሜሪካ እና እስራኤል ጋር የሚደረገው ማንኛውም ስምምነት ሊባኖስን እንዲያካትት ይፈልጋሉ። ይህም ከአሜሪካው ፕሬዚደንት ትራምፕ ጋር የሚደረገውን ድርድር አወሳስቦታል።

    የሊባኖስ መገናኛ ብዙኃን እንደዘገበው የእስራኤል የአየር እና የከባድ መሣሪያ ጥቃት ረቡዕ ዕለትም በአገሪቷ ደቡባዊ ክፍል የተለያዩ ከተሞች እና መንደሮች ላይም ተጠናክሮ ቀጥሏል።

    እስራኤል የረቡዕ ዕለቱን ጥቃት በተመለከተ ወዲያውኑ የሰጠችው አስተያየት የለም። ሆኖም ቀደም ብሎ በታይር ሄዝቦላህ የሚጠቀምባቸውን ስድስት መሠረተ ልማቶች እና በበርካታ የደቡባዊ ሊባኖስ አካበቢዎች የሚገኙ መሣሪያዎቹን እንዳወደመች ገልጻለች።

  8. አሜሪካ አዲስ ጥቃት ከፈጸመች በኋላ ኢራን በባሕረ ሰላጤው የሚገኙ የጦር ሰፈሮችን ዒላማ አደረገች

    ዶናልድ ትራምፕ ኢራንን “ክፉኛ” እንደበድባታለን ማለታቸውን ተከትሎ የአሜሪካ ጦር ጥቃት በመፈጸሙ ቴህራን በባሕረ ሰላጤው በሚገኙ ጦር ሰፈሮች ላይ የአጸፋ እርምጃ ወሰደች።

    የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም) ፕሬዚዳንት ትራምፕ ኢራን ጦርነቱን ለማቆም የሚያስችል “ስምምነትን ለመቀበል ብዙ ጊዜ ፈጀች” ካሉ በኋላ ለተከታታይ ሁለት ቀናት “ራስን የመከላከል ጥቃቶችን” መፈጸሙን አስታውቋል።

    በምላሹ ኢራን በባሕሬን፣ ኩዌት የሚገኙ የጦር ሰፈሮች ላይ ጥቃት መፈጸሟን አስታውቃለች።

    እነዚህ ጦር ሰፈሮች ከዚህ ቀደምም ተመሳሳይ የአጸፋ እርምጃ የወሰደችባቸው ናቸው።

    ሁለቱ አገራት እርስ በእርስ የሚያደርጉት መታኮስ በሚያዚያ ወር የተደረሰውን የተኩስ አቁም አደጋ ላይ ጥሎታል።

    አሜሪካ የቴህራን የአየር መከላከያዎችን፣ ራዳሮችን እና ሌሎች ተቋማት ላይ ድብደባ ከፈጸመች በኋላ በአገሪቱ ደቡባዊ ክፍል በሆርሙዝ አቅራቢያ አካባቢ ፍንዳታ ተሰምቷል።

    የእስላማዊ አብዮታዊ ዘብ በበኩሉ በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚያልፉ ሁለት የነዳጅ መርከቦች ላይ ጥቃት መፈጸሙን የኢራን መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    ስለ ጥቃቱ ወዲያውኑ ማረጋጋጫ የሰጠ አካል የለም።

    ይህ የተከሰተው የኢራን መገናኛ ብዙኃን የሆርሙዝ ወሽመጥ “ለማንኛውም ዓይነት መርከብ ሙሉ በሙሉ ዝግ መሆኑን” ካስታወቁ በኋላ ነው።

    ሴንትኮም ግን “የንግድ መርከቦች በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል እያለፉ ነው” ሲል መግለጫ ሰጥቷል።

    በወሽመጡ የሚያልፉ መርከቦች ላይ ጥቃት ከደረሰ እና መስመሩ ሙሉ በሙሉ ዳግም ከተዘጋ በኋላ የነዳጅ ዋጋ ጭማሪ አሳይቷል።

    በእስያ ገበያ ዛሬ ማለዳ ብሬንት ድፍድፍ ነዳጅ ዘይት በበርሜል የ2 በመቶ ጭማሪ በማሳየት 95 ዶላር መሸጥ ጀምራል።

    የተባበሩት መንግሥታት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ መካከለኛው ምሥራቅ “ወደ ማይወጣው ቀውስ ውስጥ እየገባ ነው” ሲሉ አስጠንቅቀው በቅርብ ጊዜ የተከሰቱት ግጭቶች “የተኩስ አቁሙ የተኩሱን መጠን መቀነስ ብቻ ላይ አስተዋጽኦ ያደረገ ይመስላል” ብለዋል።

