ቀጥታ, ፕሬዝዳንት ትራምፕ የአሜሪካ ተደራዳሪዎች ከኢራን ጋር ስምምነት ለመፈጸም "እንዳይጣደፉ" አሳሰቡ

አሜሪካ እና ኢራን ጦርነቱን ለመቋጨት የሚያደርጉት ድርድር ወደ ማጠናቀቂያው እንደተቃረበ መነገሩን ተከትሎ፤ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ተደራዳሪዎቻቸው “በጥድፊያ" ከኢራን ጋር "ስምምነት እንዳይፈጽሙ” አዘዙ። በሁለቱ አገራት ንግግር እየተደረገበት ያለው የስምምነት ዕቅድ ከያዛቸው ነጥቦች መከካከል፤ የተኩስ አቁሙን ለ60 ቀናት ማራዘም፣ የሆርሙዝ ወሽመጥን በድጋሚ መክፈት እንዲሁም የኢራንን የኒውክሌር ፕሮግራም በተመለከተ ተጨማሪ ድርድር ማካሄድ የሚሉት ይገኙበታል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ሩቢዮ ከኢራን ጋር የሚደረገው ንግግር የማይሳካ ከሆነ አሜሪካ “ሌላ አማራጭ ትፈልጋለች” አሉ

    የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማርኮ ሩቢዮ ሰኞ ዕለት አገራቸው ከኢራን ጋር ጥሩ ስምምነት ታደርጋለች ወይም “በሌላ መንገድ” ትፈታዋለች ሲሉ ተናገሩ።

    በሕንድ የሚገኙት ሩቢዮ ሌሎች “አማራጮችን” ከመፈለግ በፊት ለዲፕሎማሲ ያለውን ዕድል ሁሉ መስጠት አስፈላጊ መሆኑን ለጋዜጠኞች ተናግረዋል።

    ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ እሁድ ዕለት ተወካዮቻቸው ከኢራን ጋር ስምምነት ለማድረግ እንዳይጣደፉ አሳስበዋል።

    ሩቢዮ “ሆርሙዝን ለመክፈት የሚያስችል ተጨባጭ የሆነ ስምምነት ጠረጴዛው ላይ አለ። ወሽመጡን ክፈቱ፤ ተጨባጭ፣ እውነተኛ በጊዜ የተገደበ ድርድር ወደ ማድረግ ግቡ፤ እናም ተስፋ አለኝ እናሳካዋለን” ብለዋል።

    እሁድ ዕለት ፕሬዚዳንት ትራምፕ በትሩዝ ሶሻል ገጻቸው ላይ አሜሪካ በኢራን ወደቦች ላይ የጣለችው ዕገዳ “ከስምምነት ላይ እስክንደርስ፣ ስምምነቱ እስኪጸድቅ እና እስኪፈረም ድረስ በሙሉ ኃይል ተግባራዊነቱ ይቀጥላል” ብለዋል።

    አክለውም “ሁለቱም አካላት ጊዜ መውሰድ እና የሚገባ ነገር ላይ መድረስ አለባቸው” ሲሉ ጽፈዋል።

    የኢራን መንግሥት በትራምፕ ሆነ በሩቢዮ አስተያየቶች ላይ አስተያየቱን አልሰጠም።

    ታስኒም የዜና ወኪል ግን አሜሪካ የስምምነቱ ወሳኝ ነጥቦችን እያስተጓጎለች ነው በማለት እንዳይንቀሳቀሱ የታገዱ ፈንዶች እንዲለቀቁ ጠይቋል።

    የኢራን ፓርላማ ቃል አቀባይ ኢብራሂም ሬዛይ በበኩላቸው በጦርነቱ ወቅት “ዓይን ላጠፋ ዓይን” የሚል መርህ ሲከተሉ እንደነበር ገልጸው፤ በዲፕሎማሲ አለመግባባት ወቅት ደግሞ “ለተግባር ተግባራዊ ምላሽ መስጠት” የሚል መሆኑን ተናግረዋል።

    በኤክስ ገጻቸው ላይ ኢራን በጫናዎች ወይንም ማስፈራሪያዎች አትንበረከክም ያሉት ቃል አቀባዩ፤ አሜሪካ ስምምነት ላይ መድረስ የምትፈልግ ከሆነ መደራደር አለባት ነገር ግን ነዳጅ በ6 ዶላር ማግኘት የምትፈልግ ከሆነ ማስመሰሏን ትቀጥል ሲሉ ጽፈዋል።

    በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የሰላም ስምምነት ይፈረማል የሚል ተስፋ እየጨመረ በመምጣቱ ሰኞ ዕለት የዓለም የነዳጅ ዋጋ በ6 በመቶ ገደማ ቀንሷል።

