ቀጥታ, የየመን የባሕር ዳርቻዎችን በመቆጣጠር በቀይ ባሕር ላይ ስጋት የደቀኑት ሁቲዎች እና የኢራን ጥሪ

የየመን ሁቲ ታጣቂዎች ወደ ቀይ ባሕር በሚስገባው ወሳኙ የባብ ኤል መንደብ መተላላፊያ አቅራቢያ የሚገኙ ወደቦችን እየተቆጣጠሩ ባሉበት በአሁኑ ወቅት ኢራን ድርድር እንዲጀመር ጥሪ አቀረበች።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. የየመን የባሕር ዳርቻዎችን በመቆጣጠር በቀይ ባሕር ላይ ስጋት የደቀኑት ሁቲዎች እና የኢራን ጥሪ

    የየመን ሁቲ ታጣቂዎች ወደ ቀይ ባሕር በሚስገባው ወሳኙ የባብ ኤል መንደብ መተላላፊያ አቅራቢያ የሚገኙ ወደቦችን እየተቆጣጠሩ ባሉበት በአሁኑ ወቅት ኢራን ድርድር እንዲጀመር ጥሪ አቀረበች።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአገሪቱ አጋር የሆኑት ሁቲ ታጣቂዎች በየመን ውስጥ እያካሄዱት ባለው ጦርነት እየታየ ያለውን ለውጥ በመጥቀስ ባወጣው መግለጫ የመን ላይ የተጣለው ወታደራዊ ከበባ እንዲነሳ እና ድርድር እንዲጀመር ጥሪ አቅርቧል።

    በኢራን መንግሥታዊ የዜና ወኪል ኢርና በኩል ይፋ የተደረገው መግለጫ፣ “የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ፣ የሙስሊሙን ሕዝብ ጥቅም መጠበቅ አስፈላጊነትን እያሳሰበች፣...በአሜሪካ ድጋፍ እየተስፋፋ ያለውን የጽዮናዊው ሥርዓት ጥቃት እና መስፋፋት በምትጋፈጥበት ወቅት፣ የየመን ችግር በከበባ እና በወታደራዊ ጥቃት ሊፈታ እንደማይችል ታሳስባለች” ብሏል።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጨምሮም የየመን ኃይሎች “በተስማሙበት የሰላም ፍኖተ ካርታ መሠረት ውይይቱ በአስቸኳይ እንዲቀጥል እና ስምምነት የተደረሰባቸው ጉዳዮች መተግበራቸው” አስፈላጊ መሆኑን አጽንኦት ሰጥቶ፣ ኢራንም “ማንኛውንም ጥረት ለመደገፍ ዝግጁ ናት” ብሏል።

    ይህ የኢራን መግለጫ የወጣው፣ ሁቲዎች በየመን የሚገኘውን የሞካ ወደብን ጨምሮ አንዳንድ የአገሪቱን አካባቢው በመቆጣጠር እየገሰገሱ እና በሳዑዲ አረቢያ የሚደገፉት የየመን መንግሥት ኃይሎች እያፈገፈጉ መሆናቸው እየተዘገበ ባለበት ጊዜ ነው።

    ትናንት ሐሙስ ጳጉሜ 5 በሳዑዲ አረቢያ ድጋፍ የሚያገኙት የየመን ኃይሎች እና አጋሮቻቸው ዱባብ ከተባለችው ሌላ ወደብ መውጣታቸውም ተዘግቧል።

    የሞካ ወደብ በሁቲዎች እጅ መውደቁ፣ በኢራን የሚደገፉት ሁቲዎች የነዳጅ እና የሸቀጦች ዋነኛ መተላለፊያ በሆነው የቀይ ባሕር መስመር ላይ ያላቸውን ቁጥጥር ያጠናክራል።

    ይህ ወደብ ቀይ ባሕርን ከሕንድ ውቅያኖስ በሚያገናኘው የባብ ኤል መንደብ ባሕር ወሽመጥ አካባቢ የሚገኝ በመሆኑ ለባሕር ላይ እንቅስቃሴ ወሳኝ ነው።

    በተጨማሪም የፈረንሳይ ዜና ወኪል ኤኤፍፒ ሐሙስ ዕለት አንድ ወታደራዊ ምንጭን ጠቅሶ እንደዘገበው፣ ሁቲዎች “ሮኬቶች እና ታጣቂዎችን በጫኑ ጀልባዎች በመጠቀም በፈጸሙት ወረራ” በደቡባዊ ቀይ ባሕር የሚገኘውን ዛቅር የተባለውን ደሴት ተቆጣጥረዋል።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ የሁቲ ታጣቂዎች እንደ ዋነኛ ጠላት የሚመለከቷት የሳዑዲ አረቢያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፋይሳል ቢን ፋርሃን ከኢራኑ አቻቸው አባስ አራግቺ ጋር በየመን ስላለው ሁኔታ በስልክ ተወያይተዋል።

    ሳዑዲ ዓለም አቀፍ እውቅና ያለውን የየመን መንግሥት እና ሌሎች ፀረ ሁቲ ታጣቂዎችን የምትደግፍ ሲሆን፣ ኢራን ደግሞ የሁቲዎች አጋር መሆኗ ይታወቃል።

  2. የየመን ሁቲ ታጣቂዎች ሞካ የተባለ ወደብን መቆጣጠራቸው ተዘገበ

    በሳዑዲ ከሚደገፈው የየመን መንግሥት ጋር ከባድ ውጊያ ውስጥ የሚገኙት የሁቲ ታጣቂዎች ሞካ የተባለውን በቀይ ባሕር ላይ የምትገኘው ሞካ የተባለችውን ወደብ መቆጣጠራቸውን ሮይተርስ የዜና ወኪል የየመን መንግሥት ባለሥልጣናትን ጠቅሶ ዘገበ።

    እየተካሄዱ ባሉ ውጊያዎች ሁቲዎቹ በቀይ ባሕር ላይ የሚገኙ ስትራቴጂያዊ ወደቦችን ለመቆጣጠር እየጣሩ ሲሆን፣ ይህም መርከቦች ከሕንድ ውቅያኖስ ወደ ቀይ ባሕር የሚገቡበትን ወሳኙን የመርከቦች መተላለፊያ በር ባብ ኤል መንደብ ወሽመጥ ላይ ላይ ያላቸውን ቁጥጥር የበለጠ እንዲያጠናክሩ ያስችላቸዋል።

    ከዚህ ቀደም በሳዑዲ አረቢያ የሚደገፉ ኃይሎች እና በሁቲዎች መካከል በየመን የተፈጠረው ከባድ ግጭት፣ ጦርነቱ የበለጠ እንዳይሰፋ ስጋት አስከትሎ ነበር።

    ሁቲዎች በመርከቦቿ ላይ በጣሉት የእንቅስቃሴ ዕገዳ እና በመሠረተ ልማቶቿ ላይ ለተፈፀሙ ጥቃቶች ምላሽ ሳዑዲ በየመን ውስጥ በርካታ ቦታዎችን በአየር ደብድባለች።

    በሁቲዎች ጥቃት ምክንያት ውጥረት እየተባባሰ መምጣቱን ተከትሎ፣ በደቡብ ምዕራብ ሳዑዲ አረቢያ በምትገኘው የካሚስ ሙሻይት ከተማ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መታወጁ ተሰምቷል።

  3. የአሜሪካ እና የኢራን ጦርነት እንዴት ሊቆም ይችላል?

