ለሳምንታት ተቃውሞ የተካሄደባቸው የሕንድ ትምህርት ሚኒስትር ሥልጣናቸውን ለቀቁ
ከአንድ ወር በላይ በዘለቀ በወጣቶች የሚመራ የተቃውሞ እንቅስቃሴ ከትምህርት ሚኒስትርነት እንዲወርዱ ሲጠየቁ የነበሩት ዳርሜንድራ ፕራድሃን፤ ከሥልጣን መልቀቃቸውን አስታወቁ።
አንድ ባለሥልጣን ስራ አጥ ወጣቶችን “በረሮዎች” ብለው በመጥራታቸው ለስላቅ ከተመሰረተ በኋላ የተቃውሞ እንቅስቃሴውን የመራው ‘ኮክሮች ጃንታ ፓርቲ’፤ የሚኒስትሩን ከሥልጣን መውረድ ተከትሎ ተቃውሞው ማብቃቱን አስታውቋል።
ግንቦት ላይ ተቃውሞ የተጀመረው ወደ ከፍተኛ የትምህርት ተቋም ለመግባት የሚሰጠው ፈተና ሾልኮ በመውጣቱ ነው። በዚህ ምክንያት ራሳቸውን ያጠፉ ተማሪዎች እንዳሉ ተገልጿል።
የትምህርት ሚኒስትሩን ተጠያቂ ያደረጉት እና ራሳቸውን 'ኮክሮችስ' ብለው የሚጠሩ ወጣት ተቃዋሚዎች ተደጋጋሚ ሠልፎችን ሲያደርጉ ቆይተዋል።
ይህንን ሰልፍ ሲመራ የነበረው ‘ኮክሮች ጃንታ ፓርቲ’ ተጠያቂነት እንዲሰፍን እንዲሁም የትምህርት ስርዓቱ ላይ ለውጥ እንዲደረግ ዘመቻ አድርጓል። ፓርቲው ዛሬ ቅዳሜ የትምህርት ሚኒስትሩ ከሥልጣን መውረዳቸውን በበጎ ቢቀበለውም፤ የወጣቶች ጥያቄ ከዚህም የተሻገረ መሆኑን ገልጿል።
ኋላ ላይም የፓርቲው ቃል አቀባይ መንግሥት የቀረቡትን ጥያቄዎች በሙሉ መቀበሉን አስታውቀዋል። የሚኒስትሩ ከሥልጣን መልቀቅ አንዱ ጥያቄ ነበር።
መንግሥት ፈተናው ሾልኮ ከወጣ በኋላ ራሳቸውን አጥፍተዋል ለተባሉ ተጎጂዎች ቤተሰቦች 103 ሺህ ዶላር ካሳ ለመስጠት መስማማቱንም ቃል አቀባዩ ገልጸዋል። ለአንድ ወር በዘለቀው ተቃውሞ የተሳተፉ ወጣቶች ላይም ሕጋዊ እርምጃ እንደማይወሰድ ተናግረዋል።
የፕራድሃንን የሥልጣን መልቀቂያ የተቀበሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ፤ እስካሁን አዲስ የትምህርት ሚኒስትር እስካሁን አልተኩም።
ወጣት ተቃዋሚዎች የባለሥልጣኑን መውረድ እንደ ድል የቆጠሩት ሲሆን ሰልፍ ሲያደርጉ በነበሩበት ስፍራ ተገኝተው ደስታቸውን እየገለጹ ነው።