    “የተኩስ መጠኑን መቀነስ ወደ ሙሉ ጦርነት እንዲሻገር ማድረግ የለብንም። ሁሉም ወገኖች ወደ ዲፕሎማሲያዊ መፍትሄ መምጣት አለባቸው። ተጨማሪ ጥቃት አያስፈልግም። ከዚህ በኋላ ምንም ሰበብ አያስፈልግም” ሲሉ በመግለጫቸው ላይ ጠቅሰዋል።

  9. አሜሪካ በባሕረ ሰላጤው የነዳጅ መርከብ መምታቷን ካስታወቀች በኋላ ሦስት የሕንድ መርከበኞች ጠፉ

    የአሜሪካ ጦር "ከኢራን ነዳጅ ለማጓጓዝ ሙከራ በማድረግ የአሜሪካን እገዳ ጥሷል" የተባለ የነዳጅ መርከብን በባሕረ ሰላጤዋ ኦማን አወደመች።

    የአሜሪካ ማዕከላዊ እዝ በኤክስ ገጹ ባሰፈረው ጽሑፍ መርከበኞቹ ከአሜሪካ የተሰጣቸውን አቅጣጫ በተደጋጋሚ ማክበር ባለመቻላቸው የጦር አውሮፕላኑ "የፓላውን ሰንደቅ ዓላማ በምታውለበልበው ሴትቤሎ መርከብ" በሞተሯ ክፍል ላይ ጥቃት በመፈፀም ማውደሙን ገልጿል።

    በኦማን ባሕር ዳርቻ ሴትቤሎ ላይ ጥቃት ከተፈፀመ በኋላ የሕንድ መንግሥት ሦስት መርከበኞቹ እንደጠፉ እና 21 ሕንዳውያን የመርከበኞች ቡድን መታደግ መቻሉን ገልጿል።

    “በቀጠናው የንግድ መርከቦች እና የሲቪል መሠረተ ልማቶች ላይ የሚፈፀመው ጥቃት ሊቆም ይገባል" ብሏል።

    ቴህራን የሆርሙዝ ወሽመጥን ከዘጋች በኋላ የአሜሪካ ጦር የኢራንን ወደብ አገልግሎት እንዳይሰጥ አግዷል።

    ወሽመጡ 20 በመቶ የሚሆን የዓለም ነዳጅ እና ጋዝ የሚጓጓዝበት መስመር ነው።

    የአሜሪካ ጦር እገዳ ከጣለ አንስቶ ስምንት መርከቦችን ያወደመ ሲሆን ሌሎች 134 መርከቦችን ደግሞ አቅጣጫ እንዲለውጡ ማድረጉን ማዕከላዊ እዟ አስታውቋል።

  10. ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ “ዛሬም ኢራንን ክፉኛ እንመታለን” አሉ

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ዛሬ ረቡዕ ባደረጉት ንግግር ኢራንን “ክፉኛ እንመታለን” ሲሉ ዛቱ።

    ፕሬዝዳንቱ እንዳሉት ሁለቱ አገራት የሰላም ስምምነት ላይ ለመድረስ “ቢቃረቡም” ኢራን “መዘግየቷን” ጠቅሰዋል።

    “ትናንት በጣም ደብድበናቸዋል። ዛሬም ክፉኛ እንመታቸዋለን” በማለት ፕሬዝዳንቱ አስጠንቅቀዋል።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ኢስማኤል ባጋይ “የትኛውንም ጥቃት ወይም ዛቻ ችላ ብለን አናልፍም” ብለዋል።

    ትራምፕ ግን ኢራን ድርድሩን “በጣም በማጓተቷ አሁን ዋጋውን ትከፍላለች” ሲሉ ተናግረዋል።

    “የኢራን ጦር ተዳክሟል። የባሕር እና የአየር ኃይላቸው አለ ለማለት አያስደፍርም። ሙሉ በሙሉ ወድቀዋል” በማለት በትሩዝ ሶሻል የማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ጽፈዋል።

    ኢራን የአሜሪካ ተዋጊ ሄሊኮፕተርን መትታ መጣሏን ተከትሎ አሜሪካ የአጸፋ እርምጃ ወስዳለች።

    በምላሹም ኢራን በባሕረ ሰላጤው አገራት የሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሰፈሮችን ዒላማ ያደረጉ የሚሳዔል እና የድሮን ጥቃቶችን መፈጸሟን አስታውቃለች።