    የአሜሪካ እና የኢራንን ጦርነት ለማስቆም ተጨባጭ የሆነ ስምምነት ላይ ይደረሳል የሚለው ተስፋ ደብዝዞ ይታያል፤ ሁለቱ ተፋላሚ ወገኖች ጥቃቶችን በመፈጸም እና የማይለሳለሱ አቋሞችን በማንጸባረቅ ላይ ናቸው።

    እነዚህ ጥቃቶች የተከሰቱት አሜሪካ ወደ አዲስ ምዕራፍ እየገባች መሆኗን ከገለጸች ከቀናት በኋላ ነው፤ በኢራን እና ከኢራን ጋር የንግድ ግንኙነት ያላቸው አገራት ላይ ያነጣጠረ ሰፊ የኢኮኖሚ ማዕቀብ ይፋ አድርጋለች።

    የአሜሪካ ዓላማ ኢራንን ወደ ድርድር ማምጣት እና በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ የምትፈጽማቸውን ጥቃቶች እንድታቆም ማስገደድ ነበር። ይህ ለዓለም ንግድ በጣም ወሳኝ የሆነው የመርከብ መተላለፊያ መስመር፣ አሜሪካ እና እስራኤል ግጭቱን ባለፈው የካቲት ወር ከጀመሩ ወዲህ በተግባር ተዘግቶ ቆይቷል።

    ሁለቱ ወገኖች በሰኔ ወር የፈረሙት እና በ60 ቀናት ውስጥ ወደ ቋሚ የተኩስ አቁም እና የሰላም ስምምነት ሊያመራ የነበረው የመግባቢያ ሰነድ ጊዜው አልፏል።

    ግጭቱ ወደ ሰባተኛ ወሩ ሲገባ፣ በቀጣይ እንዴት ሊቀጥል ይችላል የሚለውን በተመለከተ ሦስት ባለሙያዎች አስተያየት ሰጥተዋል። ዝርዝሩን እዚህ ያንብቡ የአሜሪካ እና የኢራን ጦርነት እንዴት ሊቆም ይችላል? የሦስት ተንታኞች ዕይታ

  4. የየመን ሁቲዎች ወደ ቀይ ባሕር የሚያስገባውን ባብ ኤል መንደብን ለመቆጣጠር መቃረባቸው ተዘገበ

    የኢራን አጋር የሆኑት የየመን ሁቲ አማፂያን ወደ ቀይ ባሕር ለመግባት ወሳኝ በሆነው የባብ ኤል መንደብ መተላለፊያ ወሽመጥ ላይ ወሳኝ ተጽእኖ ለማሳረፍ እየተቃረቡ መሆናቸው ተዘገበ።

    በዓለም ላይ ከሚገኙ እጅግ አስፈላጊ የንግድ መርከቦች መተላለፊያ መስመሮች መካከል አንዱ የሆነውን የባሕር ላይ መተላለፊያ ለመቆጣጠር መቃረባቸውን ሮይተርስ የዜና ወኪል አራት የየመን መንግሥት ወታደራዊ ምንጮችን ጠቅሶ ዘግቧል።

    ሁቲዎች በየመን ውስጥ በሳዑዲ አረቢያ ከሚመራው ጥምር ጦር እና ድጋፍ ከሚያገኙ ኃይሎች ጋር እያካሄዱ ያለው ውጊያም ወደ ሙሉ ጦርነት እንደገና የመመለስ አዝማሚያ እያሳየ ነው።

    ምንጮቹ እንዳሉት፣ ሁቲዎች ከባብ ኤል መንዳብ ወሽመጥ ጋር በቀጥታ የሚገናኙ የየመን የባሕር ዳርቻ ከተሞችን ሙሉ በሙሉ ለመቆጣጠር እየተቃረቡ ሲሆን፣ መላውን የየመን የቀይ ባሕር ዳርቻዎች ለመያዝ ወታደራዊ ግፊት እያደረጉ ነው።

    ባለፉት ቀናት ዓለም አቀፍ ዕውቅና ባለው የየመን መንግሥት ውስጥ ያሉ በሳዑዲ አጋሮች እና በሁቲዎቹ መካከል የሚካሄደው ውጊያ ተባብሷል።

    ይህም በኢራን ግጭት ውስጥ ሁለተኛ የጦርነት ግንባር ሲሆን፣ በዓለም አቀፍ የነዳጅ ምንጮች አቅርቦት ላይ ስጋት እየፈጠረ ነው።

    የባብ ኤል መንዳብ ወሽመጥ ሰርጥ በቀይ ባሕር ደቡባዊ ጫፍ ላይ የሚገኝ ከሕንድ ውቅያኖስ ወደ ቀይ ባሕር መግቢያ እና መውጫ ነው። ይህ ቦታ በአረብ ባሕረ ገብ ምድር ላይ የምትገኘውን የመንን ከጅቡቲ እና ከኤርትራ ጋር የሚለይ ነው።

    አሁን ወሽመጡን ለመቆጣጠር ጥረት እያደረጉ ያሉት ሁቲዎች ሰሜናዊ የየመንን አብዛኛውን ክፍል እንዲሁም በርካታ ሕዝብ የሚኖርባቸውን የአገሪቱን ክፍል የሚያስተዳድሩት ሁቲዎች ባብ ኤል መንደብን መያዝ ከቻሉ በቀታናው ከፍተኛ ተጽእኖ ማሳደር ይችላሉ።

    ወሽመጡ ከፍተኛ ነዳጅ እና ጋዝ ከሚመረትበት የባሕረ ሰላጤው አገራት የሚመጣ ድፍድፍ ነዳጅ ወደ ሱዌዝ ቦይ ለመድረስ ወደ ቀይ ባሕር የሚያስገባ በር ነው። እንዲሁም ወደ እስያ አገራት የሚያመሩ የተለያዩ ምርቶች እና ሸቀጦች የጫኑ ግዙፍ መርከቦችም ይተላለፉበታል።

    የየመን ሁቲ ታጣቂዎች ጥረታቸው ተሳክቶ ባብ ኤል መንደብን ለመቆጣጠር ወሳኝ የሆኑ ግዛቶችን መያዝ ከቻሉ የሚፈጥሩት ተጽእኖ ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥን በመዝጋት በዓለም የነዳጅ አቅርቦት ላይ ከፈጠረችው ቀውስ ቀጥሎ ሌላ አሳሳቢ ሁኔታን ሊፈጥሩ ይችላሉ።

  5. ኢራን ለኒውክሌር ስምምነት “ስላልተገዛች” የፀጥታው ምክር ቤት ጉዳዩን እንዲመለከት ተጠየቀ

    የተባበሩት መንግሥታት የኒውክሌር ተቆጣጣሪ አካል፤ ኢራን ለስምምነት “አልተገዛችም” በሚል ጉዳዩን ወደ ፀጥታው ምክር ቤት ወሰደ።

    የኒውክሌር ጦር መሣሪያ ግንባታን ለመግታት እና ኒውክሌርን ለሰላማዊ ዓላማ ለማዋል የወጣውን ዓለም አቀፍ መመሪያ ኢራን እንዳላከበረች ተገልጿል።

    የኢራን ጉዳይ ወደ ፀጥታው ምክር ቤት ሲመራ በ20 ዓመታት ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው።

    ዓለም አቀፉ የአውቶሚክ ኢነርጂ ተቋም በቪየና ባደረገው ጉባዔ ላይ ነው ውሳኔውን ያስተላለፈው።

    ኢራን ያላትን የበለፀገ ዩራኒየም መጠን ጨምሮ ስለ ኒውክሌር መረጃ እንዳልሰጠች እንዲሁም የኒውክሌር ተቋማቷን ለዓለም አቀፍ መርማሪዎች ክፍት እንዳላደረገች ተገልጿል።

