የአሜሪካ ጠቅላይ አቃቤ ሕግ ተጠርጣሪው ፕሬዚዳንቱን ጨምሮ ባለሥልጣኖቻቸውን ዒላማ ማድረጉን ተናገሩ

በአሜሪካ የቢቢሲ አጋር የሆነው ሲቢኤስ በዋይት ሐውስ ዘጋቢዎች የእራት ግብዣ ላይ ተኩስ ከፍቶ በቁጥጥር ሥር የዋለው ተጠርጣሪ ለመርማሪዎች ፕሬዚዳንት ትራምፕ ዒላማው እንደነበሩ መናገሩን ዘገበ። ሲቢኤስ በስም ያልጠቀሳቸውን ምንጮች በእራት ግብዣው ላይ ከአምስት እስከ ስምንት የሚደርሱ ጥይቶች ተተኩሰዋል ብለዋል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ‘የመጀመርያ ደረጃ ግኝቶች’ የሚጠቁሙት ተጠርጣሪው ‘የአስተዳደሩን ባለሥልጣናት’ ዒላማ ማድረጉን ነው- አቃቤ ሕግ

    የአሜሪካ ጠቅላይ አቃቤ ሕግ ቶድ ብላንቼ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የአሜሪካ ጠቅላይ አቃቤ ሕግ ቶድ ብላንቼ

    የአሜሪካ ጠቅላይ አቃቤ ሕግ ቶድ ብላንቼ በዋይት ሐውስ ዘጋቢዎች የእራት ግብዣ ላይ ተኩስ የከፈተው ተጠርጣሪ ምርመራ እንደቀጠለ ነው አሉ።

    ነገር ግን “የመጀመርያ ደረጃ” ግኝቶች ዒላማ ያደረገው የአስተዳደሩን ባለሥልጣናት እንደሆነ እና ይህም ፕሬዚዳንቱንም ሊያካትት ‘እንደሚችል’ እንደሚያሳዩ ተናግረዋል።

    ጠቅላይ አቃቤ ሕጉ ለኤንቢሲ እንደተናገሩት መርማራዎች ተጠርጣሪው መሣሪያውን የገጣጠመው በሆቴሉ ውስጥ ነው የሚለውን እያጣሩ መሆኑን አስታውቀዋል።

    አክለውም ተጠርጣሪው “ብዙም ርቀት መሄድ አልቻለም” ብለዋል።

    “በጣም በትንሹ ነው ደህንነቶችን ያለፈው” ያሉት ብላንቼ ተጠርጣሪው ከሎስ አንጀለስ ወደ ቺካጎ እናም ወደ ዋሺንግተን በባቡር ተጉዞ ሊሆን ይችላል ብለዋል።

    ጠቅላይ አቃቤ ሕጉ ተጠርጣሪው ላይ ሰኞ ክስ እንደሚመሰረት አረጋግጠዋል።

    ብላንቼ ከሲቢኤስ ጋር በነበራቸው ቃለ ምልልስ ወቅት ተጠርጣሪው ለመርማሪዎች ትብብር ለማድረግ ፈቃደኛ ሳይሆን መቅረቱን ተናግረዋል።

  2. በዋይት ሐውስ ዘጋቢዎች የእራት ግብዣ ላይ ስለነበረው ተኩስ የማናውቃቸው ጉዳዮች

    የዋይት ሐውስ ዘጋቢዎች የእራት ግብዣ ላይ የተገኙ ሰዎች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ምንም እንኳ ቅዳሜ ምሽት በዋይት ሐውስ በነበረው የእራት ግብዣ ላይ ስለተፈጠረው ተኩስ እንዲሁም የተጠርጣሪውን መያዝ ብናውቅም አሁንም ያልተመለሱ ጥያቄዎች አሉ።

