ቀጥታ, ከአሜሪካ ጋር የተደረሰው ስምምነት በኢራን ባለሥልጣናት እስኪጸድቅ እየተጠበቀ መሆኑ ተዘገበ

ኢራን ከአሜሪካ ጋር የደረሰችው የመግባቢያ ሰነድ ይዘት በሚመለከታቸው የአገሪቱ ከፍተኛ ባለሥልጣናት የመጨረሻ ውሳኔ እንዳልተሰጠበት ከኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ጋር ግንኙነት ያላቸው የዜና ምንጮች ዘገቡ።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. የናይጄሪያ ፕሬዝዳንት ታጣቂዎች “እጃቸውን እንዲሰጡ” አስጠነቀቁ

    የናይጄሪያው ፕሬዝዳንት ቦላ ቲኑቡ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የናይጄሪያው ፕሬዝዳንት ቦላ ቲኑቡ

    በናይጄሪያ የሚንቀሳቀሱ ታጣቂ ቡድኖች “እጃቸውን እንዲሰጡ ካልሆነ ግን አገሪቷ ባላት ኃይል ሁሉ እንደሚመቱ” ፕሬዝዳንት ቦላ አሕመድ ቲኑቡ አስጠነቀቁ።

    ፕሬዝዳንቱ ይህን ያሉት በአገሪቷ የሚከበረውን ‘የዲሞክራሲ ቀን’ በማስመልከት በብሔራዊ መገኛኛ ብዙኃን ባስተላለፉ መልዕክት ነው።

    በመልዕክታቸው በቅርቡ የተፈፀመው የተማሪዎች እገታ የዚህ ዓመቱን በዓል እንዳደበዘዘው ተናግረዋል።

    ሆኖም የአገሪቷ ፀጥታ ጉዳይ ከመንግሥት እጅ አለመውጣቱን ገልጸዋል።

    "ዲሞክራሲ ያለ ደኅንነት ተጨባጭ አይደለም” ያሉት ፕሬዝዳንቱ፣ ከ50 ሺህ በላይ አዳዲስ የፖሊስ መኮንኖችን፣ ለመከላከያ እና ለፀጥታ 4 ቢሊዮን ዶላር ዓመታዊ በጀት መመደባቸውን አስታውቀዋል።

    በሺዎች የሚቆጠሩ አዲስ ወታደራዊ ምልመላዎችም እንዲካሄዱ ተወስኗል ብለዋል።

    ፕሬዝዳንቱ ከሦስት ዓመት በፊት ወደ ሥልጣን ከመጡ በኋላ ጦራቸው ባለፈው ዓመት ብቻ 13 ሺህ "ሽብርተኞችን" መግደሉን እና በታጣቂዎቹ ምክንያት የሚደርስ የንጹኃን ሞትም ከአውሮፓውያኑ 2015 ወዲህ በ81 በመቶ መቀነሱን ተናግረዋል።

    ከ124 ሺህ በላይ ተዋጊዎች እና ቤተሰቦቻቸው መሣሪያቸውን ማውረዳቸውንም አክለዋል።

    ሆኖም ተንታኞች በታጣቂዎች የሚፈፀሙ ጥቃቶች በተለያዩ የአገሪቷ ግዛቶች ነዋሪዎች ላይ ተፅዕኖ ማሳደር መቀጠላቸውን ገልጸዋል።

    ወደ ደቡባዊ የአገሪቱ ክፍሎችም እየተዛመቱ ነው ብለዋል።

  2. ከኢራን ጋር ግንኙነት ያለው ቡድን የአሜሪካ ደኅንነት ተቋማትን የድሮን መረጃ መጥለፉን አስታወቀ

    ፊቱ የማይታይ የበይነ መረብ መረጃ መዝባሪ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በበይነ መረብ ላይ የጽንፈኛ ቡድኖችን እንቅስቃሴ የሚከታተለው ድርጅት ከኢራን ጋር ግንኙነት ያለው የበይነ መረብ ሰርሳሪ ቡድን የአሜሪካ ደኅነንት ተቋማት የሆኑትን ሲአይኤን እና ኤፍቢአይ የድሮኖች ሥርዓትን ሰብሮ በመግባት የዓለም ዋንቻን ዒላማ ማድረጉን መገልጹን አስታወቀ።

    የአሜሪካ ተቋም የሆነው "ሰርች ቱ አይደንቲፋይ ኢንተርናሽናል ቴረሪስት ግሩፕስ” ባወጣው መግለጫ “ሃንዛላህ” የተባለው ቡድን “በድሮን ለወራት የተቀረጹ ምሥሎች እና መረጃዎች ንማግኘት መቻሉን” አሳውቋል ብሏል።

    የመረጃ መረብ ቀበኞቹ (ሃከርስ) ድሮኖቹ በፀረ ሽብር ዘመቻዎች ወቅት የሰዎችን ገጽታ እና የመኪኖችን የሰሌዳ ቁጥር የሚለይ የሚለይ ቴክኖሎጂ ያላቸው መሆኑን አስታውቀዋል።

    የአሜሪካ ፌደራል መንግሥት ፖሊሶችን እና የኤፍቢአይ ወኪሎችን የዓለም ዋንጫ ውድድሮች በሚካሄድባቸው ስታዲየም ሱሪያ በማሰማራት ጥበቃ እያደረገ ሲሆን ፈቃድ ያላገኙ ድሮኖች እንዳይንቀሳቀሴሱ ተከልክለዋል።

    የአሜሪካ ፍትሕ ሚኒስቴር ቀደም ሲል ከኢራን ጋር ግንኙነት ባላቸው ወገኖች የበይነ መረብ ጥቃት ሊፈጸም የሚችልበት አጋጣሚ ሊኖር እንደሚችል አስጠንቅቆ ነበር።

    ሃንዛል የተባለው ቡድን ከድሮኖች የተመዘበሩ ናቸው ያላቸውን ምሥሎች እና ቪዲዮዎችን ይፋ ደያረገ ሲሆን፣ የአሜሪካ የደኅንነት መሥሪ ያቤቶች ግን ድረኖቹ ሃክ (መጥለፍ) በመደረጋቸው ላይ ጥያቄ አንስተዋል።

    የሽብር ቡድኖችን የሚከታተለው ድርጅት እንዳለው ይፋ ከሆኑት ቪዲዮዎች መካከል አንዱ ጠለፋው የተፈጸመው በታኅሣሥ 2024 ፖሊስ የአንድ ተቋምን ሶፍት ዌር በተጠቀመበት አጋጣሚ መሆኑን አመለክቷል።

    የመረጃ መዝባሪው ቡድን ሃንዛል በበኩሉ ባለፈው መጋቢት ወር የኤፍቢአይ ዳይሬክተር የሆኑትን ካሽ ፓቴልን የግል አካውንት በመስበር የግለሰቡን ግላዊ ፎቶዎችን እና ሌሎች መረጃዎች ንአጋርቷል።

    የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መሥሪ ያቤት የዚህን የመረጃ ቀበኛ ቡድን አባላትን ለሚጠቁሙ ሰዎች አስከ 20 ሚሊዮን ዶላር ድረስ ሽልማት ለመስጠት ቃል ገብቷል።

  3. ከአሜሪካ ጋር የተደረሰው ስምምነት በኢራን ባለሥልጣናት እስኪጸድቅ እየተጠበቀ መሆኑ ተዘገበ

    የአሜሪካ ምክትል ፕሬዝዳንት ቫንስ እና የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አራግቺ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images/Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የአሜሪካ ምክትል ፕሬዝዳንት ቫንስ እና የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አራግቺ

    ኢራን ከአሜሪካ ጋር የደረሰችው የመግባቢያ ሰነድ ይዘት በሚመለከታቸው የአገሪቱ ከፍተኛ ባለሥልጣናት የመጨረሻ ውሳኔ እንዳልተሰጠበት ከኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ጋር ግንኙነት ያላቸው የዜና ምንጮች ዘገቡ።

    ታስኒም የተባለው የዜና ወኪል ስማቸው ያልተገለጸ ጉዳዩን የሚያውቁ ምንጮችን ጠቅሶ እንደዘገበው ፕሬዝዳንት ትራምፕ “ባለፉት ቀናት በማስፈራራት፣ በጫና እና በወታደራዊ እርምጃ እንዲሁም በኳታር አሸማጋዮች በኩል የኢራንን አቋም ለማስቀየር ሞክረው ነበር። ነገር ግን ኢራን የተደረጉትን አዳዲስ ለውጦች ለመቀበል አልፈቀደችም” ብለዋል።

    የዜና ወኪሉ ጨምሮም እንደገለጸው ከአሜሪካ ጋር መግባባት ላይ የተደረሰበት ሰነድ “በሚመለከታቸው የኢራን ተቋማት ተመርምሮ ተቀባይነትን ማግኘት አለበት፤ ነገር ግን እስከዚያው የሚነገሩ ግምቶች እና ዜናዎች ትክክለኛ አይሆኑም።”

    ሌላኛው የኢራን ዜና አገልግሎት ፋርስ አሜሪካ አንዳንድ ቅድመ ሁኔታዎቿን የተወች መሆኑን፣ ነገር ግን “ገና ምንም ዓይነት ስምምነት ላይ አልተደረሰም። ስዊትዘርላንድ ውስጥ ስምምነቱ ስለመፈረሙ ወይም ፊት ለፊት ስለሚደረግ ንግግር የሚወራው ተጨባጭ አይደለም” በማለት ዘግቧል።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ሐሙስ ማታ “የኢራን መንግሥት ባለሥልጣናት በእያንዳንዱ ነጥብ ላይ ውሳኔ እስከሚሰጡ ድረስ ስለፊርማው ሥነ ሥርዓት እና ቦታው መነጋገር የሚፈይደው ነገር የለም” ብለው ነበር።

    ነገር ግን የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ቀደም ብለው ከኢራን ጋር ከስምምነት መደረሱን በመግለጽ “ከኢራን ጋር የሚደረገውን ጦርነት አብቅተናል” በማለት አሳውቀው ነበር።

    ፕሬዝዳንቱ በጽህፈት ቤታቸው ለጋዜጠኞች እንደተናገሩት በጥቂት ቀናት ውስጥ ለስምምነቱ ፊርማ ምክትላቸው ጄ.ዲ ቫንስ ወደ አንድ የአውሮፓ ከተማ እንደሚሄዱ ገልጸዋል።

    በተጨማሪም የአሜሪካ ኃይሎች በደቡባዊ ኢራን የጣሉት የባሕር ላይ ዕገዳ ስምምነቱ እስኪቋጭ ድረስ ሙሉ ለሙሉ ተግባራዊ መሆኑ እንደሚቀጥል ተናግረዋል።

  4. ታዋቂዋ ዘፋኝ አሪያና ግራንዴ የአሜሪካ መንግሥት ሙዚቃዋን ለፀረ ስደተኞች ፖሊሲው እንዳይጠቀም ጠየቀች

    አሪያና ግራንዴ

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty

    የምስሉ መግለጫ, አሪያና ግራንዴ

    ታዋቂዋ አሜሪካዊት ዘፋኝ አሪያና ግራንዴ ሙዚቃዋ የአሜሪካን የስደተኞች ፖሊሲን ለማስተዋወቅ ጥቅም ላይ እንዳይውል የፕሬዝዳንቱን ጽህፈት ቤት ጠየቀች።

    በቲክቶክ ላይ በተጋራው ቪዲዮ ላይ የአሜሪካ የድንበር ጠባቂዎች ሰዎችን እጃቸውን በካቴና እያሰሩ ወደ እስር ቤት ሲወስዷቸው የአሪያና ግራንዴ “ጉድባይ” [ደህና ሁኑ] የሚለው ታዋቂ ዘፈን በማጀቢያነት ጥቅም ላይ ውሏል።

    የቪዲዮው ማብራሪያ “ደህና ሁኑ...ፕሬዝዳንት ትራምፕ በታሪክ በደንብ የሚጠበቅ ድንበር ፈጥረዋል” ይላል።

    አሪያና ግራንዴ ይህንን ቪዲዮ በተመለከተ "እባካችሁ ሙዚቃዬን ከዚህ ጭካኔ ከተሞላበት፣ ሰብአዊነት ከጎደለው ክፋት ጋር አታያይዙት” ስትል ጽፋለች።

    የዋይት ሐውስ ቃል አቀባይ አቢጌል ጃክሰን ለአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን በሰጠችው ምላሽ “በትክክልም ጭካኔ የሞላበት፣ ሰብአዊነት የጎደለው እና ክፉው ድርጊት ሕገወጥ ስደተኞች ንጹሃን አሜሪካውያንን መጉዳታቸው ወይም መግደላቸው ነው” ብላለች።

    ዋይት ሐውስ ቪዲዮውን ያጋራው ፕሬዝዳንት ትራምፕ ለቀጣይ ሁለት ዓመት ተኩል ለስደተኞች ተቆጣጣሪ ተቋማት የሚውል 70 ቢሊዮን ዶላር በጀት ካጸደቁ በኋላ ነው።

    አሪያና ግራንዴ በቪዲዮው ላይ ቅሬታዋን ካሰማች በኋላ የቪዲዮው ድምጽ እንዳይሰማ ሲደረግ የእሷ አስተያየትም ጠፍቷል።

    አሪያና ግራንዴ ሙዚቃቸው ለፕሬዝዳንት ትራምፕ የፖለቲካ አጀንዳ ማስተዋወቂያነት እንዳይውል ከጠየቁ ቁጥራቸው እየጨመረ ከመጣው የአርቲስቶች ዝርዝር ውስጥ ስሟ ተካትቷል።

