ቀጥታ, ኢራን ከታገደባት ሀብት ውስጥ ስድስት ቢሊዮን ዶላር ሊለቀቅላት እንደሆነ ገለጸች

ኢራን እንዳይንቀሳቀስ ከታገደባት 12 ቢሊዮን ዶላር ውስጥ ግማሹ ሊለቀቅ መሆኑን የአገሪቱ ፕሬዝዳንት መሱድ ፔዜሽኪያን ተናገሩ። አሜሪካ እና ኢራን አራት ወራት ያለፈውን ጦርነት ለመቋጨት በተፈራረሙት የመግባቢያ ስምምነት ላይ ከሰፈሩ ጉዳዮች መከካል የኢራን የታገደ ሀብት አንዱ ነው።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. በጋና በተከሰተ የጎርፍ አደጋ ቢያንስ 13 ሰዎች ሞቱ

    በጋና መዲና አክራ በተከሰተ የጎርፍ አደጋ ሳቢያ ቢያንስ 13 ሰዎች መሞታቸውን የአገሪቱ የእሳት አደጋ መከላከያ መሥሪያ ቤት አስታወቀ።

    በቀጣይም ከአገሪቱ ምሥራቃዊ ክፍል መነሻውን ያደረገ አውሎ ንፋስ እና ዝናብ ሊኖር ስለሚችል ዜጎች ከቤት እንዳይወጡ ወይም ከፍ ያለ ሥፍራ ላይ እንዲሆኑ ማሳሰቢያ ተሰጥቷል።

    ካለፈው እሑድ ዝናብ የተከማቸ ውሃ መጠኑ እየቀነሰ ቢመጣም የሟቾች ቁጥር ሊጨምር እንደሚችል ተገልጿል።

    በተለይም ዝቅተኛ አካባቢዎች ለአደጋ ተጋላጭ ሆነዋል።

    በማኅበራዊ ሚዲያ የታዩ ተንቀሳቃሽ ምሥሎች ቤቶች እና ተሽከርካሪዎች በጎርፍ ተውጠው ያሳያሉ፤ ሕንጻዎች ላይም ጉዳት ደርሷል።

    በጎርፍ ጉዳት በደረሰባቸው አካባቢዎች ፖሊስ እና የእሳት አደጋ ተከላካዮችን ጨምሮ የድንገተኛ አደጋ ሠራተኞች ተሰማርተዋል።

    የጋና የአገር ውስጥ ሚኒስቴር እንዳለው ያለውን ሁኔታ እንዲከታተሉ እና የሰዎችን ሕይወት እንዲሁም ንብረት እንዲያድኑ ሠራተኞቹ ተሰማርተዋል።

    እስካሁን 470 ሰዎችን ማትረፍ እንተቻለ ተገልጿል።

    በጎርፉ ምክንያት በአክራ የሚገኝ የፕላስቲክ ፋብሪካ ውስጥ እሳት ተነስቷል።

  2. ዋትስአፕ ስልክ ቁጥር ሳይታይ በ‘ዩዘርኔም’ ብቻ መነጋገርን ሊፈቅድ ነው

    የመልክዕክት መለዋወጫ መተግበሪያ የሆነው ዋትስአፕ፤ ተጠቃሚዎች ‘ዩዘርኔም’ ብቻ በመለዋወጥ ቁጥራቸውን ሳይታወቅ ከሰዎች ጋር እንዲነጋገሩ ሊፈቅድ ነው።

    በዓለም አቀፍ ደረጃ ሦስት ቢሊዮን ተጠቃሚዎች ያሉት ዋትስአፕ፤ ይህ አሠራር በሚቀጥሉት ጥቂት ወራት ውስጥ ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ እንደሚሆን ገልጿል።

    ከዚህ ሳምንት ጀምሮ ግን ተጠቃሚዎች መለያ የሚሆናቸውን ‘ዩዘርኔም’ እንዲመርጡ ፈቅዷል። ይህንን መለያ ማስቀመጥ ግዴታ እንዳይሆን ተነግሯል።

    ተቋሙ እንደገለጸው፤ ተጠቃሚዎች ባሻቸው ጊዜ ‘ዩዘርኔሙን’ ማጥፋት ወይም መቀየር ይችለሉ።

    አሠራሩ ተግባራዊ መሆን ሲጀምር የዋትስአፕ ተጠቃሚዎች ‘ዩዘርኔም’ ብቻ በመለዋወጥ ከሰዎች ጋር መነጋገር ይችላሉ። የማይፈለጉ መልዕክቶችን ‘ብሎክ’ የማድረጊያ አማራጭ አሁንም ቢሆን ይቀጥላል።