    ቴህራን ዓለም አቀፉ የአቶሚክ ኢነርጂ ተቋም ያስተላለፈውን ውሳኔ ኮንናለች። አሜሪካ እና እስራኤል በፈጸሙባት ጥቃት ሳቢያ የኒውክሌር ማዕከሎቿ ለጉብኝት ክፍት መሆን እንዳልቻሉም ገልጻለች።

    በፀጥታው ምክር ቤት የኢራን አጋር የሆኑት ቻይና እና ሩሲያ ድምጽን በድምጽ የመሻር ሥልጣን ስላላቸው ቴህራን ላይ አዲስ ማዕቀብ የሚጣልበት ዕድል ጠባብ ነው።

    የዓለም አቀፉ የአውቶሚክ ኢነርጂ ተቋም ምክረ ሐሳብ የቀረበው በዩናይትድ ኪንግደም፣ በፈረንሳይ፣ በጀርመን እና በአሜሪካ ነው። ሐሳቡን 23 አገራት ሲደግፉት፤ ስምንት አገራት ደግሞ ድምጸ ተዓቅቦ አድርገዋል።

  6. ኢራን በአሜሪካ የአየር ኃይል ሰፈር ላይ በፈጸመችው ጥቃት በርካታ የጦር አውሮፕላኖች መጎዳታቸው ተዘገበ

    አሜሪካ በመርከቦቿ ላይ ከባድ ጥቃት መፈጸሟን ተከትሎ ኢራን ዮርዳኖስ ውስጥ በሚገኝ የአሜሪካ የአየር ኃይል ሰፈር ላይ በወሰደችው የአጸፋ እርምጃ በርካታ የጦር አውሮፕላኖች መጎዳታቸው ተዘገበ።

    የአሜሪካው ሲቢኤስ ኒውስ ከክስተቱ ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት ያላቸውን ምንጮች ጠቅሶ እንደዘገበው፣ ኢራን ረቡዕ ዕኩለ ሌሊት ላይ በዮርዳኖስ የሚገኘው የሙዋፋቅ ሶልቲ የአሜሪካ አየር ኃይል ሰፈር ላይ በፈጸመችው የሚሳዔል ጥቃት በርካታ የአሜሪካ ጦር አውሮፕላኖች ጉዳት ደርሶባቸዋል።

    በጉዳቱ ብርቱነት ምክንያት ስማቸው እንዳይጠቀስ የጠየቁት ምንጮች፣ ወደ ስምንት የሚጠጉ ኤፍ-15 ተዋጊ አውሮፕላኖች ቀላል ጉዳት እንደደረሰባቸው እና ከጥገና በኋላ ወደ ሥራ መመለሳቸውን ተናግረዋል።

    ምንጮቹ እንደገለጹት፣ አንድ አጥቂ አውሮፕላን በሚሳዔል ከተመታ በኋላ አንደኛው ክንፉ ከባድ ጉዳት ደርሶበታል።

    ለቴሌቪዥን ጣቢያው መረጃ የሰጡ የስለላ ምንጮች እንደተናገሩት በጥቃቱ በንብረት ላይ ጉዳት ቢደርስም የተገደለ አንድም የአሜሪካ ወታደር የለም ብለዋል።

    ይህ ጥቃት፣ አሜሪካ በአንድ የጦር መርከቧ ላይ ለተፈጸመ የኢራን ጥቃት ምላሽ በመስጠት አምስት የኢራን ነዳጅ ጫኝ መርከቦችን መምታቷን ካስታወቀች ከጥቂት ሰዓታት በኋላ የተፈጸመ ነው።

    በምላሹ የኢራን አብዮታዊ ዘብ ስምንት ነዳጅ ጫኝ መርከቦችን፣ ሁለት የአሜሪካ የጦር መርከቦችን እንዲሁም በዮርዳኖስ ያለውን የሙዋፋቅ ሶልቲ የአየር ኃይል ሰፈርን ዒላማ ማድረጋቸውን ገልጸዋል።

    በተጨማሪም በዮርዳኖስ የሚገኙ የአሜሪካ ኃይሎች የኢራንን ጥቃት ለመከላከል ከ30 በላይ የፓትሪዮት ሚሳዔሎችን እንደተኮሱ ተዘግቧል።

    ነገር ግን የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስቴር (ፔንታገን) በዮርዳኖስ ውስጥ በሚገኘው የአየር ኃይል ሰፈር በነበሩ አውሮፕላኖች ላይ ስለደረሰው ጉዳት እስካሁን ማረጋገጫም ሆነ ማስተባበያ አልሰጠም።

  7. ኅዳር ላይ ከሚካሄደው የአሜሪካ የአጋማሽ ዘመን ምርጫ በፊት የኢራን ጦርነት እንደማያከትም ትራምፕ ተናገሩ

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አገራቸው ኅዳር ላይ የአጋማሽ ዘመን ምርጫ ከማካሄዷ አስቀድሞ የኢራን ጦርነት ያከትማል ብለው እንደማያስቡ ተናገሩ። እስከዚያ ድረስ የነዳጅ ዋጋ ይቀንሳል ብለው እንደማያምኑም ፕሬዝዳንቱ ገልጸዋል።

    “ምርጫው ካለቀ በኋላ ወዲያውኑ ጦርነቱ ይቆማል ብዬ አስባለሁ። ምክንያቱም ከዚያ በላይ መቋቋም አይችሉም” ብለዋል።

    ፕሬዝዳንቱ የአጋማሽ ዘመን ምርጫ ከመካሄዱ አስቀድሞ በቴክሳስ የሚከናወነው የሪፐብሊካን ፓርቲ ጉባዔ ላይ ይገኛሉ።

    ምርጫው በአገሪቱ የመንግሥት መዋቅር ውስጥ ያለውን የኃይል ሚዛን ሊለውጥ ይችላል።

    ትራምፕ የኢራንን ጦርነት እንዲያቆሙ ከሪፐብሊካን ፓርቲያቸው ጫና በርትቶባቸዋል።

    ከሐምሌ ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ የነዳጅ ዋጋ በበርሜል 100 ዶላር ደርሷል።

    ትራምፕ “ከምርጫው በኋላ የነዳጅ ዋጋ ይቀንሳል” ብለዋል።

    ኢራን ምርጫው ላይ ጫና ለማሳደር “በጣም እየተጣጣረች” እንደሆነ የተናገሩት ፕሬዝዳንቱ፤ ዲሞክራቶች ሥልጣን ይዘው “የኒውክሌር ግንባታ የመቀጠል ዓላማ” እንዳላትም ገልጸዋል።

    ኢራን የኒውክሌር ጦር መሣሪያ የመገንባት ፍላጎት እንደሌላት በተደጋጋሚ አስታውቃለች።

  8. "ጦነርቱ እንዲቆም አሜሪካ በኒውክሌር እና በሚሳዔል ጉዳዮቼ ጣልቃ መግባት የለባትም" - ኢራን

    ከአሜሪካ ጋር የምታካሂደው ግጭት መልሶ እየተባባሰ ባለበት በአሁኑ ጊዜ የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ጦርነቱ እንዲቆም አሜሪካ በኢራን የኒውክሌር እና የሚሳዔል ፕሮግራሞች ላይ ጣልቃ መግባቷን ማቆም አለባት አለ።

    አብዮታዊ ዘቡ እንደገለጸው፣ ጦርነቱ እንዲቆም አሜሪካ በእስላማዊቷ ሪፐብሊክ ላይ የምታደርገውን ዛቻ ማቆም እና ከኢራን የቀረቡትን ቅድመ ሁኔታዎች፣ በተለይም ከኒውክሌር ፕሮግራሟ ጋር የተያያዙትን መቀበል ይገባታል።