    በተመሳሳይ ሙዚቃዋ የስደተኛ ተቆጣጣሪዎችን ሥራ በሚያሳይ ቪዲዮ ላይ ጥቅም ላይ የዋለባት ሌላኛዋ አሜሪካዊት ሙዚቀኛ ሳብሪና ካርፔንተር “እኔን እና ሙዚቃዎቼን ሰብአዊነት ለሌለው ዓላማችሁ ፈጽሞ አትጠቀሙ” ብላ ጽፋ ነበር።

    አባ፣ ሴሊን ዲዮን እና ቢዮንሴ ፕሬዝዳንት ትራምፕ ድጋሚ ለመመረጥ ቅስቀሳ በሚያደርጉበት ጊዜ ሙዚቃዎቻቸውን እንዳይጠቀሙ ከጠየቁ ድምጻውያን መካከል ይገኙበታል።

  5. የትራምፕ አስተዳደር ኢራናውያን ስደተኞችን ወደ ማዕከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ ለመላክ ማቀዱ ተዘገበ

    ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር ኢራናውያን ስደተኞችን ወደ ማዕከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ ለመላክ ማቀዱን ሮይተርስ የዜና ወኪል ዘገበ።

    ሮይተርስ ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸውን ባለሥልጣንን እና ሁለት ጠበቆችን ጠቅሶ እንደዘገበው፤ የትራምፕ አስተዳደር በግጭት ወደምትናጠው አገር ኢራናውያን ስደተኞችን ለመላክ አቅደዋል።

    ኢራናውያን ስደተኞችን የሚወክሉት ጠበቃ ኤምሊ ትሩሰል እንደተናገሩት ወደ ማዕከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ ይላካሉ ከተባሉት መካከል ሁለት ሴቶች ይገኙበታል። ኢራናውያኑ ወደ ትውልድ አገራቸው ከተመለሱ እንግልት እና ስቅይት እንደሚጠብቃቸው ጠበቃቸው ተናግረዋል።

    ሮይተርስ እንደዘገበው በቅርቡ ማዕከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ፤ አሜሪካ የምታስወጣቸውን ስደተኞች ለመቀበል ከአገሪቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጋር ስምምነት ላይ ደርሷል።

    ስለ ጉዳዩ ሁለቱም ወገኖች አስተያየት አልሰጡም።

    ሮይተርስ ያነጋገራቸው ባለሥልጣን እንደተናገሩት በመጀመሪያው ጉዞ ከኢራናውያን በተጨማሪ ሶሪያውያን እና አፍጋኒስታናውያን የሆኑ 20 ስደተኞች የሚጓዙ ይሆናል።

    ከአሜሪካ የሚባረሩት ስደተኞች በሚቀጥለው ሳምንት መጨረሻ ገደማ ወደ አፍሪካዊቷ አገር እንደሚጓዙ ተናግረዋል።

    ከሚባረሩት ሰዎች መካከል ሕጋዊ መኖሪያ ለማግኘት አመልክተው ሳለ ተይዘው ከአሜሪካ እንዲባረሩ በኢሚግሬሽን ፍርድ ቤት የተወሰናባቸው ይገኛሉ።

    ስደተኞች ሲባረሩ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

  6. ከትራምፕ ንግግር በኋላ የነዳጅ ዋጋ ሲቀንስ፣ ኢራን ስምምነቱ ገና አልተቋጨም አለች

    ቴህራን ውስጥ የሚታይ የሕንጻ ላይ ምሥል

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ከኢራን ጋር የሚደረገውን ጦርነት የሚያስቆም ስምምነት ላይ መደረሱን ሲያስታውቁ ኢራን ግን ገና መቋጫ ላይ አለመደረሱን ገለጸች።

    በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የሚካሄደው ጦርነት የበለጠ ይባባሳል ተብሎ በተሰጋበት ጊዜ ፕሬዝዳንት ትራምፕ በኢራን ላይ እንደሚፈጸም የተናገሩትን ጥቃት ሰርዘው የመጀመሪያ ደረጃ ስምምነት ላይ መደረሱን ተናግረዋል።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ኢስማኤል ባጋይ ለአገራቸው ቴሌቪዥን ከስምምነት ተደርሷል መባሉን “ግምታዊ” በማለት “ከመደምደሚያው ላይ እንዳልተደረሰ” ገልጸዋል።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ከዚህ ቀደምም ሁለቱ አገራት ጦርነቱን ወደሚያበቃ ስምምነት እየተቃረቡ መሆናቸውን በተደጋጋሚ ተናግረው እንደነበር ይታወሳል።

    ይህ የትራምፕ ንግግር ከተሰማ በኋላ ውጥረቱ በተባባሰባቸው ባለፉት ቀናት ጭማሪ እየሳየ የነበረው የዓለም ገበያ ዋጋ ከአራት በመቶ በላይ ቅናሽ በመሳየት በበርሜል ወደ 89 ዶላር ወርዷል።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ በጽሕፈት ቤታቸው ለጋዜጠኞች እንደተናገሩት "ኢራን ፈጽሞ የኒውክሌር ጦር መሳሪያ እንዳይኖራት የሚያደርግ ስምምነት ላይ ደርሰናል፤ ይህንን ለማሳካት ስንል ነበር በዚህ ሁሉ ውስጥ ያለፍነው። በጣም ትልቅ ስምምነት ነው” ብለዋል።

    ጨምረውም የስምምነቱ ሰነድ ተዘጋጅቶ ሲያበቃ “በጣም በፍጥነት” ሁለቱ አገራት “ምናልባትም ፊርማው አውሮፓ ውስጥ” ይካሄዳል ብለዋል።

    በጦርነቱ ምክንያት የተዘጋው ወሳኙ የባሕር መተላለፊያ መስመር ሆርሙዝም “ስምምነቱ ሲፈረም ወዲያውኑ ይከፈታል” በማለት በጉዳዩ ላይ ከእስራኤል እና ከመካከለኛው ምሥራቅ አጋር አገራት ጋር መነጋገራቸውን እነሱም “ደስተኛ” መሆናቸውን ተናግረዋል።

    ለውጤቱ ለትራምፕ ያላቸውን አድናቆት የገለጹት የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ስምምነቱ “[የኢራንን] የዳበረ ዩራኒየም ማስወገድ፣ የዩራኒየም ማበልጸጊያ ተቋማትን ማውደም፣ የሚሳዔል ምርቷን መገደብ እና በቀጣናው ላሉ ሽብርተኛ ቡድኖች ድጋፏን ማቆም” የሚሉ እንደሚገኙበት ገልጸዋል።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ እንዳሉት ደግሞ የሚፈረመው የመግባቢያ ሰነድ “ቢጠናቀቅም” አሜሪካ “ከልክ ያለፉ እና አዳዲስ ጥያቄዎችን እያቀረበች ነው” በማለት ኢራን ካስቀመጠችው “ቀይ መስመር ፈቀቅ እንደማትል” አስታውቀዋል።

