የሶማሊያው ፕሬዝዳንት የሥልጣን ዘመናቸው ማብቃቱን ተከትሎ የተፈጠረው አጣብቂኝ

የሶማሊያ ተቃዋሚዎች የምርጫ ማሻሻያውን በመቃወም ሠልፍ ጠርተዋል

የፎቶው ባለመብት, Reuters

የምስሉ መግለጫ, የሶማሊያ ተቃዋሚዎች የምርጫ ማሻሻያውን በመቃወም ሠልፍ ጠርተዋል
ታትሟል
የንባብ ጊዜ: 4 ደቂቃ

የሶማሊያ ፕሬዝዳንት ሐሰን ሼክ ሞሐሙድ የሥልጣን ዘመናቸውን ለማራዘም ያደረጉትን ሙከራ ተከትሎ ከዚህ ቀደም አጋጥሟቸው አያውቅም የተባለ ከፍተኛ ተቃውሞ እየተጋፈጡ ነው።

በአገሪቱ ሕገ መንግሥት መሠረት የፕሬዝዳንቱ የሥልጣን ዘመን የሚያበቃው አርብ ግንቦት 7/2018 ዓ.ም. ነው።

ፕሬዝዳንቱ በቅርቡ የራሳቸውን እና የፓርላማውን ሥልጣን ከአራት ወደ አምስት ዓመት ለማራዘም እና እስከ ሚቀጥለው ዓመት ምርጫውን ለማራዘም የሕገ መንግሥት ማሻሻያ ለማድረግ ጥረት ካደረጉ በኋላ ውጥረት ጨምሯል።

ተቃዋሚዎች አደባባይ ወጥተው ድምጻቸውን ሲያሰሙ ቢያንሰ ሁለት ሰዎች ከተገደሉ እና በርካቶች ከተጎዱ በኋላ መንግሥት በአገሪቱ ዋና ከተማ ሞቃዲሹ ግንቦት 3/2018 ዓ.ም. የድጋፍ ሠልፎችን አካሄዷል።

የደኅንነት ኃይሎች ተቃዋሚዎች ተጨማሪ ሠልፎች እንዳያካሄዱ ለመከላከል በመሪዎቻቸው መኖሪያ አካባቢ ተሰማርተዋል።

ዋነኛው የተቃዋሚ ጥምረት የሆነው እና የቀድሞውን ፕሬዝዳንት ሻሪፍ ሼክ አህመድን እና በርካታ ጠቅላይ ሚኒስትሮችን፣ የፑንትላንድ እና የጁባላንድ ግዛት መሪዎችን የያዘው 'ሶማሊ ፊውቸር ካውንስል' ፕሬዝዳንቱ ሕገ መንግሥታዊ የሥልጣን ገደባቸው ካበቃ በኋላ ቅቡልነት አይኖራቸውም ሲል መግለጫ አውጥቷል።

በመንግሥት እና በተቃዋሚዎች መካከል ሊደረግ ታስቦ የነበረው ተከታታይ ንግግር ሳይሳካ ቀርቷል።

ተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎች ፕሬዝዳንቱን ሥልጣንን ይጠቀልላሉ በማለት የሚወነጅሏቸው ሲሆን፣ ድርጊታቸው ወደ አዲስ አለመረጋጋት እና ግጭት እንደሚገፋት አስጠንቅቀዋል።

የቀድሞ ፕሬዝዳንት ሞሐመድ አብዱላሂ ፎርማጆ ሁሉም የፖለቲካ ባለድርሻ አካላት መካከል የአሁኑ ፕሬዝዳንት የሥልጣን ጊዜ ሳያበቃ አካታች የምርጫ ሂደት እንዲደረስ ጥሪ አቅርበዋል።

የፖለቲካ ውጥረቱን የቀሰቀሰው ምንድን ነው?

በመጋቢት ወር ፓርላማው የፕሬዝዳንቱን የሥልጣን ዘመን የሚያራዝም እና ምርጫን የሚያዘገይ የሕገ መንግሥት ማሻሻያዎችን አጽድቋል። ይህ ግን በተቃዋሚ ቡድኖች ሰፊ ትችት እንዲቀሰቀስ አድርጓል።

የቀድሞው የደቡብ ምዕራብ ግዛት ፕሬዝዳንት አብዲያስ ላፍታጋሬ በፌደራል መንግሥቱ ወታደሮች ከተነሱ ከቀናት በኋላ ጠቅላይ ሚኒስትር ሃምዛ አብዲ ባሬ የግዛቲቱ ጊዜያዊ አስተዳዳሪ ሆነው ሲሾሙ ውጥረቱ የበለጠ ተባብሷል።