    • ·በአሜሪካ የቢቢሲ አጋር የሆነው ሲቢኤስ ተጠርጣሪው ለፖሊስ የትራምፕ አስተዳደር ሰዎችን ዒላማ ማድረጉን ቢናገርም የሕግ አስከባሪዎች ግን ጥቃቱን ለመፈጸም ያነሳሳው ምክንያት መረጋገጥ አለበት ብለዋል።
    • የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን ወንጀሉን የፈጸመው ሰው ኮሌ ቶማስ አለን እንደሚባል በመግለጽ ቢዘግቡም ፖሊስ ግን እስካሁን ድረስ በይፋ ስለማንነቱ ያለው ነገር የለም።
    • ተጠርጣሪው በርካታ የጦር መሣሪያዎችን መያዙን ፖሊስ ተናግሯል። የተለቀቁ የደህንነት ካሜራ ምስሎች ግለሰቡ የደህንነት ሰዎችን አልፎ ሲሮጥ አሳይተዋል። በእራት ግብዣው ላይ የደህንነት ሁኔታው ምን ያህል የተጠናከረ ነበር የሚለው አሁንም መመለስ ያለበት ጥያቄ ሆኗል።
    • የዋይት ሐውስ ዘጋቢዎች የእራት ግብዣ በሚቀጥሉት 30 ቀናት ውስጥ ወደ ሌላ ጊዜ እንደሚተላለፍ ቢገለጽም ቀኑ እስካሁን ድረስ በትክክል አልታወቀም።
  3. ንጉሡ ወደ አሜሪካ ከመጓዛቸው በፊት ተጨማሪ የደህንነት ውይይቶች ይደረጋሉ - ዩኬ

    የዩናይትድ ኪንግደም ጠቅላይ ሚንስትር ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ዳረን ጆንስ

    የፎቶው ባለመብት, Jeff Overs/BBC

    የዩናይትድ ኪንግደም ጠቅላይ ሚንስትር ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ዳረን ጆንስ ንጉሡ ወደ አሜሪካ ከመጓዛቸው በፊት “ዛሬ ተጨማሪ [የደህንነት] ውይይት ይከናወናል” አሉ።

    ንጉሥ ቻርልስ ሳልሳዊ እና ንግሥት ካሚላ ከሰኞ ጀምሮ ለአራት ቀናት ጉብኝት ወደ አሜሪካ ይጓዛሉ።

    ትናንት ማታ በዋሽንግተን የነበረውን ተኩስ ተከትሎ የደህንነት ጥበቃው በተመለከተ ከቢቢሲ ለቀረበላቸው ጥያቄ “ከጉዳዩ ጋር በተያያዘ ተገቢው ደህንነት ይኖራል" ብለዋል።

    ከትናንትናው ክስተት በፊትም ቢሆን መንግሥት እና ቤተ መንግሥቱ ከአሜሪካ አቻዎቻቸው ጋር በቅርበት በመስራት ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል።

    የጎንዮሽ የአገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትር ክሪስ ፊሊፕ በበኩላቸው ንጉሱ በአግባቡ መጠበቃቸውን ማረጋገጥ "አስፈላጊ" ነው ብለዋል። ጉብኝቱ “መከናወን” አለበት ምክንያቱም ዓመፅ የዲፕሎማሲ ግንኙነቶችን እንዲያቆም መፈቀድ የለበትም ሲሉ አክለዋል።

    ደህንነቱ "በአስቸኳይ መገምገም አለበት" ካሉ በኋላ ለእነዚህ ጉዞዎች ብዙውን ጊዜ ጥበቃው በጣም ጥብቅ እንደሆነም አክለዋል።

    በአሜሪካ የቀድሞ የዩኬ አምባሳደር ኪም ዳሮች በዋይት ሐውስ ዘጋቢዎች የእራት ግብዣ ላይ ስለነበረው የተኩስ ልውውጥ ለቢቢሲ ሲናገሩ በዝግጅቱ ላይ "የደህንነት ችግሮች" አሉ ብለዋል።

    ወደ ሕንፃው ለመግባት “የግብዣ ካርድን ማሳየት ብቻ ነው" ያሉት አምባሳደሩ ከዚያም ወደ አዳራሹ ለመግባት የበር ፍተሻ ማሽንን ማለፍ እና ቦርሳ ማስተፈተሽ ብቻ ነበር ብለዋል።

    “ነገር ግን ሆቴል ነው፤ እናም ሆቴሉ በእንግዶች የተሞላ ነው" ሲሉ አክለዋል።

    "መጥፎ ዓላማ ላለው ሰው ማለፍ የሚያስፈልገው አንድ የደህንነትን መቆጣጠሪያን ብቻ ነው" ሲሉ በስፍራው የነበረውን ልል የደህንነት ሁኔታ አብራርተዋል።

  4. በዋይት ሐውስ ዘጋቢዎች የእራት ግብዣ ላይ ተኩስ ስለከፈተው ተጠርጣሪ ምን እናውቃለን?