  11. እስራኤል በሊባኖስ በፈጸመችው የአየር ጥቃት ቢያንስ 17 ሰዎች መገደላቸው ተዘገበ

    እስራኤል በደቡብ ሊባኖስ ውስጥ በፈጸመችው የአየር ጥቃት ቢያንስ 17 ሰዎች መገደላቸውን የአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ።

    የሊባኖስ ብሔራዊ የዜና አገልግሎት እንደዘገበው ታይር ዳባ በተባለ አካባቢ በተከታታይ በተፈጸመ ጥቃት ዘጠኝ ሰዎች ተገድለዋል።

    ኢራን የምትደግፈው ሄዝቦላህ በደቡብ ሊባኖስ የእስራኤል ወታደሮች በተቆጣጠሯቸው አካባቢዎች ተጨማሪ ጥቃቶች መፈጸሙን አስታውቋል።

    ትናንት ማክሰኞ እስራኤል በሊባኖስ በፈጸመችው ጥቃት 15 ሰዎች መገደላቸውም ተዘግቧል።

    እስራኤል በሄዝቦላህ ላይ የከፈተችውን ዘመቻ እንዳትገፋበት ኢራን ብታሳስብም እስራኤል ጥቃት መፈጸሟን ቀጥላለች።

    ኢራን ከአሜሪካ ጋር ያለው ጦርነት የሚያከትመው ስምምነታቸው ሊባኖስን የሚያካትት ከሆነ ብቻ መሆኑን ገልጻለች። ድርድሩን የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ውስብስብ አድርገውታል ስትልም ከስሳለች።

    ትራምፕ በበኩላቸው ኢራን ድርድሩን “በጣም በማጓተቷ አሁን ዋጋውን ትከፍላለች” ሲሉ ዝተዋል።

    ኢራን የአሜሪካ ተዋጊ ሄሊኮፕተርን መትታ መጣሏን ተከትሎ አሜሪካ የአጸፋ እርምጃ ወስዳለች።

    በምላሹም ኢራን በባሕረ ሰላጤው አገራት የሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሰፈሮችን ዒላማ ያደረጉ የሚሳዔል እና የድሮን ጥቃቶችን መፈጸሟን አስታውቃለች።

  12. ኢራን ከአሜሪካ ጋር የምታደርገው ድርድር የሚቀጥልበትን መንገድ እንደምታጤን አስታወቀች

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ፤ ቴህራን ከዋሽንግተን ጋር የምታደርገው ድርድር የሚቀጥልበትን መንገድ እንደምታጤነው አስታወቁ።

    ኢራን የአሜሪካን ሄሊኮፕተር መትታ መጣሏን ተከትሎ አሜሪካ የአጸፋ እርምጃ ወስዳለች።

    ቃል አቀባዩ ኢስማኤል ባጋይ፤ ኢራን እና አሜሪካ የተኩስ ልውውጥ ማድረጋቸውን ተከትሎ “ዲፕሎማሲ በባቦ ሜዳ አይከናወንም። የዲፕሎማሲ ሒደት እንዲቀጥል ለማስቻል በተወሰነ መጠን ለእንቅስቃሴ ክፍተት መስጠት ያስፈልጋል” ብለዋል።

    አሜሪካ “የሚቃረኑ መልዕክቶች በማስተላለፍ የድርድር ሒደቱን እየጎዳች ነው” ሲሉ ወንጅለዋል። “አቋም እና ፍላጎት በመለወጥ” እንዲሁም “በተደጋጋሚ የተኩስ አቁም በመጣስም” አሜሪካን ከስሰዋል።

  13. ኢራን “ድርድሩን በማጓተቷ ዋጋ ትከፍላች” ሲሉ ትራምፕ አስጠነቀቁ

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ኢራን ድርድሩን “በጣም በማጓተቷ አሁን ዋጋውን ትከፍላለች” ሲሉ አስጠነቀቁ።

    “የኢራን ጦር ተዳክሟል። የባሕር እና የአየር ኃይላቸው አለ ለማለት አያስደፍርም። ሙሉ በሙሉ ወድቀዋል” በማለት በትሩዝ ሶሻል የማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ጽፈዋል።

    ፕሬዝዳንቱ አክለውም “ኢራን ታወራለች እንጂ ምንም አትከውንም። የመካከለኛዋ ምሥራቅ ጉልበተኛ ሞታለች” ብለዋል።

    “እነሱን የሚጠቅም ስምምነት ላይ ለመድረስ ለድርድር በጣም ረዥም ጊዜ ወስደዋል። አሁን ዋጋውን ይከፍላሉ” በማለትም ዝተዋል።

    ኢራን በባሕረ ሰላጤው አገራት ውስጥ የሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሰፈሮችን ዒላማ እንደምታድርግ አስጠንቅቃለች።