    ተጠቃሚዎች የሚመርጡት ስም ከ35 ፊደላት ያነሰ መሆን አለበት። እጅግ ታዋቂ የሆኑ ሰዎችን ስም ግን ሌሎች ተጠቃሚዎች እንዲጠቀሙበት አይፈቀድም።

  3. በደቡብ አፍሪካ ፀረ ስደተኞች ተቃውሞ ምክንያት የፀጥታ ኃይሎች ከፍተኛ መጠን ተሰማሩ

    ዛሬ ማክሰኞ በደቡብ አፍሪካ የተለያዩ ከተሞች የሚደረገው ፀረ ስደተኞች ተቃውሞ ወደ አመጽ ሊያመራ ይችላል በሚል ስጋት በመላ አገሪቱ በርካታ የፖሊስ አባላት ተሰማርተዋል።

    የተቃውሞ ሰልፉ የሚካሄደው፤ ፀረ ስደተኛ የሆኑ ቡድኖች ሕጋዊ ሰነድ የሌላቸው የውጭ አገር ዜጎች አገሪቱን ለቅቀው እንዲወጡ ያስቀመጡት ይፋዊ ያልሆነ ቀነ ገደብ ዛሬ መጠናቀቁን ተከትሎ ነው።

    ተቃውሞ ሊካሄድ ከታቀደባቸው ከተሞች አንዷ የሆነችው ጆሃንስበርግ ባልተለመደ ሁኔታ ፀጥታ ነግሶባታል።

    ሰልፍ በሚካሄድባቸው ጎዳናዎች የሚገኙ መደብሮች ተዘግተዋል። የፖሊስ አባላት በከተማዋ ዋና ዋና መንገዶች ላይ ይታያሉ።

    ጆሃንስበርግ ውስጥ ከሚገኙ ትልቅ ስፍራዎች አንዱ በሆነው ሶዌቶ ውስጥ የውጭ አገር ዜጋን መደብር ዘርፈዋል የተባሉ አምስ ሰዎች በቁጥጥር ስር እንደዋሉ ፖሊስ አስታውቋል።

    ኩዋዙሉ ናታል ግዛት ውስጥ ደግሞ ሱቅ ሰብረው በመግባት የተወነጀሉ አምስት ሰዎች ታስረዋል። የግዛቱ ዋና ከተማ በሆነችው ደርባን ውስጥ በርካታ የንግድ ማዕከላት ተዘግተዋል።

    የደቡብ አፍሪካ ፕሬዝዳንት ሲሪል ራማፎሳ ሰልፈኞች በሰላማዊ እና ኃላፊነት በተሞላበት መልኩ እንዲንቀሳቀሱ በተደጋጋሚ አስጠንቅቀዋል።

  4. የኢራኑ ጠቅላይ መሪ በድርድሮች ውስጥ ያልተቋረጠ ተሳትፎ እንደነበራቸው ተነገረ

    ኢራን ከአሜሪካ ጋር እየተደረጉ ያሉ ድርድሮች በመንግሥት ፖሊሲዎች ላይ ተመሥርተው በጠቅላይ መሪው ሞጅታባ ኻሜኒ ሙሉ ተሳትፎ እየተካሄደ መሆኑን ፕሬዝዳንት ፔዜሽኪያን ተገናሩ።

    ፕሬዝዳንቱ ቆም በተባለችው ከተማ ውስጥ ከሃይማኖት መምህራን ጋር ባደረጉት ስብሰባ፤ ከአሜሪካ ጋር የሚደረገውን ጦርነት ለማስቆም የተደረሰው ስምምነት ለኢራን “ዲፕሎማሲያዊ ድል” ነው ብለዋል።

    ጨምረውም አንዳንድ ዘገባዎች በኢራን መሪዎች መካከል ልዩነት እንዳለ አስመስለው ማቅረባቸውን ተችተው “የአገሪቱን የአቋም አንድነት” ለማስጠበቅ ሲባል ምላሽ ከመስጠት መቆጠባቸውን አመልክተዋል።

    ኢራን እና አሜሪካ የመግባቢያ ስምምነቱን ከፈረሙ በኋላ በኢራን መንግሥት ውስጥ ያሉ አንጃዎች እና ታዋቂ ሰዎች ስምምነቱን አጥብቀው ሲተቹ ነበረ።