  2. የዩኬ መከላከያ ሚኒስቴርን ጭኖ የነበረ ጄት በሩሲያ ድንበር አቅራቢያ ሲግናሉ ተጠለፈ

    የዩናይትድ ኪንግደም ሮያል አየር ኃይል ጄት ባለፈው ሳምንት የአገሪቱን መከላከያ ሚኒስትርን ጭኖ በሩሲያ ድንበር አቅራቢያ በሚበርበት ሰዓት ሲግናሉ ተጠልፎ (Jamming) እንደነበር ተገልጸ።

    ክስተቱ ያጋጠመው መከላከያ ሚኒስትሩ ጆን ሃሌይ ኢስቶኒያ ውስጥ የሚገኙ የብሪታኒያ ወታደሮችን ጎብኝተው ሲመለሱ እንደነበር የዩኬው ታይምስ ጋዜጣ ዘግቧል።

    ጥቃቱ የአውሮፕላኑ አቅጣጫ ጠቋሚ ‘ጂፒኤስ’ እንዲያጠፋ የሚያደርግ በመሆኑ አብራሪዎቹ ሌላ የጉዞ ስርዓት ለመጠቀም ተገድደዋል። ሦስት ሰዓት በሚፈጀው በረራ ላይ ከተፈጸመው ጥቃት ጀርባ ሩሲያ እጇ እንዳለ ተገምቷል።

    ይህ ጠለፋ ያጋጠመው፤ ሁለት የሩሲያ የጦር አውሮፕላኖች ባለፈው ወር በጥቁር ባሕር በኩል ሲበር የነበረ የዩናይትድ ኪንግደም የስለላ አውሮፕላንን “በተደጋጋሚ እና በአደገኛ ሁኔታ” መጥለፋቸው ይፋ በተደረገ ማግሥት ነው።

    የአሁኑ ጥቃት የተፈጸመው የመከላከያ ሚኒስትሩን ዒላማ በማድረግ መሆኑ አልተረጋገጠም። ነገር ግን የአውሮፕላኑ ጉዞ በበረራ መከታተያ ድረ ገጾች ላይ ወጥቶ እንደነበር ጋዜጣው ዘግቧል።

    ቢቢሲ ስለ ጉዳዩ የመከላከያ ሚኒስቴርን አስተያየት ጠይቋል።

    መከላከያ ሚኒስትሩ በኢስቶኒያ ቆይታቸው በሩሲያ ድንበር አቅራቢያ በሚካሄድ የኔቶ ወታደራዊ ልምምድ ላይ የሚሳተፉ የዩኬ ሠራዊት አባላትን አነጋግረዋል።

    ባለፈው ወር ደግሞ የሩሲያ ሱ-35 ተዋጊ ጄት ‘ሩቬት ጆይንት’ የተባለውን የስለላ አውሮፕላንን እጅግ ተጠግቶ አውቶፓይለቱን እንዲጠፋ በማድረግ የአውሮፕላኑ አደጋ ጊዜ ስርዓቱ እንዲበራ አድርጎ ነበር።

    ሌላ ሱ-27 ጄት ደግሞ ስድስት ጊዜ በዩናይትድ ኪንግደም አውሮፕላን ፊት እንዳለፈ እና ስድስት ሜትር ርቀት ድረስ ወደ አውሮፕላኑ አፍንጫ እንደተጠጋ ተገልጿል።

  3. በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የሰላም ስምምነት ይደረሳል በሚል ተስፋ የነዳጅ ዋጋ ቅናሽ አሳየ

    በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የሰላም ስምምነት ይፈረማል የሚል ተስፋ በስፋት በመታየቱ የነዳጅ ዋጋ በከፍተኛ ሁኔታ ቀነሰ። የእስያ የአክሲዮን ገበያዎች ላይም ጭማሪ ታይቷል።

    ቅዳሜ ዕለት የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከቴህራን ጋር የሰላም ስምምነቱ ነጥቦች "በአብዛኛው ድርድር ተደርጎባቸዋል" በማለት ዝርዝሩን ይፋ ሳያደርጉ ቀርተዋል።

    ሁለቱ አገራት በበርካታ ጉዳዮች ላይ መስማማታቸው ሲገለጽ ቢቆይም ትራምፕ ተደራዳሪዎች ከኢራን ጋር ስምምነት ለመፈራረም እንዳይጣደፉ አሳስበዋል።

    ሰኞ ጠዋት በእስያ ገበያ ብሬንት ድፍድፍ ነዳጅ 5.5 በመቶ ቅናሽ ያሳየ ሲሆን በአሜሪካ ደግሞ የ5.8 በመቶ ቀንሶ 90.99 ዶላር ተሸጧል።

    ትራምፕ ከኢራን ጋር የሚደረገው ድርድር የሆርሙዝ ወሽመጥን ዳግም ማስከፈትን የሚያካትት ነው ያሉ ሲሆን ይህም ለወራት መንቀሳቀሻ አጥተው የቆሙ ነዳጅ ጫኝ መርከቦችን በነጻነት እንዲጓዙ ያስችላል ተብሎ ነበር።

