ሐረር ውስጥ ለ12 ዓመታት ለመውለድ የሞከረች እናት በአንድ ጊዜ አምስት ሕፃናትን ተገላገለች

የፎቶው ባለመብት, Hiwot Fana Specialised Hospital
ለ12 ዓመታት ልጅ ለመውለድ የሞከረች የሐረሪ ክልል ነዋሪ በአንድ ጊዜ አምስት ልጆችን መገላገሏ ተገለጸ።
በድሪያ አደም የተባለችው እናት እሷና ባለቤቷ "በአንድ ጊዜ አምስት ልጆች ስላገኙ እጅግ እንደተደሰቱ" ተናግራለች።
የ35 ዓመቷ በድሪያ በሕይወት ፋና ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል አራት ወንዶችን እና አንዲት ሴት ልጆችን በሠላም መገላገሏን ሆስፒታሉ ተናግሯል።
"ደስታዬን በቃላት መግለጽ አልችልም" የምትለው በድሪያ፤ ልጅ የማግኘት ጸሎቷ ምላሽ እስኪያገኝ ድረስ "ድብርት እና ህመም ውስጥ" እንደነበረች አስታውሳለች።
የሆስፒታሉ የሕክምና ዳይሬክተር ዶ/ር መሐመድ ኑር አብዱላሂ፤ እናትየውና ጨቅላ ህጻናቱ በሆስፒታሉ የሕክምና እንክብካቤ እየተደረገላቸው እንደሚቆዩ ተናግረዋል። ህጻናቱ ከ1.3 እስከ 1.4 ኪ.ግ ይመዝናሉ ተብሏል።
ከአንድ ኪሎ ግራም በላይ የሚመዝኑ ሕፃናት በህይወት የመቆየት እና የጤናማ እድገት የማሳየት ዕድላቸው ከፍተኛ እንደሆነ ለቢቢሲ ተናግረዋል።
በድሪያ በተፈጥሯ መንገድ መጸነሷን ዶክተሩ ለቢቢሲ ገልጸዋል። በተፈጥሮ አምስት ልጆችን የመፀነስ ዕድሉ ከ55 ሚሊዮን ሰዎች ውስጥ አንድ ጊዜ የሚያጋጥም ነው።

የፎቶው ባለመብት, Hiwot Fana Specialised Hospital
በድሪያ ማክሰኞ ምሽት ልጇቿን በቀዶ ሕክምና መውለዷን ዶ/ር መሐመድ ተናግረዋል።
"በእርግዝናዋ ወቅት መደበኛ የህክምና እንክብካቤ ስታገኝ ነበር። ከአንድ በላይ ልጆች እንደፀነሰች ተነግሯታል። ሙሉ የህክምና እርዳታ አግኝታለች" ያሉት ዶ/ር መሐመድ፤ "ደስተኛ" እንደሆነች ገልጸዋል።
በድሪያ በመጀመሪያ ላይ አራት ህፃናትን እንዳረገዘች ተነግሯት ነበረ ቢሆንም ግን ስትወልድ አምስት መሆናቸውን ገልጻለች።
"ለአንድ ልጅ ብቻ ጸለይኩ፣ አላህም አምስት ሰጠኝ" ስትል ልጅ ለማግኘት "ረጅም ጊዜ በተጠባበቀችበት" ወቅት ምን እንደተሰማት ትናገራለች።
ባለቤቷ ከሌላ ጋብቻ ልጅ እንደወለደ እና ልጁም ከእነሱ ጋር እንደሚኖር ገልጻለች።
"[ሌላኛው ልጅ] ስላለን በቂ እንደሆነ እና መጨነቅ እንደሌለብኝ ይነግረኝ ነበር። ነገር ግን መንደሩ በሙሉ ልጅ መውለድ አለመቻሌን ሲጠራጠር በውስጤ እየተሰቃየሁ ነበር" ብላለች።
"ባለፈው ጊዜ ያሳለፍኩት ነገር እንደ ሩቅ ህልም ይሰማኛል፤ ማስታወስ እንኳን አልፈልግም" ስትል አክላለች።
"ለ12 ዓመታትን በህመም አሳልፌያለሁ፤ ራሴን ደብቄያለሁ። ልጆች ለማግኘት ያለማቋረጥ እጸልይ ነበር በመጨረሻም አላህ ሰምቶኛል።"
ገበሬ እንደሆነች ገልጻ ቤተሰቧን እንዴት እንደምታስተዳደር እርግጠኛ እንዳልሆነች ተናግራለች። "ነገር ግን አላህ በማህበረሰቤ እና በመንግስት በኩል ድጋፍ እንደሚያሰጠኝ አምናለሁ።"
አምስቱ ልጆች ናኢፍ፣ አማር፣ ሙንዚር፣ ናዚራ እና አንሳር የሚል ስም ወጥቶላቸዋል