    “ጠላት አሁን ያለው ሁኔታ እንዲያበቃ ከፈለገ፣ ጦርነቱን ሙሉ በሙሉ ማቆም እና በኢራን ላይ ማስፈራራት ከመፈጸም መቆጠብ አለበት” ሲሉ የአብዮታዊ ዘቡ ቃል አቀባይ ሆሴይን ሞሄቢ ተናግረዋል።

    ጨምረውም ጦርነቱ እንዲቆም እስራኤል ከሊባኖስ መውጣት እና በየመን ላይ የተጣለውን እገዳ ማንሳት ከኢራን ሌሎች ቅድመ ሁኔታዎች መካከል ይገኛሉ ብለዋል።

    ባለፈው ሰኔ በፓኪስታን አሸማጋይነት በኢራን እና በአሜሪካ መካከል በተደረሰው የመግባቢያ ስምምነት ላይ ኢራን በሁሉም የግጭት ግንባሮች ላይ ጦርነት እንዲቆም ጠይቃ ሊባኖስን በተለይ ጠቅሳለች ነበር፤ ነገር ግን አጋሯ የሆኑት ሁቲ ታጣቂዎች የሚቆጣጠሯት የመን ግን አልተካተተችም ነበር።

    የአብዮታዊ ዘቡ ቃል አቀባይ በተጨማሪም የታገዱ 24 ቢሊዮን ዶላር የኢራን ንብረቶች እንዲለቀቁም ጠይቀዋል።

    አሜሪካ “በኢራን የኒውክሌር እና የሚሳዔል መረሃ ግብሮች ላይ የምታደርገውን ማንኛውንም ጣልቃ ገብነት” ማቆም እንዳለባትም አጽንኦት ሰጥተው አሳስበዋል።

  9. ኤአይ የሰው ልጅን ሊያጠፋ የሚችልበት ዕድል ከ10 በመቶ በላይ ነው ተባለ

    በሚቀጥሉት 10 ዓመታት ውስጥ ኤአይ የሰው ልጅን ሙሉ በሙሉ ሊያጠፋ ይችላል የሚለው ዕድል ከ10 በመቶ በላይ ነው ሲል አንድ ከፍተኛ የሰው ሠራሽ አስተውሎት (ኤአይ) ደኅንነት ተመራማሪ አስጠነቀቀ።

    አንትሮፒክ የተባለው የሰው ሠራሽ አስተውሎት ተቋም ከፍተኛ የኤይአይ ደኅንነት ተመራማሪ ኢቫን ሁቢንገር በኤክስ ላይ ባወጣው ጽሑፍ፣ በሚቀጥሉት አሥር ዓመታት ውስጥ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ “ሁሉንም ሰዎች ሊገድል ይችላል” የሚለው ዕድል ከ10 በመቶ በላይ ነው ብሏል።

    ሁቢንገር አሁን ያሉት የአይአይ ሞዴሎች የሚፈጥሩት አደጋ “ዝቅተኛ” መሆኑን ቢገልጽም፣ ቴክኖሎጂው በቅርቡ ራሱን በራሱ ሊያሻሽል በሚችል ደረጃ ደርሶ ለሰው ልጅ ኅልውና አደጋ ሊፈጥር እንደሚችል ስጋት እንዳለው ገልጿል።

    ነገር ግን እነዚህ የኤይአይ ሥርዓቶች ወደፊት ተጠናክረው እንዴት የሰው ልጅን ሙሉ በሙሉ ሊያጠፉ እንደሚችሉ ዝርዝር ማብራሪያ አልሰጠም።

    ይሁን እንጂ የተመራማሪው ንግግር ኤኤይ ለሰው ልጅ የከፋ አደጋ እንደሚፈጥር ለዓመታት ሲሰጡ የነበሩ ማስጠንቀቂያዎች የበለጠ ከባድ እየሆኑ መምጣታቸውን ያሳያል። ውይይቱም “ኤአይ አደጋ ያስከትላል ወይ?” ከሚለው ወደ “አደጋው ምን ያህል ከባድ ነው?” ወደሚለው ተሸጋግሯል።

    “በቅርቡ እነዚህ ሥርዓቶች ከሰው በላይ ብልህ ይሆናሉ፤ ማናቸውንም ሥርዓቶችን ሊጠልፉ ይችላሉ፣ ማንኛውንም ዘርፍ በአንድ ሌሊት ሊቀይሩ ይችላሉ፣ እንዲሁም እውነተኛ ኃይል እና ሀብትን ሊቆጣጠሩ ይችላሉ” ብሏል።

    የኮምፒውተር ሳይንቲስት እና ለተባበሩት መንግሥታት በኤአይ ጉዳይ አማካሪ የሆነው ዴም ዌንዲ ሆል ለቢቢሲ እንደተናገረው፣ የሁቢንገር የማኅበራዊ ሚዲያ አስተያየት አስደንግጦታል።

    አማካሪው ሲናገሩ የሚሰነዘሩት አስተያየቶች በከፊል “የሕዝብ ግንኙነት ወይም የማርኬቲንግ ዘዴ” ሊሆኑ እንደሚችሉ ጠቁሟል፤ ምክንያቱም ተፎካካሪዎቹ የኤአይ ተቋማት ወደ አክሲዮን ገበያ ለመግባት እየተዘጋጁ መሆናቸው ነው።

    ከ10 ሚሊዮን በላይ ጊዜ ተመልካች ባገኘው የኤክስ ጽሁፉ ላይ ሁቢንገር፣ “ኤአይ ለሰው ልጅ ኅልውና አደጋ እንዳለው በእውነት እናምናለን” ብሏል።

    ኤአይ ለሰዎች ደኅንነት አስጊ ባልሆነ ሁኔታ እንዲሠራ ጥረት እየተደረገ ቢሆንም ብዙ ተመራማሪዎች እንደሚሉት ግን ጥረቶቹ እየተሳኩ አይደለም። ከጥቂት ወራት በፊት የኤአይ ሥርዓቶች ራሳቸው የሳይበር ጥቃቶችን እንደፈጸሙ ክስተቶች ተመዝግበዋል።

  10. በፋርስ ባሕረ ሰላጤ በርካታ መርከቦች መቃጠላቸው ተዘገበ

    በፋርስ ባሕረ ሰላጤ እና በሆርሙዝ የባሕረ ወሽጥ አካባቢ ባለፉት ቀናት በተፈጸሙ ጥቃቶች ምክንያት በርካታ መርከቦች በእሳት መቃጠላቸው እና ጉዳት እንደደረሰባቸው ተዘገበ።

    የዩናይትድ ኪንግደም ንግድ እንቅስቃሴ ባለሥልጣን እንዳመለከተው በተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ከሚገኘው ፖርት ራሺድ ወደብ በሰሜን ምዕራብ ርቀት ላይ መልኅቅ ጥሎ የነበረ አንድ መርከብ ወደ አንድ ጎኑ እየሰመጠ ሲሆን ይህም ውሃ ወደ መርከቡ እየገባ መሆኑን ያሳያል ተብሏል።

    ከዚህ በፊት መርከቡ በተወንጫፊ ዒላማ ተደርጎ ጥቃት እንደደረሰበት መዘገቡም ይታወሳል።

    የብሪታንያው የባሕር ንግድ እንቅስቃሴ ባለሥልጣን እንዳለው፣ ይህ ጉዳይ በሦስተኛ ወገን ሪፖርት ተደርጎ ቀርቧል።

    የመርከብ እንቅስቃሴን የሚቆጣጠር ሌላ የብሪታንያ ተቋምም በፋርስ ባሕረ ሰላጤ አካባቢ በርካታ መርከቦች በእሳት መቃጠላቸውን አስታውቋል።