    ጠቅላይ መሪው ሞጅታባ ኻሜኒ ስምምነቱን በተመለከተ መልዕክታቸውን ካስተለላፉ በኋላ የሚሰነዘረው ትችት በእጅጉ ጠንክሮ ተሰምቷል።

    በተለይ ደግሞ ከስምምነቱ በኋላ ከተቃዋሚዎች መካከል አንዱ በድርድሩ እና በአመራር ኃላፊነት ላይ ተገቢውን ሚና አልተጫወቱም ያሏቸውን መሪዎች ለመግደል ከዛቱ በኋላ ጉዳዩ በእጅጉ ተካርሮ ነበር።

  5. ስምምነቱ ከተጣሰ አስፈላጊውን እርምጃ እንወስዳለን - ኢራን

    ከአሜሪካ በተደረሰው ስምምነት ላይ የትኛውንም ዓይነት ጥሰት በሚፈጸምበት ጊዜ ኢራን “ያለምንም ጥርጥር ተገቢ እና አስፈላጊውን እርምጃ በመውሰድ ምላሽ ትሰጣለች” ሲሉ የአገሪቱ ተጠባባቂ የመከላከያ ሚኒስትር ተናገሩ።

    የኢራን መንግሥት ይፋዊ የዜና ወኪል ኢርና እንደዘገበው ሚኒስትሩ ማጂድ ሬዛ ይህንን የተናገሩት ከኳታር ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የመከላከያ ሚኒስትር ጋር ባደረጉት የስልክ ውይይት ላይ ነው።

    የኢራን ተጠባባቂ ሚኒስትር የባሕረ ሰላጤው አገር ከሆነችው ኳታር ጋር አገራቸው የመከላከያ ትብብር ለማስፋት ያላትን ዝግጁነትም ገልጸዋል።

    ነገር ግን የመግባቢያ ስምምነት የተፈራረሟትን አሜሪካንን በጥርጣሬ እንደሚመለከቱ “ጠላታችንን አናምንም ጣቶቻችን ከመሳሪያችን ቃታ ላይ አይነሱም” ሲሉ ተናግረዋል።

    በየካቲት ወር መጨረሻ ገደማ አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ ጥቃት ከጀመሩበት ጊዜ አንስቶ ኢራን ኳታር ውስጥ ያሉትን ጨምሮ ሌሎች ዒላማዎችን በአጸፋ ጥቃት መትታለች።

    የኢራኑ ባለሥልጣን “ቀጣናው የውጭ ኃይሎች መጠቀሚያ መሆን የለበትም፣ የውጭ ኃይሎች በአካባቢው መኖራቸው ደኅንነትን የሚፈጥር ሳይሆን፤ አለመግባባትን፣ አለመተማመንን እና የደኅነንት ስጋትን ያስከትላል” ሲሉ በአካባቢው ያሉትን የአሜሪካ ኃይሎችን ከስሰዋል።

    አሜሪካ በመካከለኛው ምሥራቅ አገራት በተለይም በኳታር፣ በኩዌት እና በባህሬን ውስጥ የባሕር እና አየር ኃይል ጦር ሰፈሮች ያሏት ሲሆን፣ በጦነርቱ ወቅትም የኢራን ጥቃት ዒላማዎች ሆነው ቆይተዋል።

    ኳታር በአሁኑ ጊዜ ከፓኪስታን ጋር በመሆን ኢራን እና አሜሪካ ዘላቂ የሰላም ስምምነት ላይ እንዲደርሱ ጥረት እያደረገች ነው።

  6. ኢራን ከታገደባት ሀብት ውስጥ ስድስት ቢሊዮን ዶላር ሊለቀቅላት እንደሆነ ገለጸች

    ኢራን እንዳይንቀሳቀስ ከታገደባት 12 ቢሊዮን ዶላር ውስጥ ግማሹ ሊለቀቅ መሆኑን የአገሪቱ ፕሬዝዳንት መሱድ ፔዜሽኪያን ተናገሩ።

    አሜሪካ እና ኢራን አራት ወራት ያለፈውን ጦርነት ለመቋጨት በተፈራረሙት የመግባቢያ ስምምነት ላይ ከሰፈሩ ጉዳዮች መከካል የኢራን የታገደ ሀብት መለቀቅ አንዱ ነው።

    እስካሁን ሲደረጉ በነበሩ ንግግሮች ላይ ኢራን ጫና ውስጥ ላለውን ኢኮኖሚዋ እረፍት የሚያስገኘው ይህ ሀብት እንዲለቀቅ አጥብቃ ስትጠይቅ ቆይታለች።