የፌደራል መንግሥቱ በደቡብ ምዕራብ ቀጥተኛ ምርጫ እንዲያካሄድ ያስተላለፈው ውሳኔ ጋር በተጣጣመ መልኩ በጋልሙዱግ እና ሒርሸበሌ ተመሳሳይ እርምጃ ለመውሰድ በመወሰኑ በሞቃዲሹ እና በተቃዋሚ መሪዎች መካከል አለመግባባት ተፈጥሯል።

የሞሐሙድ ተቺዎች አንድ ሰው አንድ ድምጽ የሚለው ዕቅድ አለመረጋጋት፣ ውስን የሆነ የማዕከላዊ መንግሥት ቁጥጥር እንዲሁም ያልተፈቱ ሕገ መንግሥታዊ ግጭቶች ባሉበት ከአውሮፓውያኑ 2000 ጀምሮ በሥራ ላይ ያለውን በጎሳ ላይ የተመሠረተውን የምርጫ ሥርዓት ለመተው አስቸጋሪ ያደርገዋል ሲሉ ይከራከራሉ።

መንግሥት በሞቃዲሹ የያዘው የማፍረስ ዘመቻ ተቃዋሚዎች "የሕዝብ መሬትን ለግል ፍላጎት እየቸበቸቡ ነው" በማለታቸው ውጥረትን ካባባሱ ጉዳዮች መካከል አንዱ ሆኗል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ በዋና ከተማዋ የጋዜጠኞች እና የአክቲቪስቶች መታሰር በአገሪቱ እያደገ የመጣውን የሚዲያ ዕቀባ እና የፖለቲካ አለመግባባት እንዲያድግ አድርጓል።

ሶማሊያ ቀጥተኛ ምርጫ ለመጨረሻ ጊዜ ያካሄደችው እአአ በ1969 ነው

የፎቶው ባለመብት, radio mogadishu

የምስሉ መግለጫ, ሶማሊያ ቀጥተኛ ምርጫ ለመጨረሻ ጊዜ ያካሄደችው እአአ በ1969 ነው

የአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ውጥረቱን እንዴት ዘገቡት?

Skip podcast promotion and continue reading
የቢቢሲ አማርኛ ዩቲዩብ ቻናል

ዜና፣ ትንታኔ እና ታሪኮችን በምሥል እና በድምጽ ለማግኘት

ይህንን በመጫን ሰብስክራይብ ያድርጉ

End of podcast promotion

የአገር ውስጥ መገናኛ ብዙኃን በአሜሪካ አደራዳሪነት በፌደራል መንግሥቱ እና በተቃዋሚዎች መካከል ግንቦት 5/2018 ዓ.ም. የተደረገውን ውይይት ሰፊ ሽፋን ሰጥተውታል።

የመንግሥት ልዑካን በፕሬዝዳንት ሞሐሙድ እና ቀዳማይ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ሳላህ አህመድ ጃማን የተወከለ ሲሆን፣ ተቃዋሚዎች ደግሞ የተወከሉት በቀድሞው ፕሬዝዳንት ሻሪፍ ሼክ አህመድ እና በፑንትላንድ መሪ ሳኢድ አብዱላሂ ዴኒ ነው።

በግል ባለቤትነት የተያዘው ሶማሊ ጋርዲያን ድረ ገጽ ዳግም የሚቀሰቀስ አለመረጋጋት ለዓመታት የተደረገውን አገር የመገንባት ጥረት እንዳይቀለብሰው አስጠንቅቋል።

አክሎም አልሸባብ ላይ የሚደረገውን ወታደራዊ ዘመቻም አደጋ ላይ የሚጥል መሆኑን ጠቅሷል።

ድረገጹ የተቃዋሚዎች የመጀመሪያ ጥያቄ በቁጥጥር ሥር የዋሉ ደጋፊዎቻቸው እንዲለቀቁ የሚጠይቅ ነው ሲል ዘግቧል።

የቀድሞው ሚኒስትር አብዲርሃማን ባድዮው "ዓለም አቀፍ አሸማጋዮች ጣልቃ የገቡት ዘግይተው በመሆኑ በሁለቱም ወገን ላይ የሚያደርጉት ጫና እዚህ ግባ የሚባል አይደለም" ብለዋል።

ሙስታቅባል የተባለ ሌላ የግል መገናኛ ብዙኃን ደግሞ ሁለቱም ተደራዳሪ ወገኖች በምርጫ እና ሕገ መንግሥታዊ ማሻሻያዎች ላይ ባለመስማማታቸው ግንቦት 6 ድርድራቸው ይቀጥላል ብሎ ነበር።

ጋሮዌ ኦንላየን በበኩሉ ስማቸውን ያተገለጸ ምንጮች ጠቅሶ የፌደራል መንግሥቱ ቴክኒካል ኮሚቴ እንዲቋቋም እየገፉ ነው ሲል ዘግቧል።