    ዶናልድ ትራምፕ በማኅበራዊ ድረ ገጻቸው ላይ ያጋሩት የተጠርጣሪው ምስል

    የፎቶው ባለመብት, @REALDONALD TRUMP / TRUTHSOCIAL

    የምስሉ መግለጫ, ዶናልድ ትራምፕ በማኅበራዊ ድረ ገጻቸው ላይ ያጋሩት የተጠርጣሪው ምስል

    ተጠርጣሪው በቁጥጥር ሥር የዋለው ቅዳሜ ምሽት የዋሺንግተን ዘጋቢዎች የእራት ግብዣ በሚካሄድበት ሆቴል ውስጥ ተኩስ ከከፈተ በኋላ ነው።

    በአሜሪካ የቢቢሲ አጋር የሆነው ሲቢኤስ ተጠርጣረው ስሙ ኮል ቶማስ አለን እንደሚባል ዘግቧል።

    የ31 ዓመቱ ተጠርጣሪ ቶረንስ በሎስ አንጀለስ ካሊፎርኒያ ነዋሪ ነው ተብሏል።

    ሲቢኤስ ግለሰቡ በቁጥጥር ሥር ከዋለ በኋላ ለሕግ አስከባሪ አካላት በትራምፕ አስተዳደር ውስጥ ያሉ ባለሥልጣናትን ተኩሶ ለመምታት ፈልጎ እንደነበር መናገሩን ዘግቧል።

    ሲቢኤስ ምንጮችን ጠቅሶ እንደዘገበው ከአምሰት እስከ ስምንት ጊዜ ተኩሷል።

    በአካባቢው የሚገኙ የደህንነት ካሜራዎች ተጠርጣሪው የደህንነት አባላትን ሮጦ ሲያመልጥ እና ሲከተሉት ያሳያል።

    ፖሊስ ከጥቃቱ በኋላ በሰጠው መግለጫ የደህንነት አባላት እና ግሰለሰቡ መካከል የተኩስ ልውውጥ ነበር።

    የዋሺንግተን ጊዜያዊ የፖሊስ ሃላፊ ጄፍሪ ካሮል ተጠርጣሪው በጥይት እንዳልተመታ ገልጸው ነገር ግን ወደ ሆስፒታል ለተጨማሪ ምርመራ መወሰዱን ተናግረዋል።

    ተጠርጣሪው በዋሺንግተን ሒልተን ሆቴል እንግዳ እንደነበር የተገለጸ ሲሆን “የጦር መሣሪያ፣ ከበርካታ ቢላዎች ጋር” ታጥቆ ነበር ተብሏል።

    ፖሊስ አሁን ባሉት ማስረጃዎች ተጠርጣሪው ብቻውን መንቀሳቀሱን አስታውቋል።

  5. በዋይት ሐውስ ጋዜጠኞች የእራት ግብዣ ላይ ተኩስ ሲከፈት የተፈጠረውን ትርምስ የሚያሳይ ምስል

    የተኩስ ድምጽ ከመሰማቱ በፊት ዶናልድ ትራምፕ ከባለቤታቸው ቀዳማዊት እመቤት ሜላኒያ ትራምፕ እና ከዋይጂያ ጂያንግ የዋይት ሐውስ ዘጋቢዎች ማህበር ፕሬዝዳንት አጠገብ ተቀምጠው ነበር

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የተኩስ ድምጽ ከመሰማቱ በፊት ዶናልድ ትራምፕ ከባለቤታቸው ቀዳማዊት እመቤት ሜላኒያ ትራምፕ እና ከዋይጂያ ጂያንግ የዋይት ሐውስ ዘጋቢዎች ማህበር ፕሬዝዳንት አጠገብ ተቀምጠው ነበር

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በተገኙበት የዋይት ሐውስ ጋዜጠኞች የእራት ግብዣ ላይ ተኩስ ሲከፈት እርሳቸውን ጨምሮ ሌሎች ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት በፍጥነት አካባቢውን እንዲለቅቁ ተደርጓል።