    ኢራን የአሜሪካን ሄሊኮፕተር መትታ መጣሏን ተከትሎ ዋሽንግተን የአጸፋ እርምጃ ወስዳለች።

  14. አሜሪካ እንዳይገባ የተከለከለው ሶማሊያዊ የዓለም ዋንጫ ዳኛ ሞቃዲሾ ሲደርስ ደማቅ አቀባበል ተደረገለት

    የዓለም ዋንጫን እንዲዳኙ ከተመረጡት ዳኞች ማከከል አንዱ ሆነው ሶማሊያዊ ዳኛ ኦማር አርታን አሜሪካ እንዳይገባ ከተከለከለ በኋላ ወደ አገሩ ሲመለስ ደመቅ አቀባበል ተደረገለት።

    በዓለም ዋንጫ የመጀመሪያው ሶማሊያዊ ዳኛ ይሆናል ተብሎ ሲጠበቅ የነበረው አርታን ሞቃዲሾ ሲደርስ ሶማሊያውያን የአገራቸውን ስም እንዲከላከሉ ጥሪ አቀረበ።

    አርታን ሞቃዲሾ አውሮፕላን ማረፊያ ሲደርስ የአገሪቱ ባለሥልጣናት፣ የብሔራዊ እግር ኳስ ፌደሬሽን ተወካዮች እና የሲቪል ማኅበረሰብ አባላት ደማቅ አቀባበል አድርገውለታል።

    በአውሮፕላን ማረፊያው ከተገኙ ሰዎች መካከል የቤተሰብ አባላቱም ይገኙበታል ተብሏል።

    በአውሮፕላን ማረፊያው አጭር ንግግር ያደረገው ዳኛው ለተደረገለት አቀባበል አመስግኖ በሚቀጥለው ዓለም ዋንጫ ላይ ለመሳተፍ ያለውን ተስፋ ገልጿል።

    “ቃል የምገባላችሁ ነገር ፈጣሪ ካለ በሚቀጥለው እሳተፋለሁ። እናም ሶማሊያውያን በዚያ ደስተኛ ይሆናሉ፤ ሁላችንም የሶማሊያን ስም መከላከል አለብን” ብሏል።

    አርታን በዓለም ዋንጫ ላይ ዳኛ ሆኖ የተመረጠ የመጀመሪያው ሶማሊያዊ ሲሆን፣ ሰኞ ዕለት ማያሚ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ከደረሰ በኋለ እንዳይገባ በመከልከሉ በሌላ ሰው ተተክቷል።

    አርታን ወደ አሜሪካ እንዳይገባ ለምን እንደተከለከለ በይፋ ባይገለጽም፤ ነገር ግን የዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር የጉዞ እገዳ ከጣለባቸው በርካታ አገራት መካከል ሶማሊያ አንዷ ናት።

    በአውሮፕላን ማረፊያው ለጋዜጠኞች በሰጠው መግለጫ ወጣቶች በአገራቸው ተስፋ እንዳይቆርጡ መክሯል።

    “ሶማሊያ ጥሩም ሆነች መጥፎ የኛ ናት፤ ፓስፖርቱ የኛ ነው፤ የምንጋራው እኛው ነን። በጋራ ሆነን እንከላከለዋለን” ብሏል።

    ዓለም አቀፉ ዳኛ የተሰማውን ከመግlጽ ውጪ በስፋረው ከተገኙ ጋዜጠኞች ለቀረቡለት ጥያቄዎች ምላሽ አልሰጠም።

    ኦማር አርታን ዛሬ ከሰዓት በሞቃዲሾ ውስጥ የሚያካሄድ ጨዋታ ላይ ተገኝቶ አቀባበል ይደረግለታል እንዲሁም ግጥሚያውን ይመለከታል ተብሎ ይጠበቃል።

  15. ኢራን የአሜሪካ ጦር ሰፈሮች የሚገኙባቸው የባሕረ ሰላጤው አገራትን ዒላማ እንደምታድርግ አስጠነቀቀች

    ኢራን በባሕረ ሰላጤው አገራት ውስጥ የሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሰፈሮችን ዒላማ እንደምታድርግ እና አገራቱ ግዛታቸውን አሜሪካ ለምትፈጽምባት ጥቃት እንዳይፈቅዱ አስጠነቀቀች።