  7. ፕሬዝዳንት ትራምፕ ኢራን ላይ የሚደርሰው ጥቃት ‘እንደቆመ’ አስታወቁ

    ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ኢራን ላይ የሚሰነዘረው ጥቃት ‘እንደተገታ’ አስታወቁ።

    ከኢራን ጋር የሚደረገው ውይይት መሻሻል እንዳሳየ እና ከስምምነት ሊደረስ እንደሚችልም ገልጸዋል።

    ትራምፕ ትናንት ሐሙስ ኢራንን “ክፉኛ እንመታለን” ብለው ቢዝቱም፤ ሊያደርሱት የነበረውን ጥቃት ለመሰረዝ መወሰናቸውን ተናግረዋል።

    ፕሬዝዳንቱ ኻርግ ደሴት ላይ ጥቃት እንደሚፈጸም አስጠንቅቀው ነበር።

    ከኢራን ጋር የሚፈረመው የመግባቢያ ሰነድ “የመጨረሻ ደረጃ” ላይ መድረሱን ጠቅሰው በዚህ ሳምንት ስምምነቱ ሊገባደድ እንደሚችል አስረድተዋል። ስምምነቱ የሚፈረመው አውሮፓ ውስጥ እንደሚሆን ጠቁመዋል።

    ስምምነቱ ኢራን የኒውክሌር መሣሪያ እንዳይኖራት የሚያግድ እንዲሁም በአፋጣኝ የሆርሙዝ ወሽመጥ እንዲከፈት የሚያስገድድ እንደሚሆን ትራምፕ አስረግጠው ተናግረዋል።

    ትራምፕ ይህንን ቢሉም የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ስምምነት ላይ ለመድረስ አለመቃረባቸውን አስታውቀዋል።

    አሜሪካ በድርድሩ “ከልክ ያለፈ ጥያቄ” እያቀረበች እንደሆነም ጠቅሰዋል።

    ኳታር ሁለቱን አገራት ለማሸማገል ጥረት እያደረገች እንደሆነ ተጠቁሟል።

    ትራምፕ ኢራን ላይ ጥቃት እንደማይፈጸም መግለጻቸውን ተከትሎ የድፍድፍ ነዳጅ ዋጋ ቀንሷል።

  8. አሜሪካ ‘ከማትወጣው ማጥ’ ውስጥ ትገባለች ስትል ኢራን አስጠነቀቀች

    የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባኤ ጋሊባፍ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባኤ ጋሊባፍ

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የኢራንን ወሳኝ የነዳጅ ማስተላለፊያ ደሴት የመቆጣጠር ዕቅድ እንዳላቸው ይፋ ካደረጉ በኋላ አሜሪካ ‘ከማትወጣበት ማጥ’ ውስጥ ትገባለች ሲሉ የኢራን ከፍተኛ ባለሥልጣን አስጠነቀቁ።

    የኢራን ፓርላማ አፈጉባኤ እና ከአሜሪካ ጋር በሚደረገው ንገግር ዋነኛ ተደራዳሪ የሆኑት ሞሐመድ ባጊር ጋሊባፍ በኤክስ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት መልዕክት “የተሳሳተ ስልት እና ግብታዊ ውሳኔ ሁሉን ነገር በአስከፊ ሁኔታ ይገለባብጠዋል” ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

    ባለሥልጣኑ ጨምረውም እነዚህ ውሳኔዎች “ለዓመታት የማይወጣበት ማብቂያ የሌለውን አዘቅት” በመፍጠር “የነዳጅ መሠረተ ልማቶች እና ገበያውን” ሊያውድሙት ይችላሉ ብለዋል።

    አሜሪካ እንደምትለው የምትቀጥል ከሆነ “ሌላኛዋን ኢራን ትመለከታላችሁ” በማለት ጋሊባፍ አስጠንቅቀዋል።

  9. ለዓለም ዋንጫ አሜሪካ እንዳይገባ የተከለከለው ሶማሊያዊው ዳኛ የአውሮፓ ጨዋታን እንዲመራ ተመረጠ

    ኦማር አርታን

    የፎቶው ባለመብት, SOCIAL

    የምስሉ መግለጫ, ኦማር አርታን

    አሜሪካ እንዳይገባ ተከልክሎ በዓለም ዋንጫ ላይ የመዳኘት ዕድልን የተነፈገው ሶማሊያዊ የእግር ኳስ ዳኛ ኦማር አርታን የአውሮፓ ሱፐር ካፕ ጨዋታን እንዲዳኝ ተመረጠ።

    ሶማሊያዊው ዳኛ በዓለም ዋንጫ ላይ እንዳያጫውት መደረጉ ከበርካቶች ዘንድ ተቃመሞን ያስከተለ ሲሆን፣ የአውሮፓ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ግን ሌላ ጨዋታ እንዲዳኝ መርጦታል።

    የ34 ዓመቱ አርታን በነሐሴ ወር በፈረንሳዩ ፓሪስ ሳን ዠርሜን እና በእንግሊዙ አስቶንቪላ መካከል ኦስትሪያ ሳልዝበርግ ውስጥ የሚካሄደውን ግጥሚያ እንዲመራ መመረጡን ፌዴሬሽኑ አረጋግጧል።

    ሶማሊያዊው ዳኛ ከአውሮፓውያኑ 2018 ጀምሮ በዳኝነት በፊፋ የተመዘገበ ሲሆን፣ ባለፈው የአውሮፓውያን ዓመት ደግሞ የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን የዓመቱ ዳኛ ብሎ መርጦታል። በተጨማሪም የዚህ ዓመቱን የዓለም ዋንጫ ከሚዳኙ ዳኞች መካከል አንዱ ነበር።

    አሜሪካ ዳኛውን ወደ ግዛቷ እንዳይገባ በመከልከሏ በዓለም ዋንጫ የማጫወት ዕድሉ የተጨናገፈበነት አርታን ወደ አገሩ ሲመለስ ደማቅ አቀባበል በተደረገለት ጊዜ በቀጣዩ የዓለም ዋንጫ በዳኝነት እንደሚሳተፍ ተስፋውን ገልጿል።

  10. ፕሬዝዳንት ትራምፕ ወሳኙን የኢራን የነዳጅ ማስተላለፊያ ደሴትን በቅርቡ እንደሚቆጣጠሩ አስታወቁ

    ኻርግ ደሴት እና ነዳጅ የሚጭን መርከብ
    የምስሉ መግለጫ, ኻርግ ደሴት ኢራን የነዳጅ ምርቷን ለገበያ የምታቀርብበት መሠረተ ልማት አለው