    የእራት ግብዣው ተዘጋጅቶ የነበረው በዋሺንግተን ዲሲ በሚገኘው የሒልተን ሆቴል ነው።

    አንዳንድ የአሜሪካ ከፍተኛ ስም እና ዝና ያላቸው ፖለቲከኞች፣ ዲፕሎማቶች እና ጋዜጠኞች በዋሺንግተን ሒልተን አዳራሽ ውስጥ ተገኝተው ነበር።

    ተኩሱ እንደተሰማ ከጠረጴዛ እና ወንበሮች ስር ለመደበቅ ተገድደዋል።

    የዋይት ሐውስ ዘጋቢዎች የእራት ግብዣ ላይ የተገኙ እንግዶች ጠረጴዛ እና ወንበሮች ስር ተደብቀዋል

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የዋይት ሐውስ ዘጋቢዎች የእራት ግብዣ ላይ የተገኙ እንግዶች ጠረጴዛ እና ወንበሮች ስር ተደብቀዋል
    የደህንነት እና ጸጥታ አባላት ትራምፕ ከመድረኩ ላይ በፍጥነት እንዲወርዱ ሲያደርጉ ሌሎች ወታደሮች ደግሞ አካባቢው ላይ ቅኝት አድርገዋል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የደህንነት እና ጸጥታ አባላት ትራምፕ ከመድረኩ ላይ በፍጥነት እንዲወርዱ ሲያደርጉ ሌሎች ወታደሮች ደግሞ አካባቢው ላይ ቅኝት አድርገዋል
    የአሜሪካ ሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባዔ ማይክ ጆንሰንን ጨምሮ በርካታ ባለሥልጣናት እና እንግዶች በደህንነት አባላት ከአዳራሹ እንዲወጡ ተደርጓል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የአሜሪካ ሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባዔ ማይክ ጆንሰንን ጨምሮ በርካታ ባለሥልጣናት እና እንግዶች በደህንነት አባላት ከአዳራሹ እንዲወጡ ተደርጓል
  6. ከዚህ በፊት ፕሬዚዳንት ትራምፕ ላይ የተሰነዘሩ ጥቃቶች

    ትራምፕ በሐምሌ 2024 የምርጫ ቅስቀሳ ላይ ባሉበት ወቅት የግድያ ሙከራ ተደርጎባቸዋል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ትራምፕ በሐምሌ 2024 የምርጫ ቅስቀሳ ላይ ባሉበት ወቅት የግድያ ሙከራ ተደርጎባቸዋል

    ትራምፕ ለፕሬዚዳንትነት እየተወዳደሩ ባሉበትም ሆነ አገሪቱን እያስተዳደሩ በርካታ የግድያ ሙከራዎች ተደርጎባቸው እንዲሁም ማስፈራሪያዎች ደርሰዋቸው ያውቃሉ።

    እንደ አውሮፓውያኑ በሐምሌ ወር 2024 በፔንሰልቫኒያ የተፈጸመባቸው የግድያ ሙከራ ቀዳሚው ነው። በወቅቱ የምርጫ ተወዳዳሪ የነበሩት ትራምፕ መድረክ ላይ ንግግር በሚያደርጉበት ወቅት መሣሪያ የታጠቀ ግለሰብ ጣሪያ ላይ በመውጣት ተኩስ ከፍቶባቸዋል።

    በወቅቱ አንድ መንገደኛ የተገደለ ሲሆን ትራምፕም ጆሯቸው ላይ ጉዳት ደርሶባቸዋል።

    የደህንነት አባላት የ20 ዓመቱ ተጠርጣሪን ቶማስ ኩክስ ላይ ተኩሰው ገድለውታል።

    ከጥቂት ሳምንታት በኋላ በመስከረም ወር በፍሎሪዳ በሚገኘው የትራምፕ የጎልፍ መጫወቻ ፕሬዚዳንቱን ለመግደል አቅዶ ነበር የተባለ ግለሰብ ከነመሣሪያው ተገኝቷል።

    አቃቤ ሕጎች ርያን ሮት የተባለው ግለሰብ በጥሻ ውስጥ በፕሬዚዳንቱ ላይ መሣሪያ ከማነጣጠሩ አስቀድሞ ለሳምንታት ትራምፕን ለመግደል ሲያሴር ነበር ብለዋል። የደህንነት አባላት ሮት ከመተኮሱ በፊት ማየት በመቻላቸው በቁጥጥር ስር አውለውታል።