    አሜሪካ እና ኢራን የአጸፋ ጥቃት እየፈጸሙ ባለበት በአሁኑ ጊዜ የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ዛሬ ረቡዕ እንዳለው ጎረቤቶቿ የፋርስ ባሕረ ሰላጤው አገራት አሜሪካ እና እስራኤል ከቀጣናው አገራት በመነሳት የሚፈጽሙባትን ጥቃት የማስቀረት “ሕጋዊ እና ሞራላዊ ኃላፊነት” አለባቸው ብላለች።

    በፕሬዝዳንት ትራምፕ ትዕዛዝ የአሜሪካ ኃይሎች በኢራን ላይ ጥቃት መፈጸማቸውን ተከትሎ ኢራን በምላሹ በፋርስ ባሕረ ሰላጤው አገራት ውስጥ የሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሰፈሮችን ዒላማ ያደረጉ ጥቃቶችን መፈጸሟን አስታውቃለች።

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ እንዳለው በዛሬው ጥቃት በባህሬን የሚገኘው አምስተኛው የአሜሪካ ባሕር ኃይል ምድብን፣ ኩዌት የሚገኘውን አሊ አል ሳሌም የአየር ኃይል ሰፈርን እና ዮርዳኖስ ውስጥ የሚገኘውን አል አዝራቅ የአየር ኃይል ሰፈርን በድሮን እና በሚሳዔሎች መትቷል።

    የዮርዳኖስ ጦር ኃይል ስለጥቃቱ ባወጣው መግለጫ የአየር መከላከያ ሥርዓቱ አምስት ሚሳዔሎችን አየር ላይ በመምታት ማክሸፉን እና በሰውም ሆነ በንብረት ላይ ጉዳት አለመድረሱን አስታውቋል።

    አሜሪካ ማክሰኞ ዕለት ለተመታባት ሄሊኮፕተር አጸፋ በደቡባዊ ኢራን የፈጸመችው ጥቃት የኮሚዩኒኬሽን ማማዎችን እና የውሃ ማከማቻ ግድቦችን ማውደሙን የኢራን አብዮታዊ ዘብ ገልጿል።

  16. ኔታንያሁ ለጠቅላይ ሚኒስትርነት ዳግም እንደሚወዳደሩ ፓርቲያቸው አስታወቀ

    ትራምፕ ቤንያሚን ኔታንያሁ ዳግም የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነው ለመወዳደር የሚችሉ እንደማይመስላቸው ቢገልጹም በዚህ ዓመት ለዳግም ምርጫ እንደሚወዳደሩ ፓርቲያቸው አስታወቀ።

    የኔቴንያሁ ሊኩድ ፓርቲ ባወጣው አጭር መግለጫ "በምርጫው ይሳተፋሉ፤ ከፈጣሪ ጋር ያሸንፋሉ" ሲል አስታውቋል።

    ምርጫው መቼ እንደሚካሄድ በይፋ ባይገለጽም በጥቅምት ወር እንደሚሆን ተገምቷል።

    ቀደም ሲል የኤቢሲ የዋሺንግተን ዘጋቢ ጆናታን ካርል በኤክስ ገጹ ላይ ትራምፕ ኔታንያሁ ስለመወዳደራቸው እርግጠኛ አለመሆናቸውን እንደነገሩት ጽፎ ነበር።

    “አላውቅም፤ በጣም አስደናቂ የሥልጣን ጊዜ ነበረው፤ መቀጠል ይፈልጋል?” ማለታቸውን ጋዜጠኛው በማኅበራዊ ድረ ገፁ ላይ አጋርቶ ነበር።

    እስራኤል የምታካሄደው ይህ ምርጫ የአገሪቱ ደኅንነት መሥሪያ ቤት ከፍተኛ ውድቀት ነው ከተባለው የመስከረም 26/2016 ዓ.ም. የሐማስ ጥቃት ወዲህ ሲካሄድ የመጀመሪያው ነው።

    ኔታንያሁ ወደ ሥልጣን በአውሮፓውያኑ 2022 ታኅሣሥ ወር ከመጡ ወዲህ ከፍተኛ መንገጫገጭ አጋጥሟቸዋል።

    በጋዛ፣ በሊባኖስ እና በኢራን ጦርነት ከመቀስቀሱ በፊት የፀረ መንግሥት ተቃውሞዎች ተካሄደውባቸዋል።

    የሕዝብ አስተያየት መስጫ መድረኮች አገሪቱን ለመምራት ከሌሎች ጋር ጥምረት የመሠረተው ፓርቲያቸው ያለው ተቀባይነት እየቀነስ መምጣቱን ያሳያሉ።

