ፔንታጎን የእስራኤል ስለላ እንደሚያሳስበው ተገለጸ
ከቅርብ ሳምንታት ወዲህ ፔንታጎን እስራኤል ከፍተኛ ልዑኮችን ጨምሮ የአሜሪካ ባለሥልጣናትን መሰለሏን በመጥቀስ “አሳሳቢ” መሆኑን ገለጸ።
ሁለቱ አገራት ኢራን ላይ በጥምረት ጦርነት ቢከፍቱም በኋላ ላይ በሊባኖስ የተነሳ በመካከላቸው ውጥረት ሰፍኗል።
ለኤንቢሲ መረጃውን ያቀበሉ የአሜሪካ ባለሥልጣናት ፔንታጎን እስራኤል ከፍተኛ የአገሪቱን ባለሥልጣናት በቀጣናው ግጭት ዙሪያ የሚያደረጉትን ክርክሮችን ለማወቅ በሚል ትሰልላለች ብሎ እንደሚያምን ተናግረዋል።
እንደ ዘገባው ከሆነ የፔንታጎን የመከላከያ ደህንነት ኤጀንሲ እስራኤል በቅርብ ሳምንታት ያደረገችውን ስለላዎች በሚመለከት ደረጃውን “አሳሳቢ” ወደሚል ከፍ ማድረጉን በውስጥ የተለዋወጧቸው መልዕክቶች ላይ አስፍሯል።
አንድ የአሜሪካ ባለሥልጣን ፔንታጎን የእስራኤልን ስለላ በሚመለከት ባለ ሰባት ገጽ ሪፖርት ማዘጋጀቱን እና አሳሳቢ ያላቸውን ክስተቶች ዘርዝሯል ብለዋል።
ባለሥልጣናቱ የደህንነት መረጃዎችን የማሰባሰብ ደረጃው በሁለት ወዳጅ አገራት መካከል ከሚጠበቀው ያለፈ መሆኑን ጠቅሰዋል።
ነገር ግን አንድ የተናጠል ክስተት የስጋት ደረጃውን ከፍ ያድርገው ወይም ተከታታይ እርምጃዎች ግልጽ አላደረጉም።
እስራኤል የአሜሪካን ልዩ መልዕክተኛ ስቲቭ ዊትኮፍ መሰለሏን ኒውዮርክ ታይምስ ቅዳሜ ዕለት የአገሪቱን ባለሥልጣናት ጠቅሶ ዘግቧል።
ዊትኮፍ ከኢራን ጋር በሚካሄደው፣ እስራኤል ከሐማስ ጋር እንደሁም ዩክሬን እና ሩሲያ ጋር በምታደርጋቸው ድርድሮች ላይ ይሳተፋሉ።
የመገናኛ ብዙኃኑ የደህንነት ሪፖርቶችን በመጥቀስ የአሜሪካ ባለሥልጣናት እስራኤል በከፍተኛ የመከላከያ ባለሥልጣናት በተለይ ኢልብሪጅ ኮልቢ እና ምክትላቸው ማይክል ፒ ዲሞኖ ላይ የምታካሄደውን ስለላ ማጠናከሯ እንዳሳሰባቸው ዘግበዋል።
ስለላው እስራኤል የኮሙኑኬሽን መስመራቸውን መጥለፍ ወይንም በአሜሪካ የፖሊሲ ውይይት ላይ በተለይ ከኢራን ጋር በሚደረገው ድርድር መረጃዎችን መሰብሰብ እንደሚሆን ተናግረዋል።
ታይምስ የጠቀሳቸው አንድ ከፍተኛ ባለሥልጣን ትራምፕ ባለፈው ዓመት ወደ ሥልጣን ከመጡ ወዲህ እስራኤል በአሜሪካ ባለስልጣናት ላይ የምታደርገው የተጠናከረ ስለላ “ያልተጠበቀ ነው” ብለዋል።
ኒውዮርክ ታይምስም ሆነ ኤንቢሲ ከፔንታጎን ምላሽ ለማግኘት ያደረጉት ጥረት አለመሳካቱን ጠቅሰዋል።