
የፎቶው ባለመብት, reuters
ኢራን በዚህ ወር የእስላማዊ አብዮታዊ ዘብ አዛዦችን፣ ወታደራዊ አማካሪዎችን
እንዲሁም ከሚሳዔል እና ድሮን ጋር የተያያዙ ቁሳቁሶችን ወደ የመን መላኳን ምንጮችን ጠቅሶ ሮይተርስ ዘገበ።
ቴህራን ይህንን እርምጃ የወሰደችው በየመን የሚገኙት አጋሮቿ ሁቲዎች፣ በቀይ
ባሕር የሚደረጉ የመርከብ ጉዞዎች ላይ አደጋ እንዲጥሉ በማለም እንደሆነ ምንጮቹ ጠቅሰዋል።
በጉዳዩ ላይ መረጃው ያላቸው አራት ምንጮች እንዲሁም የየመን ማስታወቂያ ሚኒስትር
እና የቀጣው ደኅንነት ተንታኝ፣ ኢራን ወደ የመን ወታደራዊ ቁሳቁሶችን ያጓጓዘችው እአአ ሐምሌ 13 ነው ሲሉ ለሮይተርስ ተናግረዋል።
ለደኅንነታቸው በሚል ስማቸው እንዳይጠቀስ ጠየቁ ሁለት የኢራን ምንጮች የአብዮታዊ ዘብ አዛዦች ቁጥር ከ10 እስከ 21 የሚደርስ መሆኑን ለሮይተርስ ተናግረዋል። ከእነዚህም መካከል ከፍተኛ አዛዦች እንደሚገኙበት ገልጸዋል።
ከኢራን የተነሳው አውሮፕላን በሁቲ ቁጥጥር ስር ወደሚገኘው ሰነዓ በረራ ቢያደርግም
አውሮፕላን ማረፊያው በሳዑዲ ጥቃት ከደረሰበት በኋላ ግን ወደ ቀይ ባሕር ወደብ ከተማዋ ሆዴይዳህ ማምራቱን ዘገባው ያመለክታል።
አንድ ምንጭ “የአብዮታዊ ዘብ አዛዦች ወደዚያ የተጓዙት የሁቲን ዘመቻዎች ለመደገፍ እንዲሁም በአዲስ
የሚሳዔል ሥርዓት ላይ ስልጠና ለመስጠት ነው” ብለዋል።
በተጨማሪም ኢራን የሁቲን እንቅስቃሴዎች ለመደገፍ በአውሮፕላኑ ወርቅ መላኳ ተጠቅሷል።
ቴህራን በተደጋጋሚ በየመን የሚንቀሳቀሱት ሁቲዎችን የሚሳዔል አቅም ለመገንባት
ምንም ዓይነት ድጋፍ እንዳላደረገች በመግለጽ ስታስተባብል ቆይታለች።
የኢራን መንግሥት በጉዳዩ ላይ ምላሽ እንዲሰጥ ሮይተርስ ያደረገው ጥረት ለጊዜው
አልተሳካም፥።
አውሮፕላኑ ውስጥ እንደነበሩ የተናገሩት የሁቲ የሚዲያ ኃላፊ አብደል ራህማን አል አህኖሚ፣ ኢራን ወደ የመን ወታደራዊ ባለሙያዎችን ልካለች የሚለውን ክስ "ውሸት እና ፈጠራ" ሲሉ የገለጹ ሲሆን፣ በአውሮፕላኑ ውስጥ የነበሩት ሁሉም ተሳፋሪዎች ሲቪሎች እንደነበሩም ተናግረዋል።
ሁቲዎች ከዚህ ቀደም የኢራን ተቀጽላ መሆናቸውን ያስተባበሉ ሲሆን፣ የራሳቸውን የጦር መሣሪያዎች እንደሚያመርቱም ገልጸዋል።
በየመን የሚንቀሳቀሰው ሁቲ ሳዑዲ አረቢያ አድርሳዋለች ባለው የሐምሌ 13 የሰነዓ አውሮፕላን ማረፊያ ድብደባ ምላሽ ለመስጠት፣ ሳዑዲ ላይ የባህር ላይ እገዳ መጣሉን ሰኞ ዕለት አስታውቋል።
በሳዑዲ መንግሥት የሚደገፈው የየመን መንግሥት የማስታወቂያ ሚኒስትር ሞአመር አል ኢርያኒ በበኩላቸው፣ የኢራን አብዮታዊ ዘብ አዛዦች እና መሳሪያዎች ወደ የመን መምጣታቸውን ለሮይተርስ
በስልክ በሰጡት ቃለ ምልልሰ ላይ አረጋግጠዋል።
"ተልዕኳቸው የሚሊሻዎቹን ወታደራዊ አቅም ማጠናከር እና በቀይ ባሕር እና በባብ አል ማንዳብ የባህር መስመር ላይ ያለው ዓለም አቀፍ መተላለፊያ ደኅንነትን አደጋ ላይ እንዲጥሉ ማዘጋጀት ነው" ብለዋል።