    ይህ ሪፖርት የወጣው ኢራን በሆርሙዝ ወሽመጥን ለማቋረጥ ሲሞክሩ የነበሩ 20 መርከቦች ጥቃት እንደፈጸመች ካስታወቀች በኋላ ነው።

    የብሪታንያው ተቋም “በክልሉ ውስጥ በቀጠለው ወታደራዊ እንቅስቃሴ መካከል እነዚህ መርከቦች ዒላማ እንደተደረጉ ሪፖርቶች ያመለክታሉ” ብሏል።

    ከዚህ ቀደም ኢራን እና አሜሪካ አንዳቸው በሌላኛቸው መርከቦች ላይ ጉዳት ማድረሳቸውን ማስታወቃቸው ተዘግቧል።

    አሜሪካ በመርከቦቿ ላይ ለደረሰው የኢራን ጥቃት ምላሽ አምስት የኢራን ነዳጅ ጫኝ መርከቦችን መምታቷ እና “ማውደሟን” ገልጻለች።

    በሌላ በኩል የኢራን አብዮታዊ ዘብ በአጸፋው በፈጸመው የሚሳኤል ጥቃቶች ሁለት የአሜሪካ የጦር መርከቦችን እና ስምንት ነዳጅ ጫኝ መርከቦችን ዒላማ እንዳደረገ አስታውቋል።

  11. የነዳጅ ዋጋ ከሐምሌ ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ በበርሜል 100 ዶላር ደረሰ

    የአሜሪካ እና ኢራን ግጭት ተባብሶ በመቀጠሉ እንዲሁም የየመን ሁቲ አማጽያን በሳዑዲ አረቢያ ላይ በሚያደርሱት ጥቃት ምክንያት የነዳጅ ዋጋ ከሐምሌ ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ በበርሜል 100 ዶላር ደረሰ።

    የአሜሪካ ጦር አምስት የኢራን ነዳጅ ጫኝ መርከቦች ላይ ጥቃት ማድረሱን ማዕከላዊ ዕዙ (ሴንትኮም) አስታውቋል።

    ባለፉት ሁለት ቀናት ኢራን የአሜሪካ የጦር መርከቦችን ሁለት ጊዜ ዒላማ በማድረጓ የተሰጠ የአጸፋ ምላሽ ነው ብሏል።

    የዓለም አቀፍ ነዳጅ ዋጋ መለኪያ የሆነው ብሬንት ድፍድፍ ነዳጅ ከፍተኛ ዋጋ የተመዘገበው ሐምሌ መጨረሻ ላይ ነበር። በወቅቱ የኢራን እና አሜሪካ የተኩስ አቁም ስምምነት መክሸፉ ይታወሳል።

    ኢራን የምትደግፋቸው የየመን ሁቲ አማጽያን በሳዑዲ አረቢያ ነዳጅ ማምረቻ ተቋማት ላይ ጥቃት ማድረሳቸውን ቀጥለዋል።

    ትናንት ማክሰኞ በቀይ ባሕር ላይ ነዳጅ ጫኝ መርከቦችን ዒላማ አድርገዋል።

    ብሬንት ድፍድፍ ነዳጅ በበርሜል 99.90 ደርሶ ነበር። በመካከለኛው ምሥራቅ ያለው ግጭት ሲባባስ ግን ዋጋው አሻቅቧል።

    የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ እንዳለው ከኢራን አብዮታዊ ዘብ ጋር ትስስር ያላቸው አራት ነዳጅ ጫኝ መርከቦች በኦማን ባሕረ ሰላጤ ዒላማ ተደርገዋል። አንድ ሌላ መርከብ በኻርግ ደሴት አቅራቢያ ጥቃት ደርሶበታል።

    ኢራን ለደረሰባት ጥቃት በምላሹ በዮርዳኖስ የሚገኝ የአሜሪካ የጦር ሰፈር ላይ ድብደባ ፈጽማለች።

  12. የመብራት መጥፋትን በመቃወም አደባባይ የወጡ ጋምቢያውያን እንዲረጋጉ የአገሪቱ ፕሬዝዳንት ጠየቁ

    ጋምቢያውያን ለሁለት ቀናት የኤሌክትሪክ አቅርቦት በመቋረጡ ምክንያት ለተቃውሞ አደባባይ መውጣታቸውን ተከትሎ ፕሬዝዳንቱ ችግሩ እንደሚፈታ ተናግረዋል።

    ጋምቢያውያኑ የተራዘመ ያሉት የመብራት መጥፋትን በመቃወም ተቃውሟቸውን ሲገልጹ ፕሬዝዳንት አዳማ ባሮው ሕዝቡ “እንዲረጋጋ” አሳስበዋል።

    ፕሬዝዳንቱ መብራት እየጠፋ ያለው ጋምቢያ ውስጥ ብቻ ሳይሆን በሌሎችም የምዕራብ አፍሪካ አገራት ጭምር እንደሆነ ተናግረዋል።

    ሰኞ ምሽት በጋምቢያ መዲና ባንጁል እና በዙሪያዋ በሚገኙ ከተሞች የኤሌክትሪክ አቅርቦት መቋረጥን የሚቃወሙ ሰዎች ወደ ጎዳና ወጥተው ተቃውሞዎች ተቀስቅሰዋል።

    ነዋሪዎች እስከ 48 ሰዓት ድረስ መብራት እንደሚጠፋ ተናግረዋል።

    ፕሬዝዳንቱ “በጨለማ እና በሙቀት ተውጣችሁ ስትተኙ ብቻችሁን እንዳልሆናችሁ አስቡ” ብለዋል።

    በቀጣይ ወር የኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት እንደሚጨምርም ፕሬዝዳንቱ ቃል ገብተዋል።

    ጋምቢያ እንደ ጋና እና ሴኔጋል ካሉ ጎረቤት አገራት የኃይል አቅርቦት ታገኛለች።

    ከሰኔ ጀምሮ የመብራት መቆራረጥ በስፋት ተስተውሏል። በአገሪቱ አሁን ላይ ባለው ሞቃታማ የአየር ሁኔታ የኤሌክትሪክ አቅርቦት ፍላጎት ጨምሯል።

    ነዋሪዎች አደባባይ ወጥተው ጎማ በማቃጠል እና መንገድ በመዝጋት ቅሬታቸውን አሰምተዋል።

    ፖሊስ ተቃዋሚዎችን ለመበተን አስለቃሽ ጭስ ተጠቅሟል።

  13. በብሪታኒያ የአየር ትራፊክ መቆጣጠሪያዎች ላይ በተፈጠረ ችግር ከአንድ ሺህ በላይ በረራዎች ተሰረዙ

    በብሪታንያ የአየር ትራፊክ ቁጥጥር ሥርዓት ላይ ባጋጠመ ችግር ምክንያት በመቶዎች የሚቆጠሩ በረራዎች እንዲሰረዙ ካደረገ በኋላ፣ የበረራ መዘግየቶች ረቡዕም እንደሚቀጥሉ ተገለጸ።

    በዚህ ችግር የተነሳም በአስር ሺህዎች የሚቆጠሩ መንገደኞች የተጉላሉ ሲሆን፣ የበረራ ክትትል ድረ ገጽ ፍላይትራዳር24 እንደገለጸው በአየር ትራፊክ ቁጥጥር ላይ በተፈጠረ የቴክኒክ ችግር እስከ 1,000 የሚደርሱ በረራዎች ተሰርዘዋል።