    ከሁለት ሳምንት ገደማ በፊት የተፈረመው ሰነድ እንደሚገልጸው አሜሪካ “የታገዱ የኢራን ገንዘብ በሙሉ የማስለቀቅ” ኃላፊነትን ተቀብላለች።

    ትናንቱ ሰኞ ከአገሪቱ ታዋቂ የሃይማኖት አባቶች እና የእስልምና ሕግ ሊቃውንት ጋር ለመገናኘት ወደ ቆም ከተማ ያመሩት የኢራን ፕሬዝዳንት ፔዜሽኪያን፤ ከሀብቱ ውስጥ ግማሽ ያህሉ ሊለቀቅ እንደሆነ አመልክተዋል።

    ፕሬዝዳንቱ፤ “ኳታር ውስጥ ከሚገኘው አጠቃላይ 12 ቢሊዮን ዶላር የኢራን ሀብት ውስጥ ስድስት ቢሊዮን ዶላሩ ተለቅቆ ወደ አገር እንደሚመለስ” መናገራቸውን ኢርና የዜና ወኪል ዘግቧል። ቀሪውን ሀብት ለማስለቀቅ የሚደረገው ጥረት አሁንም እንደቀጠለ ገልጸዋል።

    በተጨማሪም ፕሬዝዳንቱ፤ አሜሪካ ለተፈረመው የመግባቢያ ስምምነት “ታማኝ ሆና የምትቀጥል ከሆነ” ኢራንም “ግዴታዎቿን እንደምትወጣ” ገልጸዋል።

    ኢራን ሀብቱ ሊለቀቅላት እንደሆነ ብትናገርም እስካሁን ድረስ ስለ ጉዳዩ ከአሜሪካ በኩል ማረጋገጫ አልተሰጠም።

    ይሁን እንጂ ሁለቱ አገራት በተፈራረሙበት ወቅት ማብራሪያ የሰጡ አንድ የአሜሪካ ባለሥልጣን፤ ቀጣይ ድርድር በሂደት ላይ እያለ ከኢራን ሀብት ውስጥ የተወሰነው ሊለቀቅ እንደሚችል አንድ የአሜሪካ ባለሥልጣን ተናግረው ነበር።

    ኢራን የመግባቢያ ስምምነቱ እንደተፈረመ ውዲያውኑ ሀብቱ እንዲለቀቅላት ፈልጋ የነበረ ቢሆንም ኋላ ላይ ግን “ግዴታዎቿን ከተወጣች ብቻ ከሀብቷ ከፊሉን ማግኘት እንደምትችል” መቀበሏን ገልጸዋል።

  7. ዴሞክራቲክ ኮንጎ የኢቦላ ሥርጭትን ለመግታት በዋና ከተማዋ የሚደረጉ የሕዝብ ኹነቶችን አገደች

    የዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ የአገር ውስጥ ሚኒስቴር፤ የኢቦላ ቫይረስ ሥርጭትን ለመግታት ሲባል ዋና ከተማዋ ኪንሻሳ እና በሌሎች ሦስት ከተሞች ውስጥ ሰዎች የሚሰበሰቡባቸው ኹነቶች እንዳይካሄዱ ክልከላ መጣሉን አስታወቀ።

    በአገሪቱ የተከሰተው የገዳዩ በሽታ ወረርሽኝ እስካሁን ድረስ ከዋና ከተማዋ 1,800 ኪሎ ሜትር ገደማ ርቀት ላይ በሚገኙት በሦስት ምሥራቃዊ ግዛቶች ውስጥ መሠራጨቱ ተረጋግጧል። ባለሥልጣናቱ በሽታው 18 ሚሊዮን ነዋሪዎች ባሏት ኪንሻሳ ውስጥም ሊሠራጭ ይችላል የሚል ስጋት አላቸው።

    ተመሳሳይ ዕገዳ ተጣለባቸው ሌሎቹ ሦስት ከተሞች ኢቦላ መገኘቱ ከተረጋገጠባቸው አካባቢዎች ጋር ይጎራበታሉ።

    የዴሞክራቲክ ኮንጎ ታዋቂ ተቃዋሚ ፖለቲከኞች እርምጃው በሚቀጥለው ሳምንት ረቡዕ ሊካሄድ የታቀደውን የተቃውሞ ሰልፍ ለማደናቀፍ ያቀደ ነው በሚል ተቃውመውታል።