    ሮት ፕሬዚዳንቱን ለመግደል በመሞከር ጥፋተኛ ሆኖ በመገኘቱ በየካቲት ወር የእድሜ ልክ እስር ተፈርዶበታል።

    በየካቲት ወር የ21 ዓመቱ ኦስቲን ተከር ማርቲን በፍሎሪዳ በሚገኘው የፕሬዚዳንቱ መኖሩያ በመግባቱ ተተኩሶበት ተገድሏል። ፕሬዚዳንቱ በወቅቱ በመኖሪያ ቤታቸው አልነበሩም ተብሏል።

  7. በዋሺንግተን ዘጋቢዎች የእራት ግብዣ ላይ ስለነበረው ተኩስ የዓለም መሪዎች ምን አሉ?

    የቬንዙዌላ ተጠባባቂ ፕሬዚዳንት ዴልሲ ሮድሪጌዝ

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የቬንዙዌላ ተጠባባቂ ፕሬዚዳንት ዴልሲ ሮድሪጌዝ

    በመላው ዓለም የሚገኙ የዓለም መሪዎች በዋይት ሐውስ ጋዜጠኞች የእራት ግብዣ ላይ በነበረው ተከስ የተሰማቸውን ገልጸዋል።

    የዩኬው ጠቅላይ ሚኒስትር ኪር ስታርመር በዋይት ሐውስ ዘጋቢዎች የእራት ግብዣ ላይ በተፈጠረው “መደንገጣቸውን” ገልጸዋል። “ማንኛውም በዲሞክራሲ ተቋማት ላይ ወይም በፕሬስ ነጻነት ላይ የሚደረግ ጥቃት ጠንካራ በሆነ ሁኔታ መወገዝ አለበት” ሲሉም መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል። ስታርመር ፕሬዚዳንት ትራምፕ፣ ቀዳማይ እመቤት ሜላኒያ ትራምፕ እና ሌሎች በግብዣው ላይ የተገኙ ምንም ዓይነት ጉዳት ስላልደረሰባቸው “ትልቅ እፎይታ” እንደተሰማቸው ገልጸዋል።

    የካናዳው ጠቅላይ ሚኒስትር ማርክ ካርኔ ፕሬዚዳንት ትራምፕ እና ባለቤታቸው እንዲሁም ሌሎች በተኩስ ምንም ባለመሆናቸውን የተሰማቸውን “እፎይታ” ገልጸዋል። አክለውም “በዚህ አስደንጋጭ ክስተት ለተረበሹ ሁሉ ሃሳቤ ከእናንተ ጋር ነው” ብለዋል።

    የአውስትራሊያው ጠቅላይ ሚኒስትር አንቶኒ አልባኔዝ በበኩላቸው በስፍራው የተገኙ ሁሉ “በደህና ሁኔታ” ላይ መሆናቸውን “በመስማቴ ደስተኛ ነኝ” ብለዋል። አክለውም “የደህንነት አባላት እና የሕግ አስከባሪዎች ለሠሩት ስራ አድናቆት አለን” ሲሉ ተናግረዋል።

    የአውሮፓ ኅብረት ከፍተኛ ዲፕሎማት ካጃ ካላስ ለአሜሪካ ፕሬዚዳንት፣ ለቀዳማይ እመቤቷ እና ሌሎች በሥፍራው ለተገኙ ሁሉ ያላቸውን ድጋፍ ገልጸው ”በዲሞክራሲ ውስጥ የፖለቲካ አመጽ ስፍራ የለውም” ብለዋል።

    ኪር ስታርመር

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የቬንዙዌላ ተጠባባቂ ፕሬዚዳንት ዴልሲ ሮድሪጌዝ “የጥቃት ሙከራውን በጥብቅ አወግዛለሁ” ካሉ በኋላ በስፍራው ለተገኙ ሁሉ ያላቸውን “መልካም ምኞት” ገልጸዋል።

    የፓኪስታኑ ጠቅላይ ሚኒስትር ሼህባዝ ሻሪፍ በተኩስ “በጣም መደንገጣቸውን” ገልጸው “ጸሎታቸውን እና ሃሳባቸው” ከትራምፕ ጋር መሆኑን ጠቅሰዋል።

    የሕንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ ለፕሬዚዳንቱ፣ ቀዳማይ እመቤቷ እና ለምክትል ፕሬዚዳንቱ "ለቀጣይ ደህንነታቸው እና ጤንነታቸው መልካም ምኞታቸውን" ገልጸዋል።

    የሜክሲኮ ፕሬዚዳንት ክላውዲያ ሼይንባኡም “አመጽ ምርጫ መሆን የለበትም” ሲሉ መልካም ምኞታቸውን አስተላልፈዋል።

  8. ኤፍቢአይ እና ፖሊስ በካሊፎርኒያ የሚገኘውን የተጠርጣሪውን መኖሪያ ቤት እየፈተሹ ነው

    ኤፍቢአይ እና ፖሊስ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ኤፍቢአይ እና ፖሊስ በዋይት ሐውስ ዘጋቢዎች የእራት ግብዣ ላይ ተኩስ የከፈተው ተጠርጣሪ ጋር የተገናኘ ነው የተባለ ቤት ላይ ፍተሻ እያደረጉ ነው።

    በቴረንስ ካሊፎርኒያ ከፍተኛ የፖሊስ እንቅስቃሴ ይታያል።

    የዋይት ሐውስዘጋቢዎች የእራት ግብዣ በየዓመቱየሚካሄድ ሲሆን ዝነኛ ሰዎች እና ፖለቲከኞች የሚገናኙበት እና ወዳጅነት የሚመሰርቱበት ነው።

    የእራት ግብዣው በሚካሄድበት ሳምንት ኤምባሲዎች፣ ድርጅቶች እና የሚዲያ ተቋማት የየራሳቸውን ድግስ ስለሚያዘጋጁውጥረት ይነግሳል።

    ነገር ግን የእራት ግብዣው በዋናነት የዋይት ሐውስ ዘጋቢዎች ማኅበር የጋዜጠኝነት ተማሪዎች ለመደገፍ የሚያስችለውን ገንዘብ ለማሰባበሰብ የሚያዘጋጀው ነው።

  9. የዋይት ሐውስ ጋዜጠኞች የእራት ግብዣ ላይ ተኩስ የከፈተው ተጠርጣሪ ዒላማው ፕሬዚዳንት ትራምፕ ነበሩ ተባለ

    ዶናልድ ትራምፕ ያጋሩት የተጠርጣሪው ምስል

    የፎቶው ባለመብት, Donald Trump

    በአሜሪካ የቢቢሲ አጋር የሆነው ሲቢኤስ በዋይት ሐውስ ዘጋቢዎች የእራት ግብዣ ላይ ተኩስ ከፍቶ በቁጥጥር ሥር የዋለው ተጠርጣሪ ለመርማሪዎች ፕሬዚዳንት ትራምፕ ዒላማው እንደነበሩ መናገሩን ዘገበ።

    ሲቢኤስ በስም ያልጠቀሳቸውን ምንጮች በእራት ግብዣው ላይ ከአምስት እስከ ስምንት የሚደርሱ ጥይቶች ተተኩሰዋል ብለዋል።

    በዋሺንግተን ዘጋቢዎች የእራት ግብዣ ላይ ተኩስ በመክፈት በቁጥጥር ስር የዋለው ተጠርጣሪ ግለሰብ ኮል ቶማስ አለን እንደሚባል የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    31 ዓመቱ እንደሆነ የተገለጸው ግለሰቡ በደቡብ ምዕራብ ሎስ አንጀለስ፤ ቶራንስ፣ ካሊፎርኒያ እንደሚኖር ተገልጿል።

    የቢቢሲ አጋር የሆነው ሲቢኤስ ከካሊፎርኒያ ኢንስቲትዩት ኦፍ ቴክኖሎጂ የተመረቀው ግለሰቡ በቶረንስ አካባቢ በመምህርነት እንደሚያገለግል ዘግቧል።

    ፖሊስ ተጠርጣሪው የእራት ግብዣው በሚካሄድበት በዋሺንግተን ሒልተን ሆቴል እንግዳ እንደበር ገልጾ ሽጉጥ፣ ቢላ እና ሌሎች የጦር መሣሪያዎችን ይዞ ነበር ብሏል።