    የኢራን እና የአሜሪካ ግጭት ከዕለት ወደ ዕለት እየተባባሰ ባለበት በአሁኑ ወቅት ፕሬዝዳንት ትራምፕ በቅርቡ አሜሪካ የኻርግ ደሴትን እንደምትቆጣጠር አስታወቁ።

    ትራምፕ ጨምረውም ለአራተኛ ቀን በኢራን ላይ ከባድ ጥቃት እንደሚፈጸም ካስጠነቀቁ ከሰዓታት በኋላ የጥቃት ሃሳባቸውን መልሰው መቀልበሳቸውን አሳውቀዋል።

    ፕሬዝዳንቱ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ “ባሕር ኃይሏ፣ የአየር ኃይሏ፣ የአየር መከላከያ ሥርዓቷ እና ሁሉም የጥቃት አቅሟ” ወድሟል ያሏት ኢራንን ዳግም “ሌሊት በኃይለኛው ትመታለች” ብለው ነበር።

    "ቬንዙዌላ ላይ እንዳደረግነው ብዙም ሳይቆይ የኻርግ ደሴትን እና ሌሎች የነዳጅ መሠረተ ልማቶችን እንይዛለን፤ በዚህም የኢራንን የነዳጅ እና የጋዝ ገበያን ሙሉ ለሙሉ እንቆጣጠራለን” ሲሉ ዕቅዳቸውን አሳውቀዋል።

    ከኢራን ጋር የሚደረገው ጦርነት ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ ፕሬዝዳንት ትራምፕ የኢራን ዋነኛው የነዳጅ ማስተላለፊያ የሆነውን ኻርግ ደሴትን እንደሚቆጣጠሩ በተደጋጋሚ ሲናገሩ ነበር።

    በሰሜናዊ የባሕረ ሰላጤው አካባቢ የሚገኘው ኻርግ ደሴት ኢራን ወደ 90 በመቶ የሚሆነውን የነዳጅ ምርቷን ለቀሪው ዓለም የምታቀርብበትት ዋና መተላለፊያ ነው።

    ደሴቱ ከኢራን የባሕር ዳርቻ አቅራቢያ የሚገኝ ሲሆን፣ ወደ ሁለት ሚሊዮን በርሜል መጫን የሚችሉ ግዙፍ ድፍድፍ ነዳጅ ጫኝ መርከቦች ላይ ነዳጅ ለመሙላት የሚያስችል ጥልቅ የውሃ ክፍል አለው።

  11. የኢራን ጥቃት በባሕረ ሰላጤው አገራት ላይ ጉዳት አደረሰ

    የኢራን ጥቃት በባህሬን ያደረሰው ጉዳት

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የኢራን ጥቃት በባህሬን ያደረሰው ጉዳት

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ አሜሪካ በደቡባዊ ኢራን ውስጥ ለፈጸመችው ጥቃት በባህሬን፣ በኩዌት እና በዮርዳኖስ በሚገኙ የጦር ሰፈሮቿ ላይ ጥቃት መፈጸሙን አረጋግጧል።

    የባህሬን መገናኛ ብዙኃን እንደዘገቡት ዛሬ ሐሙስ ጠዋት በተፈጸመው የኢራን የድሮን ጥቃት አንዲት የ11 ዓመት ታዳጊ ጉዳት ደርሶባታል።

    የአሜሪካ ባሕር ኃይል ሰፈር በሚገኝባት ባህሬን ላይ ኢራን በፈጸመችው ጥቃት ቤቶች እና መኪኖች መውደማቸውን የአገሪቱ ባለሥልጣናት አስታውቀዋል።

    ዮርዳኖስ ከኢራን የተተኮሱ 20 ሚሳዔሎችን መትታ መጣሏን ስትገልጽ፣ የኩዌት ጦር ኃይል ደግሞ ከኢራን የተወነጨፉ መሳሪያዎችን አየር ላይ ማስቀረቱን አስታውቋል።

    የባህሬን እሳት አደጋ ሠራተኞች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የባህሬን እሳት አደጋ ሠራተኞች
    የኢራን ጥቃት በባህሬን ያደረሰው ጉዳት

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የኢራን ጥቃት በባህሬን ያደረሰው ጉዳት
  12. አሜሪካ በኦማን ባሕረ ሰላጤ የኢራን መርከብ ላይ ጥቃት መፈፀሟ ተነገረ

    የነዳጅ እና ዕቃ ጫኝ መርከቦች ከኦማን ሙሳንዳም በሆርሙዝ ባህር ዳርቻ ላይ ቆመው ይገኛሉ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የነዳጅ እና ዕቃ ጫኝ መርከቦች ከኦማን ሙሳንዳም በሆርሙዝ ባህር ዳርቻ ላይ ቆመው ይገኛሉ

    አሜሪካ ወሳኝ እቃዎችን የጫነች መርከብ ላይ ዛሬ ጠዋት ጥቃት መፈፀሟን ሪፖርት አመለከተ።

    በኢራን መንግሥታዊ የዜና ወኪል መህር ኒውስ የጠቀሳቸው የሲሪክ አስተዳዳሪ ጥቃቱ በኦማን ባሕረ ሰላጤ መፈፀሙን ተናግረዋል።

    ከቅጽበታዊው ጥቃት አምስት መርከበኞችን መታደግ ተችሏልም ብለዋል።

    መርከቧ ጥቃት የተፈፀመባት ከኦማን ኻሳብ ከተማ ወደ ኢራን ከተማ - ሲሪክ ለመጓዝ ከተነሳች በኋላ ነበር።

    ጥቃቱን በተመለከተ አሜሪካ እስካሁን ያለችው ነገር የለም።

  13. ካናዳ ታዳጊዎች ማኅበራዊ ሚዲያ እንዳይጠቀሙ እገዳ ልትጥል ነው

    ረቂቅ ሕጉ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የቀረበው ከቡድን ሰባት አገራት ስብሰባ ቀደም ብሎ ነው

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ካናዳ ከ16 ዓመት በታች ለሆኑ ታዳጊዎች የማኅበራዊ ሚዲያን ለማገድ የሚያስችል ሕግ አቀረበች።

    ሕጉ ባለፈው ዓመት በአውስትራሊያ ከጸደቀው ጋር ተመሳሳይ ነው ተብሏል።

    ነገር ግን ከአውስትራሊያው ሕግ በተለየ የቴክኖሎጂ ኩባንያዎች ታዳጊዎቹን ለመከላከል የሚያስችል ፖሊሲዎች ካሏቸው ግዴታ ውስጥ አይገቡም።