    የብሪታንያ የትራንስፖርት ሚኒስትር ሃይዲ አሌክሳንደር ሮልፍን ዛሬ ረቡዕ ስለተፈጠረው ችግርና ምላሽ እና ማብራሪያ እንዲሰጡ የተጠየቁ ሲሆን፣ ሚኒስትሯ ለፓርላማ አባላት ችግሩ በሳይበር ጥቃት የተከሰተ እንዳልሆነ “በፍጹም እርግጠኝነት” ያስረዳሉ ተብሏል።

    በተፈጠረው ችግር ምክንያት በርካታ አውሮፕላኖች መነሳት ባለመቻላቸው የአየር ማረፊያዎች ሥራ ላይ ችግር ተፈጥሯል፤ ከሌሎች አገራት የሚነሱ በረራዎችም እንዲስተጓጎሉ ምክንያት ሆኗል።

    ችግሩ በመላው ዩናይትድ ኪንግደም እና ከዚያም በላይ ተስፋፍቶ ተሰምቷል፤ በአየርላንድ ያሉ አየር ማረፊያዎችም መስተጓጎል እንዳጋጠማቸው አስታውቀዋል። ኢዚጄት 200 በረራዎችን ሲሰርዝ፣ ብሪቲሽ ኤርዌይስ ደግሞ ከ100 በላይ በረራዎችን ሰርዟል።

    የትራንስፖርት ሚኒስትሯ ሃይዲ አሌክሳንደር “በረራዎች ሙሉ በሙሉ ወደ መደበኛ ሁኔታቸው ለመመለስ ጊዜ ይወስዳል፤ ስለዚህ መንገደኞች ከአየር መንገዶች የጉዞ መረጃቸውን እንዲያረጋግጡ እመክራለሁ” ብለዋል።

    በአውሮፓ በጣም ሥራ ከሚበዛባቸው አየር ማረፊያዎች አንዱ ከሆነው ሂትሮው አየር ማረፊያ የሚነሱ በረራዎች ለጊዜው ተቋርጠው ነበር። ከዚያ በኋላ እንቅስቃሴው ቢቀጥልም፣ ከሰዓት በኋላ ዳግም መስተጓጎል ተከስቷል።

    አውሮፕላኖች መነሳት ባለመቻላቸው ምክንያት ከሰዓት በኋላ ለሚደርሱ በረራዎች የሚሆን ቦታ በአየር ማረፊያው መጥፋቱ ተገልጿል። በዚህም ምክንያት ወደ ሂትሮው ይመጡ የነበሩ 13 በረራዎች ወደ ሌሎች በብሪታንያ እና በአውሮፓ የሚገኙ አየር ማረፊያዎች እንዲሄዱ ተደርጓል።

  14. አሜሪካ የኢራን ነዳጅ ጫኝ መርከቦችን ስትመታ፤ ቴህራን በዮርዳኖስ የጦር ሰፈር ላይ ጥቃት አደረሰች

    የአሜሪካ ጦር አምስት የኢራን ነዳጅ ጫኝ መርከቦች ላይ ጥቃት ማድረሱን ማዕከላዊ ዕዙ አስታወቀ።

    የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም) እንዳለው ባለፉት ሁለት ቀናት ኢራን የአሜሪካ የጦር መርከቦችን ሁለት ጊዜ ዒላማ በማድረጓ የአጸፋ ምላሽ ተሰጥቷል።

    ከኢራን አብዮታዊ ዘብ ጋር ትስስር ያላቸው አራት ነዳጅ ጫኝ መርከቦች በኦማን ባሕረ ሰላጤ ዒላማ ተደርገዋል። አንድ ሌላ መርከብ በኻርግ ደሴት አቅራቢያ ጥቃት ደርሶበታል።

    ኢራን ለደረሰባት ጥቃት በምላሹ በዮርዳኖስ የሚገኝ የአሜሪካ የጦር ሰፈር ላይ ድብደባ ፈጽማለች።

    ኢራን ከተኮሰቻቸው 20 ሚሳዔሎች 18 የሚሆኑትን ማክሸፏን ዮርዳኖስ አስታውቃለች።

    ኢራን እና አሜሪካ የሚያደርጉት የጥቃት ልውውጥ ባለፈው ሳምንት ተባብሶ ቀጥሏል።

    አሜሪካ እና እስራኤል ኢራን ላይ ጥቃት ከከፈቱ ስድስት ወራት ተቆጥረዋል። በቀጠለው ግጭት ሳቢያም የነዳጅ ዋጋ እያሻቀበ ይገኛል።

  15. እስራኤል የዩኬን ውሳኔ በመቃወም የአጸፋ እርምጃ ወሰደች

    ዩናይትድ ኪንግድም በዌስት ባንክ የሚካሄዱ ሕገ ወጥ የእስራኤል ሰፈራዎችን በመቃወም ከሰፈራዎቹ በሚወጡ ምርቶች ላይ እገዳ መጣሏን ተከትሎ እስራኤል የአጸፋ እርምጃ በዩኬ ላይ መውሰዷን አስታወቀች።

    የዩናይትድ ኪንደግም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኤድ ሚሊባንድ በአገራቸው ምክር ቤት ቀርበው ይፋ እንዳደረጉት ከሕገ ወጥ የሰፈራ አካባቢዎች በሚወጡ ምርቶች ላይ እገዳ መጣሉን እና ተጨማሪ የቅጣት እርምጃዎች መወሰዳቸውን ገልጸዋል።

    ይህንንም ተከትሎ በሰዓታት ውስጥ የእስራኤል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ሳአር ለዩኬ እርምጃ አጸፋ አራት ውሳኔዎችን ማሳለፋቸውን ይፋ አድርገዋል።

    • በዚህም በኢየሩሳሌም የሚገኘው የብሪታኒያ ቆንስላ ጽህፈት ቤት እንዲዘጋ
    • በደቡባዊ እስራኤል በሚገኘው የጋዛ ዓለም አቀፍ ድጋፍ ማዕከል ውስጥ የሚገኙ የብሪታኒያ ተወካዮች ለቀው እንዲወጡ
    • በዌስት ባንክ የፍልስጤም አስተደዳር ኃይሎችን የማሠልጠን የብሪታኒያ ተሳትፎ እንዲቋረጥ
    • 12 የብሪታኒያ እንደራሴዎች እና በፀረ እስአኤል እንቅስቃሴ ውስጥ የተሳተፉ ሌሎች የብሪታኒያ ዜጎች ወደ እስራኤል እንዳይገቡ የሚከለክል ውሳኔ ተላልፏል።

    የእስአኤል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጨምረውም “ከእስራኤል በተቃራኒ እርምጃ በሚወስዱ ወይም በወሰዱ” እንዲሁም የዩኬ ዓይነት ውሳኔን በሚያሳልፉ ሌሎች አገራት ላይም አገራቸው የአጸፋ እርምጃ እንደምትወስድ ገልጸዋል።

    "እኛን ለሚጎዱ ለሁሉም ይህ መልዕክት ግልጽ ነው፤ በእስራኤል ላይ ጎጂ እርምጃ የሚወስድ ማንም ወገን በቀጣናው ያለውን ተጽእኖ እና ተቀባይነት ያጣል” ሲሉ ሚኒስትሩ አስጠንቅቀዋል።