    አለን ከጥቃቱ በኋላ ወደ ሆስፒታል ተወስዶ ሕክምና የተደረገለት ሲሆን ሰኞ ዕለት በይፋ ክስ ይመሰረትበታል።

  10. ትራምፕ የአሜሪካ ተደራዳሪዎች ወደ ፓኪስታን የሚያደርጉትን ጉዞ ሰረዙ

    ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, EPA/Shutterstock

    ዶናልድ ትራምፕ ለፎክስ ኒውስ ልዩ መልዕክተኛው ስቲቭ ዊትኮፍ እና ጃሬድ ኩሽነር ወደ ፓኪስታን ለውይይት እንደማይሄዱ ተናገሩ።

    ፕሬዚዳንቱ "ሁሉም አማራጮች አሉን፤ በፈለጉት ጊዜ ሊደውሉልን ይችላሉ፤ ነገር ግን ምንም ነገር ላለመነጋገር ተጨማሪ የ18 ሰዓት በረራ አያደርጉም።" ብለዋል።

    የፎክስ ኒውስ የዋይት ሐውስ ዘጋቢ ፕሬዚዳንት ትራምፕ "ሰዎቼን ነገርያቸዋለሁ፤ ከጥቂት ሰዓት በፊት ለመሄድ እየተዘጋጁ ነበር እና 'አይሆንም ወደዚያ ለመሄድ የ18 ሰዓት በረራ አታደርጉም' ብያቸዋለሁ” ማለታቸውን ጠቅሷል።

    ትራምፕ ከጥቂት ደቂቃዎች በኋላ በማኅበራዊ ድረ ገጻቸው ላይ የልዑካን ቡድኑን ጉዞ መሰረዛቸውን አረጋግጠዋል።

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት የአሜሪካ ልዑካን ወደ ኢዝላማባድ የሚያደርጉትን ጉዞ የሰረዙት ”በጉዞ ብዙ ሰዓት ነው የሚጠፋው፤ ብዙ ሥራ ነው” በማለት ነው።

    “ወኪሎቼ ወደ ፓኪስታን ኢዝላማባድ ኢራናውያንን ለማግኘት የሚያደርጉትን ጉዞ ሰርዣለሁ።”

    “ከዚህም በተጨማሪ በአመራሩ መካከል ከፍተኛ ክፍፍል እና ግራ መጋባት አለ። ማንም መሪው ማን እንደሆነ አያውቅም። እነርሱን ጨምሮ።

    በተጨማሪም ሁሉም አማራጭ አለን። እነርሱ ግን ምንም የላቸውም! መነጋገር ከፈለጉ ማድረግ ያለባቸው መደወል ብቻ ነው!!!’’ ብለዋል

  11. ወደ ፓኪስታን የሚጓዙት የትራምፕ ተደራዳሪዎች ጃሬድ ኩሽነር እና ስቲቭ ዋትኮፍ ማን ናቸው?

    ጃሬድ ኩሽነር (ግራ) እና ስቲቭ ዋትኮፍ (ቀኝ)

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ጃሬድ ኩሽነር (ግራ) እና ስቲቭ ዋትኮፍ (ቀኝ)

    ስቲቭ ዊትኮፍ እና ጃሬድ ኩሽነር ከኢራን ጦርነት ጋር የተያያዘ ተጨማሪ ንግግር ለማድረግ ዛሬ ፓኪስታን እንደሚጓዙ ዋይት ሀውስ አስታውቋል። ሁለቱ የትራምፕ ተደራዳሪዎች ማናቸው? በሰላም ንግግሩ የሚሳተፉትስ ለምንድነው?

    ጃሬድ ኩሽነር የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አማች ሲሆኑ ባለቤታቸው የፕሬዝዳንቱ ልጅ ኢቫንካ ትራምፕ ናት።

    በትራምፕ የመጀመሪያው ሥልጣን ዘመን የፕሬዝዳንቱ አማካሪ ሆነው ሰርተዋል። አሁን ይህ አይነት ሹመት ባይኖራቸውም ቁልፍ ዓለም አቀፉ ጉዳዮች ላይ ይሳተፋሉ። እስራኤል እና ሐማስ የተኩስ አቁም ያደረጉበት ድርድር ላይም ተሳትፎ ነበራቸው።

    ስቲቭ ዊትኮፍ የሪል ስቴት አልሚ እና የትራምፕ ወዳጅ ናቸው። ባለፈው ዓመት ትራምፕ ሁለተኛ የሥልጣን ዘመናቸውን ሲጀምሩ የመካከለኛው ምሥራቅ ልዩ መልዕክተኛ ሆነው ተሾመዋል።

