አሜሪካ እና ሳዑዲ በኢራቅ ውስጥ የፈጸሙትን ጥቃት ኢራን አወገዘች
የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አሜሪካ እና ሳዑዲ አረቢያ በጥምረት ኢራቅ ውስጥ የፈጸሙትን ጥቃት “በጽኑ እንደሚያወግዝ” አስታወቀ።
ጥቃቱ የአሜሪካ እና ሳዑዲ ጥቃት ጦርነቱን በመካከለኛው ምሥራቅ ለማስፋፋት ያለመ ነው ሲልም ወቅሷል።
ኢራን ሁለቱን አገራት “ነውጠኛ” ስትል ያወገዘች ሲሆን፣ የፈጸሙት ጥቃት የተባበሩት መንግሥታት ስምምነትን እንደሚጥስም አስታውቃለች።
ጥቃቱ የአሜሪካ እና የጽዮናዊው [እስአኤል] መንግሥት “ፍላጎት” እንደሆነ የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ያወጣው መግለጫ ይጠቅሳል።
“ጽዮናዊው መንግሥት ጦርነቱን እና ግጭቱን ወደ ምዕራብ እስያ ማስፋፋት ይፈልጋል” ሲልም የእስራኤልን መንግሥት ከስሷል።
አሜሪካ እና ሳዑዲ በኢራቅ የሚገኙ እና በኢራን የሚደገፉ ታጣቂዎች ላይ ጥቃት መፈጸማቸውን ገልጸዋል።
የኢራቅ ‘ፖፑላር ሞቢላይዜሽን ፎርስ’ ቡድን በጥቃቱ ቢያንስ 20 አባላቱ እንደተገደሉበት እና 32 እንደቆሰሉበት አስታውቋል።
የአሜሪካ ጦር ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም) “ኢራቅ ውስጥ በኢራን የሚደገፈው አሸባሪ ቡድን ላይ አነጣጥረን ጥምር ጥቃት [ከሳዑዲ አረቢያ ጋር] ፈጽመናል” ብሏል።
ሳዑዲ በበኩሏ ጥቃቱ የተፈጸመው ቡድኑ የነዳጅ ማውጫዎቿን ዒላማ ካደረገ በኋላ እነደሆነ አስታውቃለች።