ትራምፕ አረብ እና ሙስሊም አገራት ከእስራኤል ጋር ስምምነት እንዲፈርሙ ግፊት እያደረጉ ነው

የፎቶው ባለመብት, EPA/Shutterstock
አሜሪካ ከኢራን ጋር ከስምምነት ለመድረስ መቃረቧን እየገለጹ ያሉት ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከዚያ በፊት ግን ዋነኞቹ ሙስሊም አገራት ከእስራኤል ጋር የአብረሃም ስምምነትን እንዲፈርሙ ጥሪ አቀረቡ።
ድርድሩ “በጥሩ ሁኔታ እየተካሄደ ነው” ያሉት ፕሬዝዳንቱ ከኢራን ጋር የሚካሄደውን ጦርነት የሚያስቆመው ስምምነት ከመፈረሙ በፊት ብዙሃኑ ሕዝባቸው ሙስሊም የሆኑ ስድስት አገራት ከእስራኤል ጋር ያላቸውን ግንኙነት የሚያሻሽለውን ስምምነት መፈረም እንዳለባቸው አስታውቀዋል።
ፕሬዝዳንት ትራምፕ ከኢራን ጋር የሚደረገውን ስምምነት ከስድስት ዓመት በፊት ዩናይትድ አረብ ኤምሬትስ እና ባህሬን በማስከተልም ሞሮኮ እና ሱዳን ከእስራኤል ጋር ከተፈራረሙት የአብረሃም ስምምት ጋር አስተሳስረው እያቀረቡት ነው።
ከበርካታ ሙስሊም እና አረብ አገራት መሪዎች ጋር መነጋገራቸውን በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ የጠቀሱት ትራምፕ ውስብስቡን ሥራ አሜሪካ መሥራቷን በመግለጽ “በተከታይነት እነዚህ አገራት በሙሉ ቢያንስ የአብረሃም ስምምነትን መፈረም ይጠበቅባቸዋል” ብለዋል።
ከእነዚህም መካከል ሳዑዲ አረቢያ፣ ኳታር፣ ፓኪስታን፣ ቱርክ፣ ግብፅ እና ዮርዳኖስን በመጥቀስ ስምምነቱን እንዲፈርሙ እንደሚፈልጉ አስታውቀዋል።
ነገር ግን ግብፅ እና ዮርዳኖስ ከእስራኤል ጋር ግንኙነት ያላቸው ሆነው ሳለ ለምን እንደጠቀሷቸው ግልጽ አይደለም። እስራኤል ከቱርክ ጋር ለረጅም ጊዜ የቆየ የሻከረ ግንኙነት ያላት ሲሆን፣ የጋዛውን ጦርነት ተከትሎ የበለጠ ተቃቅረዋል።
የተጠቀሱት አገራት የአብረሃም ስምምነትን የሚፈርሙ ከሆነ እስራኤል ከአብዛኞቹ አረብ እና ሙስሊም አገራት ጋር ያላትን ግንኙነት በከፍተኛ ሁኔታ የሚያሻሽል ነው።