  16. ዩኬ በእስራኤል ሰፈራዎች ላይ ማዕቀብ በመጣል፣ ሰፋሪዎችን ‘በዘር ማጽዳት’ ከሰሰች

    የዩናይትድ ኪንግድም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኤድ ሚሊባንድ አገራቸው ሕገወጥ ከሆኑት የምዕራብ ዳርቻ (ዌስት ባንክ) የእስራኤል ሰፈራዎች በሚመጡ ምርቶች ላይ እገዳ መጣሏን እና ተጨማሪ የቅጣት እርምጃዎችን መውሰዷን አስታወቁ።

    ሚሊባንድ በዩናይትድ ኪንግደም (ዩኬ) ፓርላማ የታችኛው ምክር ቤት ቀርበው እንደገለጹት ከእስራኤል ወደ አገሪቱ በሚገቡ ምርቶች ላይ የተጣለውን እገዳ ይፋ በደረጉበት ጊዜ “የብሪታንያ ሕዝብ በመደብሮቻችን ውስጥ [ከእስራኤል] ሰፈራዎች የሚመጡ ምርቶችን በመቀበል ወረራውን እንድንደግፍ አይፈልግም” ብለዋል።

    በተጨማሪም “ሁሉን አቀፍ የማዕቀብ ሥርዓት” እንደሚዘረጋ ገልጸው፣ በውስጡም “ተገቢ የሃይማኖት ልዩ ፈቃዶች” እንደሚካተቱ ተናግረዋል።

    ሕገ ወጥ ሰፈራዎችን የሚያመቻቹ ወይም የሚደግፉ ግለሰቦችን በመለየት “የዩኬ የማዕቀብ ቅጣት ተግባራዊ ይደረግባቸዋል” ብለዋል።

    መንግሥታቸው በምዕራብ ዳርቻ አካባቢዎች የዘር ማጽዳት እየተፈጸመ እንደሆነ እንደሚስማማ ገልጸው፣ “ሰፋሪ ሽብርተኞች” ፍልስጤማውያንን ከመሬታቸው እያፈናቀሉ መሆኑን ተናግረዋል። እንዲሁም “በአብዛኛው የእስራኤል መንግሥት ይህንን ድርጊት እንዳላየ ያልፈዋል” ብለዋል።

    ጨምረውም መንግሥታቸው የእስራኤል የምዕራብ ዳርቻ ወረራ “ሕገ-ወጥ” ነው የሚል አቋም እንዳለውም ተናግረዋል።

    “የብሪታንያ መንግሥት ይፋዊ አቋም እስራኤል ቁጥጥሯን በማጠናከር፣ ቋሚ የሉዓላዊነት ግዛት ለማስፋፋት ያላት ፍላጎት እና በሕገ ወጥ ሰፈራዎች አማካይነት በምታራምደው የመስፋፋት አጀንዳ ምክንያት ወረራው ሕገወጥ ነው” ሲሉ ገልጸዋል።

    በተጨማሪም በብሪታንያ ውስጥ ሕገወጥ የምዕራብ ዳርቻ ሰፈራዎችን ማስተዋወቅ እንደሚከለከል አስታውቀዋል።

    ሚኒስትሩ እንዳሉት ይህ ይፋ የተደረገው “ማዕቀብ ዒላማ የሚያደርገው እስራኤልን ሳይሆን፣ ሕገወጥ ሰፈራዎችን እና የሰፈራ መስፋፋትን ነው።”

    ሚሊባንድ በተጨማሪ በፍልስጤም ማኅበረሰቦች ላይ ጥቃትን የደገፉ ወይም ያነሳሱ “ጽንፈኛ ሰፋሪዎች” ላይ አዳዲስ ቅጣቶች እየተጣሉ መሆናቸውን ገልጸዋል።

    “እንዲሁም ነባሩን ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብቶች አሠራርን በማጠናከር የሰፈራዎችን መስፋፋት በተለይም ከኢየሩሳሌም በስተምሥራቅ የታቀደውን የሰፈር ልማት ለመከላከል እና ለመግታት ፈጣን እርምጃ ይፋ እናደርጋለን” ብለዋል።

  17. በዓለም ከፍተኛው ተከፋይ የሆኑት መሪ 1 ሚሊዮን ዶላር ደመወዝ ሊጨመርላቸው ነው

    የሲንጋፖር ጠቅላይ ሚኒስትር እና ሌሎችም ሚኒስትሮች ደመወዝ ሊጨመርላቸው እንደሆነ ተገለጸ።

    የሲንጋፖር ጠቅላይ ሚኒስትር ሎውረንስ ዎንግ በዓለም ከፍተኛው ክፍያ የሚሰጣቸው መሪ ናቸው። ደመወዛቸው በዓመት በ1.1 ሚሊዮን ዶላር እንደሚጨምርም ተገልጿል።

    የሚደረግላቸውን የደመወዝ ጭማሪ በቀጣይ አምስት ዓመታት ውስጥ ለእርዳታ እንደሚሰጡ ገልጸዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንዳሉት የሚኒስትሮችን ደመወዝ መጨመር ያስፈለገው ችሎታ ያላቸው ባለሥልጣናትን ወደ ኃላፊነት ለመሳብ ነው።

    ከዚህ ቀደም የሲንጋፖር መንግሥት ለባለሥልጣናት ከፍተኛ ደመወዝ መስጠት ሙስናን እንደሚያስወግድ አስታውቋል።

    የደመወዝ ጭማሪው ትችት ገጥሞታል። በተለይም ከሥራ ደኅንነት እና ከኑሮ ውድነት አንጻር ትችቶች እየተሰሙ ነው።

    የሲንጋፖር ጠቅላይ ሚኒስትር የደመወዝ ጭማሪ ሳይደረግላቸውም በፊት በዓለም ላይ ከፍተኛ ክፍያ የሚያገኙ የፖለቲካ መሪ ናቸው።

    አሁን ላይ ዓመታዊ ደመወዛቸው 2.2 ሚሊዮን የሲንጋፖር ዶላር ሲሆን በተደረገላቸው ጭማሪ ደመወዛቸው 60% በመቶ አድጎ 3.6 ሚሊዮን የሲንጋፖር ዶላር (2.8 ሚሊዮን ዶላር) ደርሷል።

    ከሲንጋፖር ቀጥሎ ከፍተኛ ደመወዝ የሚከፈለው ለሆንግ ኮንግ ዋና መሪ ጆን ሊ ነው። ደመወዛቸው 719,000 ዶላር ይደርሳል። በሦስተኛ ደረጃ የስዊትዘርላንድ ፕሬዝዳንት ጋይ ፓርሚሊን ሲሆኑ 606,000 ዶላር ያገኛሉ።

    የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ዓመታዊ ደመወዝ 400,000፣ የዩናይትድ ኪንግደም ጠቅላይ ሚኒስትር አንዲ ቡርንሀም ደመወዝ ደግሞ 230,000 ዶላር ነው።

  18. የየመን ሁቲ ታጣቂዎች በፈጸሟቸው ጥቃቶች ሳዑዲ ውስጥ 73 ሰዎች መጎዳታቸው ተገለጸ

    በየመን የሚገኘው በሳዑዲ አረቢያ የሚመራ ጥምር ጦር፣ በኢራን የሚደገፈው የየመን ታጣቂ ቡድን ሁቲ ተዋጊዎች በሳዑዲ ላይ በፈጸሙት ጥቃቶች ቢያንስ 73 ሰዎች መጎዳታቸውን አስታወቀ።