    ‘ላሙካ’ የተሰኘው የተቃዋሚ ጥምረት ቃል አቀባይ ፕሪንስ ኢፔንጌ፤ በበሽታው ኪንሻሳ ውስጥ መከሰቱ ባለመረጋገጡ የመንግሥት ውሳኔ “ፖለቲካዊ” ነው ሲሉ ተችተዋል። “ሕጋዊ አይደለም። ይህንን ውሳኔ ልንቀበል አንችልም” ሲሉ ለቢቢሲ ተናግረዋል።

    ‘ኤንቮል’ የተሰኘው ሌላ የተቃዋሚ ፓርቲ ዋና ፀሐፊ ደግሞ፤ ተቃዋሚዎች እገዳውን ችላ በማለት ሰልፉ ላይ እንዲገኙ አሳስበዋል። የተላለፈው ትዕዛዝ “ከሕብረተሰብ ጤና ውሳኔነት ይልቅ ፖለቲካዊ እርምጃ ነው” ብለዋል።

    የዴሞክራቲክ ኮንጎ መንግሥት ስለቀረበው ትችት እስካሁን ምላሽ አልሰጠም።

    በሚቀጥለው ሳምንት እንዲካሄድ የታቀደው ሰልፍ የተዘጋጀው ‘ሲ64’ በተባለው እና በቅርቡ የወጣ ሕግን ለመቃወም በተቋቋመው ጥምረት የተዘጋጀ ነው። ተቃዋሚዎች፤ ሕጉ ፕሬዝዳንቱ ፌሊክ ቲሼኬዲ ከሁለት የሥልጣን ዘመን በላይ በመሪነት እንዲቆዩ እንደሚያስችላቸው ይገልጻሉ።

  8. የቀድሞው አሜሪካ ፕሬዝዳንት ባይደን፣ ትራምፕን “ከንቱ” ሲሉ ዘለፉ

    በሳምንቱ መጨረሻ በተካሄደ የገቢ ማሰባሰቢያ ላይ ንገግር ያደረጉት የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ጆ ባይደን ተተኪያቸው ዶናልድ ትራምፕ የሚያስገነቧቸውን “የታይታ ፕሮጀክቶች” በማንሳት “ከንቱ” ሲሉ ዘለፉ።

    ባይደን በቅዳሜ ዕለቱ የዴሞክራቲክ ፓርቲ ዝግጅት ንግግራቸው ፕሬዝዳንት ትራምፕ በዋይት ሐውስ የግብር አዳራሽ ለመገንባት እንዲሁም የዋሽንግተንን አንጸባራዊ የውሃ ገንዳ ለማደስ የያዙትን ዕቅድ አጣጥለዋል።

    ቢቢሲ የባይደንን ንግግር በተመለከተ ከዋይት ሐውስ አስተያየት ለማግኘት ጥያቄ አቅርቧል።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ የቀድሞው መሪ በሥልጣን ላይ ሳሉ የፈጸሟቸውን ተግባራት በተደጋጋሚ ተችተዋል፤ ባይደንም ተመሳሳይ ምላሽ ሰጥተዋል።

    ይሁን እንጂ ባይደን 10 ደቂቃ በቆየው የቅዳሜ ዕለቱ ንግግራቸው ያሰሙት ትችት ከምንጊዜውም የበለጠ ጠንካራ ነበር።

    “የታይታ ፕሮጀክቶቹ ብቻ አይደሉም፤ የግብር አዳራሽ ለመሥራት የዋይት ሐውስ የቀኝ ክንፍን ማፍረሱ፣ በኬኔዲ ሴንተር ሕንጻ ላይ የገዛ ራሱን ለማክበር ስሙን ማስቀመጡ፣ አንጸባራቂውን የውሃ ገንዳ ለመጠገን የራሱን የውሃ ገንዳ ሰው መቅጠሩ ጭምር ነው” ብለዋል።

    “ውይ! እንዴት ያለው ከንቱ [ሰው] ነው” ሲሉም አክለዋል።

    ባይደን በንግግራቸው የጠቀሱት ፕሬዝዳንት ትራምፕ በ‘ጆን ኤፍ ኬኔዲ ሴንተር ፎር ፐርፎርሚንግ አርትስ’ ሕንጻ የፊት ገጽ ላይ ስማቸውን ለማስፈር ያደረጉትን ሙከራ ነው።