    ሕጉ የሰው ሠራሽ ቻትቦቶች እንዲሁም በኦንላየን “ያሉጎጂ ይዘቶችን” ለመከላከል ሰፊ እርምጃዎችን ይወስዳል ተብሏል።

    ተቆጣጣሪዎች የቴክኖሎጂ ኩባንያዎች ሕጉን ማክበራቸውን እንዲከተተሉ ያደርጋል።

    አንዳንድ የመናገር ነጻነት አቀንቃኞች ሳንሱርን ያስፋፋል ሲሉ ስጋታቸውን ገልጸዋል።

    ሕጉ ለምክር ቤት የቀረበው በሚቀጥለው ሳምንት በፈረንሳይ ከሚካሄደው የቡድን ሰባት አገራት ስብሰባ በፊት ነው።

    ይህ ደህንነቱ የተጠበቀ የማኅበራዊ ሚዲያ ረቂቅ ሕግ ረቡዕ ዕለት በባህል ሚኒስትር ማርክ ሚለር ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀርቦ ነበር።

    በሳምንቱ መጀመሪያ ላይ ሚለር እንዳሉት “ልጆች እየሞቱ በመሆኑ” በኦንላየን የሚደርሱ ጉዳቶችን የሚመለከት ሕግ ማውጣትን የካናዳ መንግሥት ቅድሚያ የሚሰጠው ጉዳይ ነው።

    “ልጆች በዚህች አገር ደህንነታቸው የተጠበቀ መሆኑን ለማረጋገጥ ሁሉንም ተገቢ እርምጃዎች እንወስዳለን ማለት በቂ ነው” ሲሉ ለጋዜጠኞች ተናግረዋል።

  14. ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥን ሙሉ ለሙሉ ስትዘጋ የነዳጅ ዋጋ ጭማሪ አሳየ

    ካርታ

    አሜሪካ ለሦስተኛ ቀን በኢራን ላይ ጥቃት መፈጸሟን ተከትሎ የኢራን ጦር ኃይል ማዕከላዊ ዕዝ የሆርሙዝ ወሽመጥ ነዳጅ ጫኝ እና የንግድ መርከቦች ጨምሮ ለሁሉም የባሕር ላይ እንቅስቃሴ ዝግ መሆኑን አስታወቀ።

    ባለፉት ቀናት አሜሪካ እና ኢራን ጥቃት ሲፈጽሙ የቆዩ ሲሆን፣ አሜሪካ በኢራን ውስጥ የሚገኙ ዒላማዎችን ስትመታ ኢራን በአጸፋው በፋርስ ባሕረ ሰላጤ አገራት ውስጥ በሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሰፈሮች እና በእስራኤል ላይ ጥቃት ፈጽማለች።

    ረቡዕ ሌሊት በአሜሪካ የተፈጸመውን ጥቃት ተከትሎ ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥን ከዘጋች በኋላ አብዮታዊ ዘቡ በሕገወጥ መንገድ ለማለፍ ሞክረዋል ያላቸውን ሁለት መርከቦችን መምታቱን አስታውቋል።

    የኢራን ወታደራዊ ማዘዣ የሆነው ኻታም አል-አምቢያ እንዳስታወቀው “በቀጣናው ባለው አለመረጋጋት ምክንያት የሆርሙዝ ወሽመጥ ለሁሉም መርከቦች ተዘግቷል” በማለት ለማለፍ የሚሞከሩ መርከቦች ላይ እርምጃ እንደሚወሰድ አስታውቋል።

    የወሳኙ የባሕር መተላለፊያ መዘጋት ለወራት ጋብ ብሎ የነበረው የአሜሪካ እና ኢራን ጦርነት እየተባባሰ መሆኑን የሚያመለክት ነው። ከፍተኛ መጠን ያለው የዓለም የነዳጅ ፍጆታ የሚተላለፍበት ወሽመጥ በመዘጋቱ የነዳጅ ዋጋ ላይ ጭማሪ ተከስቷል።

    ጦርነቱ በየካቲት ወር መጨረሻ ገደማ ከተቀሰቀሰ በኋላ ኢራን ሆርሙዝን ሙሉ ለሙሉ ከመዝጋት ይልቅ በመርከቦች እንቅስቃሴ ላይ ገደቦች ጥላ ቁጥጥር ስታደርግ ነበር። በተጨማሪም የባሕር መተላለፊያውን የሚመለከት አዲስ ሕግ እና አሠራር በማውጣት ሆርሙዝን በቁጥጥሯ ስር ለማስገባት ስትሠራ ቆይታለች።

    ይህ የኢራን ውሳኔ የተሰማው ኢራን የአሜሪካ የጦር ሄሊኮፕተርን መትታ ከጣለች በኋላ ከአሜሪካ ተደጋጋሚ ጥቃት ስለተፈጸመባት ነው።

    ሆርሙዝ ወሽመጥ ዓለም ለፍጆታው ከሚያስፈልገው 20 በመቶው ነዳጅ ዘይት እና ጋዝ ከባሕረ ሰላጤው አገራት በመነሳት በየቀኑ የሚተላለፍበት ወሳኝ የባሕር መስመር ነው።

  15. እስራኤል በደቡባዊ ሊባኖስ በፈፀመችው ጥቃት በርካቶች መገደላቸው ተዘገበ

    በቆሙ መኪኖች ላይ የተነሳ እሳት

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, በደቡባዊ ሊባኖስ ሲደን ከተማ በመኪና ላይ በተፈፀመ ጥቃት ሁለት ሰዎች መገደላቸው ተዘግቧል

    እስራኤል ትናንት በደቡባዊ ሊባኖስ በፈፀመችው ጥቃት ቢያንስ 17 ሰዎች መገደላቸውን የሊባኖስ መገናኛ ብዙኃን ዘገበ።

    ኤንኤንኤ እንደዘገበው ዘጠኙ ሰዎች የተገደሉት ታይር ደባ በተባለው ከተማ ውስጥ ነው።

    በዲየር ቃኖን ኤል ናህር መንደር አቅራቢያ እስራኤል በፈፀመችው ሁለት የአየር ድብደባዎች ሌሎች ሦስት ሰዎች የተገደሉ ሲሆን ሁለት ሰዎች ደግሞ በደቡባዊ ምሥራቅ ታይር በምትገኘው ሴዲቂን ተገድለዋል።

    በኋላ ላይም በሲደን ከተማ እና ማሳክን አል ሻቢያ አካባቢ በተፈፀሙ ጥቃቶች ሦስት ሰዎች መገደላቸው ተገልጿል።

    በኢራን የሚደገፈው ታጣቂ ቡድን ሄዝቦላህ በበኩሉ በእስራኤል ወታደሮች ላይ ተጨማሪ ጥቃቶችን መፈፀሙን እና የአገሪቷን ደቡባዊ ክፍል መቆጣጠሩን ገልጿል።

