አዲስ ጦርነት ከተቀሰቀሰ ኢራን የበለጠ ምላሽ በመስጠት የተራዘመ ጦርነት እንደምታካሂድ አስታወቀች
ከፍተኛ የኢራን ወታደራዊ ባለሥልጣናት አሜሪካ ሌላ ዙር ጥቃት በአገራቸው ላይ የምትከፍት ከሆነ ከባድ ጥቃት በመሰንዘር ለተራዘመ ጦርነት እየተዘጋጁ መሆናቸውን ተናገሩ።
የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ከፍተኛ ባለሥልጣን ራሱል ሳናኢ-ራድ ከአሜሪካ ጋር አዲስ ጦርነት የሚቀሰቀስ ከሆነ ቴህራን “ከዚህ በፊት ከነበረው በጠነከረ ሁኔታ” ምላሽ እንደምትሰጥ አስታውቀዋል።
ፋርስ የተባለው የኢራን ዜና ወኪል እንደዘገበው የአብዮታዊ ዘቡ ጠቅላይ አዛዥ ፖለቲካዊ ርዕዮተ ዓለም ጉዳዮች መኮንን የሆኑት ባለሥልጣን "ጠላት በአገር ውስጥ ክፍፍልን በመፍጠር እና የኢኮኖሚ ጫና በማሳደር ተቃውሞዎችን መፍጠር እንደሚችል በማሰብ ጥረት እያደረገ ነው” ብለዋል።
በተጨማሪም የኢራን ሠራዊት ምክትል ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም አሊሬዛ ሼክ በበኩላቸው የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ “ለተራዘመ ጦርነት” እና ቀጣይነት ላለው ዘመቻ ዝግጁ መሆኗን ተናግረዋል።
እንዲሁም የኢራን የጦርነት መርኅ ግልጽ ከሆነው የመከላከል አቋም ወደ “ጥቃትን ቀድሞ ማስቀረት እና ማጥቃት” መሸጋገሩን እንዲሁም የበለጠ ሚሳዔል እና ድሮን የማምረት አቅምን ቀጣይነት ላለው ዘመቻ ወሳኝ መሆኑን አመልክተዋል።
በሳምንታት ውስጥ ይጠናቀቃል የተባለው አሜሪካ በኢራን ላይ የከፈተችው ጦርነት ሞቅ ቀዝቀዝ እያለ ወራትን ያስቆጠረ ሲሆን፣ በድርድር እንዲያበቃ ለማድረግ ጥረት እየተደረገ ነው።