ተቃዋሚዎች ግን ይህንን ዕቅድ ውድቅ አድርገው "የግንቦት 7 ቀነ ገደብ ለማለፍ የመጣ ብልሃት ነው" ሲሉ መተቸታቸውን ዘግቧል።

የአልሸባብ ደጋፊ የሆነው አል ፉርቃን በበኩሉ "በመንግሥት እና በተቃዋሚዎች መካከል ያለ አለመተማመንን" አጉልቶ አቅርቦ፤ ኤምባሲዎች በሚገኙበት እና በዓለም አቀፍ ወታደሮች ከፍተኛ ጥበቃ በሚካሄድለት ሃላኔ ካምፕ የሚካሄደው ድርድር ፍሬ አለማፍራቱን ዘግቧል።

ሶማሊ ሜሞ የተሰኘው ሌላ የአልሸባብ ደጋፊ የሆነ መገናኛ ብዙኃን "በምዕራባውያን የሚመራው እና በሞቃዲሹ የሚካሄደው ድርድር ተጨናግፏል" ሲል ዘግቧል።

በሚያዝያ ወር ካብ የተሰኘው ቴሌቪዝን ጣቢያ ተቃዋሚዎች የውጭ አደራዳሪዎች እንዲመጡ ጥሪ እየቀረቡ በነበረበት ወቅት የቱርክ አምባሳደርን በሶማሊያ ጉዳይ ጣልቃ እንዳይገቡ ማስጠንቀቃቸውን ዘግቦ ነበር።

ጣቢያው በስም ያልጠቀሳቸውን የውይይቱ ተሳታፊ ተጠቅሞ "ቱርክ ከሶማሊያ የውስጥ ጉዳይ እንድትርቅ እንዲሁም ከፕሬዝዳንት ሞሐሙድ አስተዳደር ጋር የተፈራረመችውን ሕጋዊ ያልሆነ የነዳጅ ዘይት ስምምነት እንድታቆም ተነግሯታል" ሲል ዘግቧል።

የፖለቲካ ተንታኞች የፌደራል መንግሥቱ በተለይ የሥልጣን ዘመኑ እንዲራዘምለት የሚጠይቅ ከሆነ ከድርድሩ ውጤት ይጠበቃል ብለው ተስፋ አያደርጉም።

ቀጥሎ ምን ሊሆን ይችላል?

የተቃዋሚ መሪዎች ፕሬዝዳንት ሞሐሙድ የሥልጣን ጊዜያቸው ካበቃ "እንደ አገሪቱ ፕሬዝዳንት ተቀባይነት አይኖራቸውም" በማለት ነገ ቅዳሜ 8/2018 ዓ.ም. የተቃውሞ ሠልፍ ጠርተዋል።

በሚቀጥሉት ቀናት የፖለቲካ ውይይት እንዲካሄድ እንዲሁም ሦስተኛ ወገን ጣልቃ እንዲገባ ጥረት ይደረጋል ተብሎ ይጠበቃል።

ከፌደራል መንግሥቱ ጋር ግንኙነታቸውን ያቋረጡት ፑንትላንድ እና ጁባላንድ ስምምነት ላይ የማይደረስ ከሆነ በጋሮዌ እና ኪስማዩ የተናጠል ምርጫ እንደሚያካሄዱ አስጠንቅቀዋል።

የአገሪቱ መከላከያ ሚኒስትር አህመድ ሞአሊም ፊቂ የተቃውሞ ሠልፍ ያዘጋጁትን አካላት "በውጭ ኃይሎች የሚደገፉ" ሲሉ ከኮነኗቸው በኋላ ተቃዋሚዎች የውጭ ድጋፍን ሊጠይቁ ይችላሉ ተብሎ ተሰግቷል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ አስተያየት ሰጪዎች በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች ተሰማርተው የነበሩ ወታደሮች በማዕከላዊ መንግሥቱ ላይ ውጥረት በማየሉ ብቻ ወደ ሞቃዲሹ እንዲመጡ መደረጋቸው አልሸባብ ላይ ተጀምሮ የነበረውን ዘመቻ ያዳክመዋል ሲሉ ተናግረዋል ።

ተንታኞች አልሸባብ ይህንን የፖለቲካ አለመረጋጋት ተጠቅሞ ግዛቱን ሊያስፋፋ ይችላል ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

ሶማሊያ በአለመረጋጋት ውስጥ ልትቆይ የምትችል ሲሆን፣ የሕገ መንግሥት ማሻሻያ እና የሥልጣን ማራዘም የፖለቲካ ውይይቱን ተቆጣጥሮት ይቆያል።

ከዚህ ቀደም ከምርጫ ጋር የተያያዙ አለመግባባቶች በጸጥታ አባላት እና ተቃዋሚዎችንን በሚደግፉ አንጃዎች መካከል በመሣሪያ የታገዘ ግጭት ቀስቅሶ ነበር።