    ኔታንያሁ ከአሜሪካ ጋር በመሆን ኢራን ላይ ጦርነት ቢከፍቱም በቅርብ ጊዜ ግን ሁለቱ መሪዎች የተካረረ የሰልክ ምልልስ አድርገዋል።

    ሁለቱ መሪዎች አሁንም የቅርብ አጋር ቢሆኑም ትራምፕ እስራኤል በሊባኖስ ላይ የምትወስደውን ወታደራዊ እርምጃ እንድታቆም ይፈልጋሉ።

    ለዚህ ምንክያታቸው ደግሞ ከኢራን ጋር እያደረጉት ያለው ድርድር ነው።

    ዶናልድ ትራምፕ በተደጋጋሚ የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር የቀረበባቸው የሙስና ክስ እንዲነሳላቸው ሲጠይቁ ተሰምተዋል።

  17. የአሜሪካው ምክትል ፕሬዝዳንት ከኢራን ጋር በሳምንታት ወይም በመጪዎቹ ወራት ከስምምነት እንደሚደረስ ተናገሩ

    የአሜሪካው ምክትል ፕሬዝዳንት ጄ.ዲ ቫንስ አገራቸው ከቴህራን ጋር በምታደርገው ድርድር የኢራንን የኒውክሌር መረሃ ግብርን ጉዳይ “በዘለቄታው” የሚፈታ ስምምነት ላይ ለመድረስ መቃረቧን ተናገሩ።

    ሁለቱ አገራት ላለፉት ወራት አንዳቸው በሌላኛቸው ላይ ጥቃት እየፈጸሙ ጎን ለጎን ጦርነቱን ለማስቆም ድርድር እያደረጉ ቆይተው ነው አሁን ወደ መቋጫው መደረሳቸውን ምክትል ፕሬዝዳንቱ የተናገሩት።

    በድርድሩ ወቅት የኢራን የኒውክሌር ይዞታ ያላስማማ ቁልፍ ጉዳይ ሆኖ የቆየ ሲሆን፣ አሁን ቫንስ እንዳሉት ወደ መግባባት መቃረባቸውን እና በቀጣይ ሳምንታት ወይም ወራት ከስምምነት እንደሚደረስ ገልጸዋል።

    "በአሁኑ ጊዜ ከኢራን ጋር ለአሜሪካ ምጣኔ ሀብት ጥሩ የሆነው ስምምነት ላይ ለመድረስ እየተቃረብን እንደሆነ ይሰማኛል። ስምምነቱ የኢራን የኒውክሌር ጉዳይ ፕሬዝዳንት ትራምፕ ሥልጣን ላይ አስከሚቆዩበት ጊዜ ድረስ ብቻ የሚፈታ ሳይሆን በዘላቂነት አገሪቱ የኒውክሌር ጦር መሳሪያ እንዳይኖራት የሚያደርግ ነው” ሲሉ ምክትል ፕሬዝዳንት ቫንስ ለሲቢኤስ ቴሌቪዥን ተናግረዋል።

    ይህም የመንግሥታቸው የፖሊሲ ግብ መሆኑን የገለጹት ቫንስ “ያንን ግብ ለማሳካት በጣም የተቃረብን ይመስለኛል። ነገር ግን ሌሎች በርካታ የቀሩ ጉዳዮች አሉ። ለእነዚያም መቋጫ ለማበጀት ጥረታችንን እንቀጥላለን” ብለዋል።

    ምክትል ፕሬዝዳንቱ ጨምረውም ከኢራን ጋር በሚደረገው ድርድር በአሜሪካ ከሚካሄደው ወሳኙ የአጋማሽ ዘመን ምርጫ በፊት ከስምምነት እንደሚደረስ እርግጠኛ መሆናቸውን አመልክተዋል።

  18. ኢራን ሌሊቱን ለተፈጸመባት ጥቃት አጸፋ በፋርስ ባሕረ ሰላጤ የሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሰፈሮችን መታች

    አሜሪካ ተመትቶ ለወደቀው ሄሊኮፕተሯ አጸፋ በኢራን ላይ ጥቃት መፈጸሟን ተከትሎ በባሕረ ሰላጤው አገራት ውስጥ የሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሰፈሮችን ዒላማ ያደረጉ ጥቃቶችን መፈጸሙን የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ አስታወቀ።