    ማክሰኞ ዕለትም በእስራኤል ጥቃት 15 ሰዎች መገደላቸው የተገለጸ ሲሆን እስራኤል በሄዝቦላህ ላይ የምታደርገውን ዘመቻ መቀጠል እንድታቆም ከኢራን የተሰጣትን ማስጠንቀቂያ ውድቅ አድርጋለች።

    የኢራን መሪዎች ጦርነቱን ለማቆም ከአሜሪካ እና እስራኤል ጋር የሚደረገው ማንኛውም ስምምነት ሊባኖስን እንዲያካትት ይፈልጋሉ። ይህም ከአሜሪካው ፕሬዚደንት ትራምፕ ጋር የሚደረገውን ድርድር አወሳስቦታል።

    የሊባኖስ መገናኛ ብዙኃን እንደዘገበው የእስራኤል የአየር እና የከባድ መሣሪያ ጥቃት ረቡዕ ዕለትም በአገሪቷ ደቡባዊ ክፍል የተለያዩ ከተሞች እና መንደሮች ላይም ተጠናክሮ ቀጥሏል።

    እስራኤል የረቡዕ ዕለቱን ጥቃት በተመለከተ ወዲያውኑ የሰጠችው አስተያየት የለም። ሆኖም ቀደም ብሎ በታይር ሄዝቦላህ የሚጠቀምባቸውን ስድስት መሠረተ ልማቶች እና በበርካታ የደቡባዊ ሊባኖስ አካበቢዎች የሚገኙ መሣሪያዎቹን እንዳወደመች ገልጻለች።

  16. አሜሪካ አዲስ ጥቃት ከፈጸመች በኋላ ኢራን በባሕረ ሰላጤው የሚገኙ የጦር ሰፈሮችን ዒላማ አደረገች

    ሴንቲኮም በኢራን ላይ በፈጸመው ጥቃት የተከሰተ ፍንዳታ

    የፎቶው ባለመብት, US Central Command

    ዶናልድ ትራምፕ ኢራንን “ክፉኛ” እንደበድባታለን ማለታቸውን ተከትሎ የአሜሪካ ጦር ጥቃት በመፈጸሙ ቴህራን በባሕረ ሰላጤው በሚገኙ ጦር ሰፈሮች ላይ የአጸፋ እርምጃ ወሰደች።

    የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም) ፕሬዚዳንት ትራምፕ ኢራን ጦርነቱን ለማቆም የሚያስችል “ስምምነትን ለመቀበል ብዙ ጊዜ ፈጀች” ካሉ በኋላ ለተከታታይ ሁለት ቀናት “ራስን የመከላከል ጥቃቶችን” መፈጸሙን አስታውቋል።

    በምላሹ ኢራን በባሕሬን፣ ኩዌት የሚገኙ የጦር ሰፈሮች ላይ ጥቃት መፈጸሟን አስታውቃለች።

    እነዚህ ጦር ሰፈሮች ከዚህ ቀደምም ተመሳሳይ የአጸፋ እርምጃ የወሰደችባቸው ናቸው።

    ሁለቱ አገራት እርስ በእርስ የሚያደርጉት መታኮስ በሚያዚያ ወር የተደረሰውን የተኩስ አቁም አደጋ ላይ ጥሎታል።

    አሜሪካ የቴህራን የአየር መከላከያዎችን፣ ራዳሮችን እና ሌሎች ተቋማት ላይ ድብደባ ከፈጸመች በኋላ በአገሪቱ ደቡባዊ ክፍል በሆርሙዝ አቅራቢያ አካባቢ ፍንዳታ ተሰምቷል።

    የእስላማዊ አብዮታዊ ዘብ በበኩሉ በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚያልፉ ሁለት የነዳጅ መርከቦች ላይ ጥቃት መፈጸሙን የኢራን መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    ስለ ጥቃቱ ወዲያውኑ ማረጋጋጫ የሰጠ አካል የለም።

    ይህ የተከሰተው የኢራን መገናኛ ብዙኃን የሆርሙዝ ወሽመጥ “ለማንኛውም ዓይነት መርከብ ሙሉ በሙሉ ዝግ መሆኑን” ካስታወቁ በኋላ ነው።

    ሴንትኮም ግን “የንግድ መርከቦች በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል እያለፉ ነው” ሲል መግለጫ ሰጥቷል።

    በወሽመጡ የሚያልፉ መርከቦች ላይ ጥቃት ከደረሰ እና መስመሩ ሙሉ በሙሉ ዳግም ከተዘጋ በኋላ የነዳጅ ዋጋ ጭማሪ አሳይቷል።

    በእስያ ገበያ ዛሬ ማለዳ ብሬንት ድፍድፍ ነዳጅ ዘይት በበርሜል የ2 በመቶ ጭማሪ በማሳየት 95 ዶላር መሸጥ ጀምራል።

    የተባበሩት መንግሥታት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ መካከለኛው ምሥራቅ “ወደ ማይወጣው ቀውስ ውስጥ እየገባ ነው” ሲሉ አስጠንቅቀው በቅርብ ጊዜ የተከሰቱት ግጭቶች “የተኩስ አቁሙ የተኩሱን መጠን መቀነስ ብቻ ላይ አስተዋጽኦ ያደረገ ይመስላል” ብለዋል።

    “የተኩስ መጠኑን መቀነስ ወደ ሙሉ ጦርነት እንዲሻገር ማድረግ የለብንም። ሁሉም ወገኖች ወደ ዲፕሎማሲያዊ መፍትሄ መምጣት አለባቸው። ተጨማሪ ጥቃት አያስፈልግም። ከዚህ በኋላ ምንም ሰበብ አያስፈልግም” ሲሉ በመግለጫቸው ላይ ጠቅሰዋል።

  17. አሜሪካ በባሕረ ሰላጤው የነዳጅ መርከብ መምታቷን ካስታወቀች በኋላ ሦስት የሕንድ መርከበኞች ጠፉ

    የአሜሪካ ማዕከላዊ እዝ አወደምኩት ያለው የመርከቧ የሞተር ክፍል የሚያሳይ ምሥል

    የፎቶው ባለመብት, Centcom

    የምስሉ መግለጫ, የአሜሪካ ማዕከላዊ እዝ አወደምኩት ያለውን የመርከቧን የሞተር ክፍል የሚያሳይ ምሥል አጋርቷል።

    የአሜሪካ ጦር "ከኢራን ነዳጅ ለማጓጓዝ ሙከራ በማድረግ የአሜሪካን እገዳ ጥሷል" የተባለ የነዳጅ መርከብን በባሕረ ሰላጤዋ ኦማን አወደመች።