    ፕሬዝዳንቱ ስማቸውን አጽፈው የነበረ ቢሆንም ፍርድ ቤት እንዲወርድ ትዕዛዝ አስተላልፏል።

    ፕሬዝዳንቱ 400 ሚሊዮን ዶላር የሚያወጣውን የግብር አዳራሽ ለመገንባት ሲሉ የቤተ መንግሥቱ የቀኝ ክንፍ እንዲፈርስ በማድረጋቸው የሚቀርብባቸውን ወቀሳ ሲከላከሉ ቆይተዋል።

    ግንባታው የአገር ደኅንነት እና የመንግሥት እንግዳዎችን ለማስተናገድ አስፈላጊ እንደሆነ ተናግረዋል።

  9. ፕሬዝዳንት ትራምፕ በኢራን ጥያቄ መሠረት ነገ ዶሃ ውስጥ ንግግር ይደረጋል አሉ

    የአሜሪካ እና ኢራን ባለሥልጣናት ነገ ኳታር ውስጥ ለድርድር እንደሚገናኙ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አስታወቁ።

    ትራምፕ በትሩዝ ሶሻል ማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ባሰፈሩት ፅሑፍ፤ “ኢራን ስብሰባ እንዲደረግ ጠይቃለች። ነገ ዶሃ ውስጥ ይካሄዳል” ብለዋል።

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ነገ ማክሰኞ ይካሄዳል ስላሉት ስብሰባ ተጨማሪ ማብራሪያ አልሰጡም።

    የዋይት ሐውስ ቃል አቀባይ ካሮላይን ሌቪት ግን ዋነኞቹ የአሜሪካ ተደራዳሪዎች ጃሬድ ኩሽር እና ስቲቭ ዊትኮፍ “በዚህ ሳምንት ዶሃ ውስጥ የሚካሄድ የከፍተኛ ባለሥልጣናት ስብሰባ ላይ ለመሳተፍ ወደ ዶሃ እንደሚበርሩ” ለፎክስ ኒውስ ተካግረዋል።

    ከዚህ የከፍተኛ ባለሥልጣናት ስብሰባ ጎን ለጎን የቴክኒካል ንግግር እንደሚካሄድም አክለዋል።

    የኢራን ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ካዜም ጋሪባባዲ ግን ዛሬ በሰጡት አስተያየት ሁለቱ አገራት በዚህ ሳምንት ቴክኒካዊ ንግግር ለማድረግ ዕቅድ ይዘዋል መባሉን አስተባብለው ነበር።

    የኢራን ቴክኒካዊ ድርድር ቡድን ኃላፊ የሆኑት ጋሪባባዲ “የሌላኛውን ወገን ግዴታዎች አፈጻጸም መከታተልን ጨምሮ ከኳታር ጋር የሚደረጉት ምክክሮች ቢቀጥሉም፤ የሥራ ቡድኖቹ ቴክኒካዊ ንግግር ዶሃ ውስጥ ይካሄዳል በሚል በአንዳንድ መገናኛ ብዙኃን የተሠራጨው ዘገባ ግን የተረጋገጠ አይደለም” ብለዋል።

    የኢራኑ ባለሥልጣን ይህንን ከማለታቸው አስቀድሞ የተወሰኑ መገናኛ ብዙኃን ስማቸው ያልተጠቀሰ የአሜሪካ ባለሥልጣናትን ዋቢ በማድረግ፤ ቴህራን እና ዋሽንግተን የሚፈጽሟቸውን የአጸፋ ጥቃቶች ለማቆም እና ድርድሩን ለመቀጠል መስማማታቸውን ዘግበው ነበር።

    የአሜሪካዎቹ የዜና ምንጮች ሲኤንኤን እና አክሲዮስ ደግሞ የቴክኒካዊ ድርድሩ ቀጣይ ክፍል ነገ ማክሰኞ ኳታር ውስጥ እንደሚካሄድ አስነብበው ነበር።

    እነዚህ ዘገባዎች የወጡት አሜሪካ እና ኢራን አንዳቸው ሌላኛቸው የተኩስ አቁም ስምምነቱን እንደጣሱ በመግለጽ ክስ ሲያሰሙ ከቆዩ በኋላ ነው። ባለፉት ቀናት በሆርሙዝ ወሽመጥ ውስጥ እና በዙሪያው በርካታ ጥቃቶች የተፈጸመዋል።