    ጥቃቶቹ መቼ እንደተፈጸሙ በግልጽ ባይነገርም የጥምረቱ ጦር ለእነዚህ የሁቲ ታጣቂዎች ጥቃቶች ጠንካራ ምላሽ እንደሚሰጥ ገልጿል።

    በየመን በርካታ ሕዝብ የሚኖርባቸውን አካባቢዎችን እንዲሁም የአገሪቱን ሰሜናዊ አብዛኛውን ከፍል የሚቆጣጠሩት ሁቲዎች፣ ሐምሌ ወር በሳዑዲ ላይ የባሕር ላይ እንቅስቃሴ እገዳ መጣላቸውን ካስታወቁ በኋላ ጥቃቶችን ሲፈጽሙባት ቆይተዋል፤ በቀይ ባሕር ላይ የሚንቀሳቀሱ መርከቦቿንም ዒላማ አድርገዋል።

    በየመን በሳዑዲ የሚመራው ወታደራዊ ጥምረት ቃል አቀባይ ኮሎኔል ቱርኪ አል ማሊኪ በቅርቡ የተባባሰውን ግጭት “አደገኛ” ሲሉ ገልጸው፣ ሁቲዎቹ በዓለም ትልቋ የነዳጅ ላኪ እና በኦፔክ ውስጥ ተፅእኖ ፈጣሪ የሆነችውን የሳዑዲ አረቢያን ሲቪል እና ኢኮኖሚያዊ ተቋማትን ዒላማ እንዳደረጉ ገልጸዋል።

    ሁቲዎቹ በሳዑዲ ላይ በፈጸሟቸው ጥቃቶች ጂዛን እና ናጅራንን ጨምሮ በተለያዩ ከተሞች ያሉ ዒላማዎችን ማጥቃታቸው ተዘግቧል።

    ፋይናንሻል ታይምስ እንደዘገበው፣ በጂዛን የሚገኙ የአራምኮ የነዳጅ ተቋማት በአዲስ ጥቃት ዒላማ የተደረጉ ሲሆን፣ የደረሰው ጉዳት ምን ያህል እንደሆነ እየተገመገመ ነው። አራምኮ በጉዳዩ ላይ እስካሁን አስተያየት አልሰጠም።

    የሳዑዲ ኢነርጂ ሚኒስቴር እንዳስታወቀው በሁቲዎች የተፈጸሙት ጥቃቶች "በሰላማዊ ሰዎች ላይ የተለያየ መጠን ያለው ጉዳት" ማድረሳቸውን እና ጥቃቶቹ ባስነሱት የእሳት ቃጠሎም "በበርካታ ስፍራዎች ላይ ሥራዎች እንዲቋረጡ" ምክንያት ሆኗል ብሏል።

    የሳዑዲ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሁቲዎች የፈጸሙትን እና "በይ ባሕር ላይ የንግድ መርከቦችን ዒላማ በማድረግ" የቀጠሉትን ጥቃቶች አውግዟል። ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብም ተገቢውን የተባበሩት መንግሥታት የፀጥታው ምክር ቤት ውሳኔዎችን ተግባራዊ በማድረግ ኃላፊነቱን እንዲወጣ ጠይቋል።

  19. ትራምፕ የካናዳውን አውሮፕላን አምራች የአሜሪካ ገበያ ለማቆም ዛቱ

    የካናዳው አውሮፕላን አምራች ቦምባርዲየር ተቋሙን ወደ አሜሪካ ካላዘዋወረ በስተቀር በአሜሪካ ምርቶቹን መሸጥ እንደማይችል ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አስጠነቀቁ።

    “ከዚህ በኋላ ቦምባርዲየር በአሜሪካ አይሸጥም። ገበያችንን ከፈለጉ እዚህ መጥተው ማምረት ይችላሉ። አሜሪካ ላይ መንጠልጠል አቁሙ” ሲሉ በትሩዝ ሶሻል ማኅበራዊ ሚዲያቸው ጽፈዋል።

    በአሜሪካ እና ካናዳ መካከል ያለው የንግድ ጦርነት እየተባባሰ መጥቷል።

    ትራምፕ አውሮፕላን አምራቹን እንደሚያግዱ የገለጹት ካናዳ በዋሽንግተን ለተጣለባት ታሪፍ የአጸፋ ታሪፍ ለመጣል ሰዓታት ሲቀራት ነው።

    ካናዳ በአሜሪካ ምርቶች ላይ 20 በሊዮን ዶላር የሚያወጣ ታሪፍ ለመጣል አቅዳለች።

    አውሮፕላን አምራቹ ባወጣው መግለጫ በሺህዎች የሚቆጠሩ አሜሪካውያን ሠራተኞች እንደቀጠረ አስታውቋል። ከአሜሪካ ተቋማት ጋር ላለው ትስስር ዋጋ እንደሚሰጥም ጠቅሷል።

    ትራምፕ አውሮፕላን አምራቹን በምን መንገድ ከአሜሪካ ገበያ እንደሚያግዱ ግልጽ አይደለም።

    መቀመጫው በካናዳ ሞንትሪያል ቢሆንም በአሜሪካ ካንዛስ ግዛት ፋብሪካ አለው።

    በዚህ ፋብሪካ 3,500 አሜሪካውያን ሠራተኞች ያሉት ሲሆን፤ ወታደራዊ አውሮፕላኖች ያመርታል።

    በቴክሳስ፣ አሪዞና፣ ፍሎሪዳ፣ ኮነትኬት፣ ኤልኖይስ፣ ዳላዌር፣ ካሊፎርንያ፣ ዲሲ እና ኒው ጀርሲም ይሠራል።

    ቢቢሲ ከካናዳ ጠቅላይ ሚኒስትር ማርክ ካርኒ ቢሮ ምላሽ ጠይቋል።

  20. ኢራን የአሜሪካን የጦር መርከቦች ዒላማ የማድረግ አቅም እንዳላት ገለጸች

    ኢራን የአሜሪካን የጦር መርከቦች ዒላማ የማድረግ አቅም እንዳላት የአገሪቱ ተጠባባቂ መከላከያ ሚኒስትር ማጅድ ኢብንኢረዛ አስታወቁ።

    ባለፉት ጥቂት ቀናት በፋርስ ባሕረ ሰላጤ ላይ ሁለት የአሜሪካ የጦር መርከቦች ላይ ጥቃት መፈጸሙን የኢራን ባለሥልጣናት ተናግረዋል።

    ኢራን በጦር መርከቦቹ ላይ ጥቃት ያደረሰችው ፀረ መርከብ አውዳሚ ሚሳዔል በመጠቀም መሆኑን አስታውቃለች።

    የኢራን ሉዓላዊ ብሔራዊ ፀጥታ ምክር ቤት ጸሐፊ ሞሼን ረዚይ እንዳሉት ባለፉት 48 ሰዓታት የኢራን ጦር “ለመጀመሪያ ጊዜ የአሜሪካ የጦር መርኮች ላይ የኢራን ፀረ መርከብ ሚሳዔል ሞክራለች”።

    “ይህ ሚሳዔል ለአሜሪካውያን ገሀነም ሆኖባቸው ሸሽተዋል” ብለዋል።

    የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም) ለኢራን ቀጥተኛ ምላሽ አልሰጠም።

    ሆኖም ትናንት ባወጣው ጽሑፍ “ለአብዮታዊ ዘቡ የሚተላለፈው መልዕክት ግልጽ ነው። ሁለት መርከቦቻችን ላይ ከተሶሳችሁ፣ ሦስት መርከቦቻችሁን እናወድማለን በምጣኔ ሃብትም የላቀ ዋጋ እናስከፍላችኋለን” ብሏል።

    ማዕከላዊ ዕዙ “የአሜሪካ ጦር ከመከላከል ወደኋላ አንልም። አስፈላጊ ከሆነ የኢራንን ውስን እና ስሱ የነዳጅ ታንከር እናወድማለን” ሲልም አክሏል።