    ሠራዊቱ ባወጣው መግለጫ ላይ እንዳመለከተው በቀጣናው የሚገኙ የአሜሪካ “አምስተኛው ምድብ ባሕር ኃይል” የራዳር ሥርዓትን እና ጦር ሰፈሮችን በበርካታ ድሮኖች መምታቱን አስታውቋል።

    የኢራን ቴሌቪዥን ጣቢያ እንደዘገበው የአገሪቱ ሠራዊት ጥቃቱን አሜሪካ በደቡባዊ ኢራን ውስጥ በሚኖሩ ዜጎች ላይ ለፈጸመችው “ጥቃት” የተሰጠ “የአጸፋ ምላሽ” በማለት በመግለጫው ላይ ጠቅሷል።

    የአሜሪካ ምንጮች ጥቃቱን በተመለከተ ባወጡት ዘገባ ኢራን በአራት ሚሳዔሎች እና በበርካታ ድሮኖች በባህሬን፣ በኩዌይት እና በዮርዳኖስ የሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሰፈሮች ላይ ጥቃት ፈጽማለች ብለዋል።

    ለኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ቅርብ የሆነው ታስኒም የዜና ወኪል እንደዘገበው ኢራን በዮርዳኖስ በሚገኝ የአሜሪካ ጦር ሰፈር ላይ ጥቃት ፈጽማለች። በዚህም ዋነኛ ዒላማ የነበረው እጅግ ዘመናዊ የሆኑት የአሜሪካ ኤፍ-35 ተዋጊ ጀቶች የሚቀመጡበት መጠለያ መሆኑን ዘቡን ጠቅሶ ዘግቧል።

    በተጨማሪም ፋርስ የተባለው የኢራን ዜና ወኪል አብዮታዊ ዘቡ በፋርስ ባሕረ ሰላጤው አካባቢ የሚገኙ "21 የአሜሪካ የአየር እና የባሕር ኃይል ጦር ሰፈሮች ዒላማ ተደርገዋል” ማለቱን ገልጿል።

  19. አሜሪካ ለተመታባት ሄሊኮፕተር አጸፋ በኢራን ላይ ጥቃት መፈጸሟን ሠራዊቷ አስታወቀ

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ቴህራን የአሜሪካ ሄሊኮፕተርን በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ መትታ ጥላለች በማለት ከከሰሱ በኋላ ሠራዊታቸው በኢራን ላይ ጥቃት ፈጸመ።

    የአሜሪካ ጦር ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም) እንዳስታወቀው ለተመታው አፓቼ ሄሊኮፕተር አጸፋ ማክሰኞ ሌሊት በኢራን ላይ ጥቃት መፈጸም ጀምሯል።

    ዕዙ "ዘመቻው በኢራን ለተፈጸመው ተቀባይነት የሌለው ጠብ አጫሪነት ተመጣጣኝ ምላሽ ነው" ያለ ሲሆን፣ በባሕረ ሰላጤው ዳርቻዎች እና በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ ፍንዳታዎች መሰማታቸው ተዘግቧል።

    የተመታው ሄሊኮፕተር ሁለት አብራሪዎች በአሜሪካ የባሕር ላይ ድሮን አማካይነት መትረፋቸው እና ምንም ጉዳት እንዳልደረሰባቸው ፕሬዝዳንት ትራምፕ ገልጸዋል።

    ኢራን ሄሊኮፕተሩን በድሮን መምታቷን የአሜሪካ ባለሥልጣናት የተናገሩ ሲሆን፣ ነገር ግን ጥቃቱ ሆን ተብሎ የተፈጸመ ስለመሆኑ ግልጽ አይደለም ብለዋል።

    ክስተቱ ማጋጠሙ የኢራን መገናኛ ብዙኃን ቢዘገብም የአገሪቱ መንግሥት ግን ተመትቶ ለወደቀው የአሜሪካ ሄሊኮፕተር ኃላፊነቱን አለመውሰዳቸውን ሜህር የተባለው የኢራን ዜና አገልግሎት ዘግቧል።

    የአሜሪካው የዜና ድረ ገጽ አክሲዮስ እንደዘገበው በጥቃቱ ዒላማ የሆኑት የኢራን የአየር መከላከያ እና የራዳር ሥርዓቶች ናቸው። የኢራን መንግሥት መገናኛ ብዙኃን ፍንዳታዎች በፋርስ ባሕረ ሰላጤው አካባቢ በሚገኙ የአገሪቱ ግዛቶች ላይ ፍንዳታዎች መሰማታቸውን ዘግበዋል።