  10. የደቡብ አፍሪካ ከፍተኛ የፖሊስ አዛዥ ከግድያ ሙከራ አመለጡ

    ከደቡብ አፍሪካ ከፍተኛ የፖሊስ አዛዦች አንዱ የሆኑት ሜጀር ጀነራል ፌሮዝ ካሀን ከግድያ ሙከራ ማምለጣቸውን ፖሊስ አስታወቀ።

    የወንጀል ምርመራ ክፍል ምክትል ኃላፊ የሆኑት ሜጀር ጀነራል ፌሮዝ ትናንት እሑድ ምሽት ወደ ቤታቸው እየነዱ ሳለ ጥይት እንደተተኮሰባቸው ተገልጿል። ወደ ድንገተኛ የሕክምና ክፍል መወሰዳቸውም ተዘግቧል።

    በደቡብ አፍሪካ በፖሊስ ኃይል የሚፈጸም ወንጀልን በተመለከተ ምርመራ የሚያካሂድ ኮሚቴ የተዋቀረ ሲሆን፤ ከፍተኛ የፖሊስ አዛዡ ከቀናት በኋላ ለኮሚቴው ቃላቸውን እንደሚሰጡ ይጠበቅ ነበር።

    የደቡብ አፍሪካ የፖሊስ ቃል አቀባይ ብርጋዲየር አትሌንዳ ሜት ክስተቱ ላይ ምርመራ መከፈቱን አስታውቀዋል።

    “ክስተቱ፤ መርማሪ ኮሚቴው ፊት ሊቀርቡ ከመሆኑ ጋር የተያያዘ ነው ማለት ወቅቱን ያልጠበቀ እና ኃላፊነት የጎደለው ነው” ብለዋል።

    የምርመራ ኮሚቴው የተዋቀረው ከፍተኛ የፖሊስ አዛዥ ሌተናንት ጀነራል ናለናሀል ምክዌንዚ የወንጀል ቡድኖች በመንግሥት መዋቅር ውስጥ ሰርገው ገብተዋል ብለው በመክሰሳቸው ነበር።

  11. ኢራን እና አሜሪካ በቴክኒክ ጉዳዮች ውይይት እንደሚቀጥሉ ተዘገበ

    ኢራን እና አሜሪካ የተኩስ ልውውጡን ለመግታት መስማማታቸውን ተከትሎ የመግባቢያ ሰነዱ ላይ ያሉ የቴክኒክ ጉዳዮችን በተመለከተ ውይይት እንደሚቀጥሉ የዋሽንግተን ባለሥልጣን ገለጹ።

    ኤኤፍፒ ያነጋገራቸው የአሜሪካ ባለሥልጣን “በስምምነቱ ያሉ ሁሉም የቴክኒክ ጉዳዮችን በተመለከተ ውይይቶች ይቀጥላሉ። ለአሁኑ ሁለቱም ወገኖች ግጭቱን ከማባባስ ይቆጠባሉ። መርከቦችም በነጻነት መጓዝ ይችላሉ” ብለዋል።

    የኢራን ባለሥልጣናት እስካሁን ድረስ ጉዳዩን በተመለከተ አስተያየት አልሰጡም።

    የሆርሙዝ ወሽመጥ አስተዳደርን በተመለከተ ውዝግቦች የተነሱ ሲሆን፤ ቴህራን እና ዋሽንግተን ባለፉት ቀናት ግጭት ውስጥ ገብተዋል።

    አሁን ላይ ግጭቱን ለመግታት መስማማታቸው ተገልጿል።

  12. ፓኪስታን በአፍጋኒስታን ላይ ባደረሰችው ጥቃት በርካታ ሰዎች መገደላቸው ተገለጸ

    ፓኪስታን በአፍጋኒስታን ላይ የአየር ጥቃት ካደረሰች በኋላ እግረኛ ጦሯን ማሰማራቷ ተገለጸ።

    የአፍጋኒስታን ባለሥልጣናት እንደተናገሩት በምዕራብ ድንበር በተፈጸመው ጥቃት ብዙ ንጹኃን ዜጎች ተገድለዋል።

    የታሊባን መንግሥት ጥቃቱን “የፈሪነት ድርጊት” እንዲሁም “ጭፍጨፋ እና ወንጀል” ሲል አውግዟል። ቢያንስ 100 ሰዎች እንደተጎዱ ወይም እንደተገደሉም አስታውቋል።

    የፓኪስታን የመረጃ ሚኒስትር አቱላህ ታራር እንዳሉት ምሽጎች ላይ ባነጣጠረው ጥቃት 29 ወታደሮች ተገድለዋል።

    “በቅርቡ በንጹኃን ላይ ለተፈጸመ የሽብር ጥቃት የአጸፋ ምላሽ ነው” ብለዋል።

    ታሊባን እንዳለው ፓኪስታን ጥቃት የፈጸመችው የንጹኃን መኖሪያ ቤቶች አካባቢ ነው። ፓኪስታን ግን ዒላማ ያደረገችው የወታደሮችን ምሽግ መሆኑን በመግለጽ አስተባብላለች።

