በጋና በተከሰተ የጎርፍ አደጋ ቢያንስ 13 ሰዎች ሞቱ
በጋና መዲና አክራ በተከሰተ የጎርፍ አደጋ ሳቢያ ቢያንስ 13 ሰዎች መሞታቸውን የአገሪቱ የእሳት አደጋ መከላከያ መሥሪያ ቤት አስታወቀ።
በቀጣይም ከአገሪቱ ምሥራቃዊ ክፍል መነሻውን ያደረገ አውሎ ንፋስ እና ዝናብ ሊኖር ስለሚችል ዜጎች ከቤት እንዳይወጡ ወይም ከፍ ያለ ሥፍራ ላይ እንዲሆኑ ማሳሰቢያ ተሰጥቷል።
ካለፈው እሑድ ዝናብ የተከማቸ ውሃ መጠኑ እየቀነሰ ቢመጣም የሟቾች ቁጥር ሊጨምር እንደሚችል ተገልጿል።
በተለይም ዝቅተኛ አካባቢዎች ለአደጋ ተጋላጭ ሆነዋል።
በማኅበራዊ ሚዲያ የታዩ ተንቀሳቃሽ ምሥሎች ቤቶች እና ተሽከርካሪዎች በጎርፍ ተውጠው ያሳያሉ፤ ሕንጻዎች ላይም ጉዳት ደርሷል።
በጎርፍ ጉዳት በደረሰባቸው አካባቢዎች ፖሊስ እና የእሳት አደጋ ተከላካዮችን ጨምሮ የድንገተኛ አደጋ ሠራተኞች ተሰማርተዋል።
የጋና የአገር ውስጥ ሚኒስቴር እንዳለው ያለውን ሁኔታ እንዲከታተሉ እና የሰዎችን ሕይወት እንዲሁም ንብረት እንዲያድኑ ሠራተኞቹ ተሰማርተዋል።
እስካሁን 470 ሰዎችን ማትረፍ እንተቻለ ተገልጿል።
በጎርፉ ምክንያት በአክራ የሚገኝ የፕላስቲክ ፋብሪካ ውስጥ እሳት ተነስቷል።