    ጠባቡ የባሕር መተላለፊያ የዓለም አንድ አምስተኛ ነዳጅ እና የተፈጥሮ ጋዝ የሚተላለፍበት ሲሆን ከየካቲት 21 2018 ዓ.ም. በኋላ ተዘግቷል።

    ቅዳሜ ዕለት ትራምፕ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ከሳዑዲ አረቢያ፣ ከዩናይትድ አረብ ኤሜሬትስ፣ ኳታር ጋር “በሰላም ስምምነቱ የመግባቢያ ሰነድ” ዙሪያ “ጥሩ ውይይት” ማድረጋቸውን ገልጸዋል።

  4. ፕሬዝዳንት ትራምፕ የአሜሪካ ተደራዳሪዎች ከኢራን ጋር ስምምነት ለመፈጸም "እንዳይጣደፉ" አሳሰቡ

    አሜሪካ እና ኢራን ጦርነቱን ለመቋጨት የሚያደርጉት ድርድር ወደ ማጠናቀቂያው እንደተቃረበ መነገሩን ተከትሎ፤ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ተደራዳሪዎቻቸው ከኢራን ጋር “ተጣድፈው ወደ ስምምነት እንዳይገቡ” አዘዙ።

    በሁለቱ አገራት ንግግር እየተደረገበት ያለው የስምምነት ዕቅድ ከያዛቸው ነጥቦች መከካከል የተኩስ አቁሙን ለ60 ቀናት ማራዘም፣ የሆርሙዝ ወሽመጥን በድጋሚ መክፈት እንዲሁም የኢራንን የኒውክሌር ፕሮግራም በተመለከተ ተጨማሪ ድርድር ማካሄድ የሚሉት ይገኙበታል።

    ትራምፕ ማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት ጽሑፍ ንግግሩ “ገንቢ” በሆነ ሁኔታ እየተካሄዱ መሆኑን ቢገልጹም፤ አክለው ግን “ሁለቱም ወገኖች ጊዜያቸውን መውሰድ እና በትክክል ማከናወን አለባቸው” ብለዋል።

    ፕሬዝዳንቱ ቅዳሜ ዕለት ስምምነቱ “በአብዛኛው ድርድር እንደተደረገበት” መገናራቸው ስምምነት ይፋ መደረጉ አይቀሬ ነው የሚል ግምት ፈጥሮ ነበር።

    የኢራን ባለሥልጣናትም ተመሳሳይ ሀሳብ አመልክተው ነበር። የአገሪቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ኢስማኤል ባጋይ ሁለቱ ወገኖች ስምምነት ላይ ለመድረስ “እጅግ ቅርብ እና እጅግ ሩቅ” ናቸው ብለው ነበር።

    የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን እንደዘገቡ ከሆነ ድርድር የሚካሄድበት እቅድ የመጨረሻው ስምምነት አይደለም። ይልቁንም ሁለቱ አገራት የተወሰኑ አጨቃጫቂ ጉዳዮች በኋላ ድርድር እንዲካሄድባቸው እንደሚፈቅድ ዘግበዋል።

    ኢራን ላይ የተጣለው ማዕቀብ የሚነሳበት መጠን እና ጊዜ፣ የታገደውን የኢራን ገንዘብን የማስለቀቅ ጉዳይ እንዲሁም አሜሪካ የቴህራንን የኒውክሌር ፍላጎት ለመገደብ ያላት ፍላጎት ለበኋላ ድርድር ከሚተዉ ነጥቦች መካከል ናቸው።

    ይህ የስምምነት ዕቅድ ሪፐብሊካኖችን ለሁለት የከፈለ ሲሆን የተወሰኑት ኢራን ላይ ለዘብተኛ አቋም የያዘ እንደሆነ በይፋ እየተናገሩ ነው።

    ትራምፕ እሁድ ዕለት በትሩዝ ሶሻል ገጻቸው ባጋሩት ልጥፍ፤ ኢራን የኒውክሌር መሣሪያ ልትሰራ እንደማትችል “መረዳት እንዳለባት” በአጽንኦት አንስተዋል። ቴህራን የኒውክሌር ፕሮግራሟ ለሰላማዊ ዓላማ እንደሚውል በተደጋጋሚ ስትገልጽ ቆይታለች።

    አንዳንድ የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን ከኢራን ጋር በሚደረሰው ስምምነት አማካኝነት ኢራን የበለጸገ ዩራኒየሟን አሳልፋ እንደምትሰጥ ዘግበዋል።

    የኢራን ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዜሽኪያን ለአገሪቱ ቴሌቪዥን በሰጡት ቃለ መጠይቅ ቴህራን “ፍላጎቷ የኒውክሌር መሣሪያ እንዳልሆነ ለዓለም ለማረጋገጥ” ዝግጁ እንደሆነች ተናግረዋል።

    የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማርኮ ሩቢዮ በበኩላቸው በድርድሩ “ጉልህ” መሻሻል ቢታይም፤ ሂደቱ “የመጨረሻ ደረጃ እንዳልደረሰ” ገልጸው ነበር።