    ፓኪስታን ሽብርተኞችን በመደበቅ አፍጋኒስታንን ስትከስ ቆይታለች። የታሊባን መንግሥት ግን ክሱን አስተባብሏል።

  13. አሜሪካ እና ኢራን ግጭቱን “ለመግታት” መስማማታቸው ተገለጸ

    አሜሪካ እና ኢራን ባለፉት ጥቂት ቀናት የገቡበትን ግጭት “ለመግታት” መስማማታቸው ተዘገበ።

    የዋሽንግተንን ባለሥልጣን ጠቅሰው የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን እንደዘገቡት ሁለቱ አገራት የተኩስ ልውውጡን ለማቆም ተስማምተዋል።

    በሆርሙዝ ወሽመጥ እና በዙሪያው ሁለቱ አገራት የተኩስ ልውውጥ ሲያደርጉ ቆይተዋል።

    አሜሪካ እና ኢራን የተኩስ አቁም ስምምነትን በመጣስ አንዳቸው ሌላቸውን ሲከሱም ነበር።

    የቢቢሲ የአሜሪካ አጋር ሲቢኤስ ያነጋገራቸው ባለሥልጣን እንዳሉት አሁን ላይ መርከቦች በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል “በነጻነት” ማለፍ ይችላሉ።

    አገራቱ ጦርነቱን ለመግታት የሚያደርጉትን ውይይት እንደሚቀጥሉም ገልጿል።

    ኢራን ጥቃት ለማቆም መስማማቷን በሚገልጸው ዘገባው ላይ እስካሁን አስተያየት አልሰጠችም።

    ኢራን እና አሜሪካ የፈረሙት የመግባቢያ ሰነድ “በሁሉም ግንባሮች ወታደራዊ ግጭት” እንደሚቆም ይገልጻል።

    ኢራን በስምምነቱ መሠረት በ60 ቀናት ውስጥ በሆርሙዝ ወሽመጥ የንግድ መርከቦች ከክፍያ ነጻ እንዲያልፉ ትፈቅዳለች።

    ባለፉት ቀናት ሁለቱ አገራት የተኩስ ልውውጥ ማድረጋቸው የመግባቢያ ሰነዱን አደጋ ውስጥ ከትቶታል።

  14. ኢራን ስምምነቱ ከተጣሰ “ከፍተኛ እርምጃ” እንደምትወስድ አስታወቀች

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ “ስምምነቱን በጣሰው በዛኛው ወገን ላይ ከፍተኛ እርምጃ እንወስዳለን” ሲሉ አስጠነቀቁ።

    ከኢራቅ ፕሬዝዳንት ናዚር አሚዲ ጋር የተወያዩት አራግቺ “በአሜሪካ እና በጽዮናዊው አስተዳደር አንዳንድ መግባቢያዎች መጣሳቸው ሰላም እና መረጋጋት በቀጣናው እንዳይሰፍን ከፍተኛ መሰናክል ይሆናል” ብለዋል።

    የስምምነቱ “በተለይ የመጀመሪያው አንቀጽ” መጣስ ሰላም እና መረጋጋትን እንደሚያውክ ገልጸዋል።

    “የመግባቢያ ሰነዱን በጥሩ መንፈስ እና ለስምምነቱ ታማኝ በመሆን መተግበር እንፈልጋለን” ብለዋል።

    ሆኖም ግን ስምምነቱ “በዚያኛው ወገን ከተጣሰ ከፍተኛ እርምጃ እንወስዳለን” በማለት አስጠንቅቀዋል።

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ በኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥ አስተዳደር ውስጥ ማንኛውም ጣልቃ ገብነት ውጥረቱን እንደሚያባብስ መናገራቸውም ይታወሳል።

    በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል እያለፈ የነበረ በፓናማ የተመዘገበ መርከብ ትናንት ቅዳሜ ጥቃት ከደረሰበት በኋላ አሜሪካ በኢራን ላይ ጥቃት ፈጽማለች።

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ በአጸፋ ምላሽ በኩዌት እና ባሕሬን በሚገኙ የአሜሪካ መሠረተ ልማቶች ላይ የድሮን እና ሚሳዔል ጥቃቶች ማድረሱን ገልጿል።

    ኩዌት እና ባሕሬን በኢራን የደረሰባቸውን ጥቃት አውግዘዋል።