    ከኤቢሲ ኒውስ ጋር በስልክ ቃለ ምልልስ ያደረጉት ፕሬዝዳንት ትራምፕ ጦራቸው ለፈጸመው ጥቃት ኢራንን ተጠያቂ አድርገው ከስሰዋታል።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ ጥቃቱን ተከትሎ በኤክስ ገጻቸው ላይ “አሜሪካ በጦር ሜዳው ላይ ሽንፈት ቢገጥማትም ቁርጠኝነታችንን እየተፈታተነች ነው” በማለት አገራቸውለሚፈጸምባት ጥቃት አጸፋ እንደምትሰጥ ዝተዋል።

    ሚኒስትሩ ጨምረውም "ሰላም የምትፈልጉ ከሆነ ቀጣናውን ለቅቃቸው ውጡ” በማለት ለአሜሪካ መልዕክት አስተላልፈዋል።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ተመትቶ የወደቀውን የሠራዊታቸውን አፓቼ ሄሊኮፕተርን በተመለከተ አስተያየት ከመስጠታቸው ቀደም ብሎ የኢራን ዋነኛ ተደራዳሪ እና የአገሪቱ ፓርላማ አፈ ጉባኤ ሞሐመድ ባጊር ጋሊባፍ በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ መልዕክት አስተላልፈው ነበር።

    "እኛ የዲፕሎማሲ ቋንቋን ነው የምንርጠው፣ ነገር ግን ሌሎች ቋንቋዎችንም አቀላጥፈን እንናገራለን። ቃላችሁን የማታከብሩ ከሆነ በደምብ ወደምንችለው የንግግር መድረክ ፊታችንን እናዞራለን” በማለት አሜሪካን በምትፈልገው መልኩ እንደሚያስተናግዷት አስጠንቅቀዋል።

  20. ፈረንሳይ የእስራኤል ፋይናንስ ሚኒስትር ወደ አገሯ እንዳይገቡ አገደች

    ፈረንሳይ ማክሰኞ ዕለት ቀኝ አክራሪው የእስራኤል የፋይናንስ ሚኒስትር ባዛሌል ስሞትሪች ወደ አገሯ እንዳይገቡ አግዳ ጋዛን “ዳግም ቅኝ የመግዛት” አጀንዳን ያራምዳሉ ስትል ኮነነች።

    የፈረንሳይ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማዕቀቡ የተጣለው ከሌሎች አገራት ጋር በመተባበር መሆኑን ገልጸው በፍልስጤማውያን ሰፋሪዎች ላይ በሚደርስ ጫና የተነሳ እገዳው መጣሉን ገልጸዋል።

    ፈረንሳይ ማዕቀቡን የጣለችው ከብሪታኒያ፣ ካናዳ፣ አውስትራሊያ፣ ኖርዌይ እና ኒው ዚላንድ ጋር በመተባባር ነው።

    “የሰፈራ እንቅስቃሴዎችን እና በዌስት ባንክ ግጭትን በማቀጣጠል ረገድ ተጠያቂ የሚሆኑ” አካላት ላይ ማዕቀቡ መጣሉን የፈረንሳይ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዣን ኖኤል ባሮት በኤክስ ገጻቸው ላይ ጽፈዋል።

    ሚኒስትሩ፣ ስሞትሪች “ዌስት ባንክን ወደ እስራኤል መጠቅለልን በይፋ ይደግፋሉ፣ በዌስት ባንክ ተጨማሪ ሰፈራዎች እንዲካሄዱ በይፋ ይንቀሳቀሳሉ” ሲሉ ኮንነዋቸዋል።

    አክለውም “ጋዛን ዳግም ቅኝ መግዛት፣ የፍልስጤም ባለሥልጣን ኢኮኖሚያዊ ድቀት እንዲገጥመው፣ እንዲሁም በፍልስጤም ሕዝብ ላይ ጎጂ ተግባራትን “ በመፈጸም ከስሰዋቸዋል።

    ስሞትሪች ወደ ፈረንሳይ እንዳይገቡ ከተከለከሉ የእስራኤል ባለሥልጣናት መካከል ሁለተኛው ናቸው።

    ከአዚህ ቀደም የብሔራዊ ደህንነት ሚኒስትሩ ኢታማር ቤን ግቪር ወደ ፈረንሳይ እንዳይገቡ ታግደዋል።

    ፈረንሳይ አራት የሰፋሪዎች ድርጅት መሪዎችን እና 21 አመጸኛ ሰፋሪዎችን ላይ እገዳ ትላለች።