    የአሜሪካ ማዕከላዊ እዝ በኤክስ ገጹ ባሰፈረው ጽሑፍ መርከበኞቹ ከአሜሪካ የተሰጣቸውን አቅጣጫ በተደጋጋሚ ማክበር ባለመቻላቸው የጦር አውሮፕላኑ "የፓላውን ሰንደቅ ዓላማ በምታውለበልበው ሴትቤሎ መርከብ" በሞተሯ ክፍል ላይ ጥቃት በመፈፀም ማውደሙን ገልጿል።

    በኦማን ባሕር ዳርቻ ሴትቤሎ ላይ ጥቃት ከተፈፀመ በኋላ የሕንድ መንግሥት ሦስት መርከበኞቹ እንደጠፉ እና 21 ሕንዳውያን የመርከበኞች ቡድን መታደግ መቻሉን ገልጿል።

    “በቀጠናው የንግድ መርከቦች እና የሲቪል መሠረተ ልማቶች ላይ የሚፈፀመው ጥቃት ሊቆም ይገባል" ብሏል።

    ቴህራን የሆርሙዝ ወሽመጥን ከዘጋች በኋላ የአሜሪካ ጦር የኢራንን ወደብ አገልግሎት እንዳይሰጥ አግዷል።

    ወሽመጡ 20 በመቶ የሚሆን የዓለም ነዳጅ እና ጋዝ የሚጓጓዝበት መስመር ነው።

    የአሜሪካ ጦር እገዳ ከጣለ አንስቶ ስምንት መርከቦችን ያወደመ ሲሆን ሌሎች 134 መርከቦችን ደግሞ አቅጣጫ እንዲለውጡ ማድረጉን ማዕከላዊ እዟ አስታውቋል።

  18. ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ “ዛሬም ኢራንን ክፉኛ እንመታለን” አሉ

    ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ዛሬ ረቡዕ ባደረጉት ንግግር ኢራንን “ክፉኛ እንመታለን” ሲሉ ዛቱ።

    ፕሬዝዳንቱ እንዳሉት ሁለቱ አገራት የሰላም ስምምነት ላይ ለመድረስ “ቢቃረቡም” ኢራን “መዘግየቷን” ጠቅሰዋል።

    “ትናንት በጣም ደብድበናቸዋል። ዛሬም ክፉኛ እንመታቸዋለን” በማለት ፕሬዝዳንቱ አስጠንቅቀዋል።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ኢስማኤል ባጋይ “የትኛውንም ጥቃት ወይም ዛቻ ችላ ብለን አናልፍም” ብለዋል።

    ትራምፕ ግን ኢራን ድርድሩን “በጣም በማጓተቷ አሁን ዋጋውን ትከፍላለች” ሲሉ ተናግረዋል።

    “የኢራን ጦር ተዳክሟል። የባሕር እና የአየር ኃይላቸው አለ ለማለት አያስደፍርም። ሙሉ በሙሉ ወድቀዋል” በማለት በትሩዝ ሶሻል የማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ጽፈዋል።

    ኢራን የአሜሪካ ተዋጊ ሄሊኮፕተርን መትታ መጣሏን ተከትሎ አሜሪካ የአጸፋ እርምጃ ወስዳለች።

    በምላሹም ኢራን በባሕረ ሰላጤው አገራት የሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሰፈሮችን ዒላማ ያደረጉ የሚሳዔል እና የድሮን ጥቃቶችን መፈጸሟን አስታውቃለች።

  19. እስራኤል በሊባኖስ በፈጸመችው የአየር ጥቃት ቢያንስ 17 ሰዎች መገደላቸው ተዘገበ

    ደቡብ ሊባኖስ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    እስራኤል በደቡብ ሊባኖስ ውስጥ በፈጸመችው የአየር ጥቃት ቢያንስ 17 ሰዎች መገደላቸውን የአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ።

    የሊባኖስ ብሔራዊ የዜና አገልግሎት እንደዘገበው ታይር ዳባ በተባለ አካባቢ በተከታታይ በተፈጸመ ጥቃት ዘጠኝ ሰዎች ተገድለዋል።

    ኢራን የምትደግፈው ሄዝቦላህ በደቡብ ሊባኖስ የእስራኤል ወታደሮች በተቆጣጠሯቸው አካባቢዎች ተጨማሪ ጥቃቶች መፈጸሙን አስታውቋል።

    ትናንት ማክሰኞ እስራኤል በሊባኖስ በፈጸመችው ጥቃት 15 ሰዎች መገደላቸውም ተዘግቧል።

    እስራኤል በሄዝቦላህ ላይ የከፈተችውን ዘመቻ እንዳትገፋበት ኢራን ብታሳስብም እስራኤል ጥቃት መፈጸሟን ቀጥላለች።

    ኢራን ከአሜሪካ ጋር ያለው ጦርነት የሚያከትመው ስምምነታቸው ሊባኖስን የሚያካትት ከሆነ ብቻ መሆኑን ገልጻለች። ድርድሩን የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ውስብስብ አድርገውታል ስትልም ከስሳለች።

    ትራምፕ በበኩላቸው ኢራን ድርድሩን “በጣም በማጓተቷ አሁን ዋጋውን ትከፍላለች” ሲሉ ዝተዋል።

    ኢራን የአሜሪካ ተዋጊ ሄሊኮፕተርን መትታ መጣሏን ተከትሎ አሜሪካ የአጸፋ እርምጃ ወስዳለች።

    በምላሹም ኢራን በባሕረ ሰላጤው አገራት የሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሰፈሮችን ዒላማ ያደረጉ የሚሳዔል እና የድሮን ጥቃቶችን መፈጸሟን አስታውቃለች።

  20. ኢራን ከአሜሪካ ጋር የምታደርገው ድርድር የሚቀጥልበትን መንገድ እንደምታጤን አስታወቀች

    ኢስማኤል ባጋይ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ፤ ቴህራን ከዋሽንግተን ጋር የምታደርገው ድርድር የሚቀጥልበትን መንገድ እንደምታጤነው አስታወቁ።

    ኢራን የአሜሪካን ሄሊኮፕተር መትታ መጣሏን ተከትሎ አሜሪካ የአጸፋ እርምጃ ወስዳለች።

    ቃል አቀባዩ ኢስማኤል ባጋይ፤ ኢራን እና አሜሪካ የተኩስ ልውውጥ ማድረጋቸውን ተከትሎ “ዲፕሎማሲ በባቦ ሜዳ አይከናወንም። የዲፕሎማሲ ሒደት እንዲቀጥል ለማስቻል በተወሰነ መጠን ለእንቅስቃሴ ክፍተት መስጠት ያስፈልጋል” ብለዋል።

    አሜሪካ “የሚቃረኑ መልዕክቶች በማስተላለፍ የድርድር ሒደቱን እየጎዳች ነው” ሲሉ ወንጅለዋል። “አቋም እና ፍላጎት በመለወጥ” እንዲሁም “በተደጋጋሚ የተኩስ አቁም በመጣስም” አሜሪካን ከስሰዋል።