    የትራምፕ አስተዳደር ለዓለም አቀፍ ድርድሮች የሚልካቸው ሰው የሆኑት ዊትኮፍ፤ በእስራኤል እና ሐማስ እንዲሁም ሩሲያ እና ዩክሬን ንግግሮች ላይ ቁልፍ ሚና ተጫውተዋል።

  12. ኢራን ለእስራኤል ይሰላል ያለችውን ተቃዋሚ በሞት ቀጣች

    የስቅላት ገመድ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ኢራን በአገሪቱ በተካሄደው ተቃውሞ ወቅት የእስራኤል የስለላ ድርጅትን “ተልዕኮ” ይዞ በመንቀሳቀስ የወነጀለችውን ግለሰብ በስቅላት መቅጣቷን ከእስላማዊ አብዮታዊ ዘቡ ጋር ግንኙነት ያላቸው ፋርስ እና ታስኒም የዜና ወኪሎች ዘገቡ።

    ኢፍራን ኪአኒ የተባለው ግለሰብ ባለፈው ጥር በተካሄደው ተቃውሞ ወቅት “ውድመት እና ቃጠሎ” በማድረስ እንዲሁም “ሽብር በመፍጠር” መከሰሱን የታስኒም ዘገባ ያመለክታል።

    የአገሪቱ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የቅጣት ውሳኔው ካስተላለፈበት በኋላ ዛሬ ጠዋት መሰቀሉን የዜና ወኪሎቹ ዘግበዋል።

    እስራኤል በጉዳዩ ላይ አስተያየት አልሰጠችም።

    የኢራን ገንዘብ ዋጋ በከፍተኛ ሁኔታ ማሽቆልቆሉን እና የኑሮ ውድነት መናሩን ተከትሎ ባለፈው ታህሳስ ላይ የተቀሰቀው የኢራን ተቃውሞ በጥር ወር በመላ አገሪቱ ተስፋፍቶ ነበር።

    ተቃውሞ የወጡ ሰልፈኞች በኢራን ባለሥልጣናት ኃይል የተሞላት እርምጃ ተወስዶባቸዋል። የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች እንደሚናገሩት ተቃውሞውን ለማፈን በተወሰደው እርምጃ በሺህዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ተገድለዋል።

  13. የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፓኪስታን የሄዱት “ስለ ኒውክሌር ለመወያየት” አለመሆኑን የአገሪቱ ከፍተኛ ፖለቲከኛ ተናገሩ

    ኢብራሂም አዚዝ ከዚህ በፊት የእስላማዊው አብዮታዊ ዘብ አዛዥ ነበሩ

    የፎቶው ባለመብት, IRGC

    የምስሉ መግለጫ, ኢብራሂም አዚዝ ከዚህ በፊት የእስላማዊው አብዮታዊ ዘብ አዛዥ ነበሩ

    የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራጋቺ በፓኪስታን ጉዟቸው ወቅት “ከኒውክሌር ንግግር ጋር የተያያዘ ምንም ዓይነት ሥራ” እንደሌላቸው የአገሪቱ ብሔራዊ ደህንነት ኮሚቴ ኃላፊ ተናገሩ።

    ኢብራሂም አዚዝ ትናንት ምሽት ከጋዜጠኞች ጋር በነበራቸው ቆይታ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ኢስላማባድ የሚገኙት “በሁለትዮሽ ግንኙነት ላይ ለመወያየት ብቻ” መሆን ተናግረዋል።

    ከዚህ በፊት የእስላማዊው አብዮታዊ ዘብ አዛዥ የነበሩት አዚዝ በኒውክሌር ላይ የሚደረግ ንግግር “ከኢራን ጠንካራ ቀይ መስመሮች መካከል አንዱ ሆኖ ይቆያል” ብለዋል።

    አሜሪካ ቴህራን የኒውክሌር ፕሮግራሟን እንደታቆም የምትፈልግ ሲሆን ይህም የመጨረሻው የሰላም ስምምነት አካል መሆን እንዳለበት በአጽንኦት ትናገራለች።

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በትናንትው ዕለት ቴህራን የስምምነት ሃሳቦችን ማቅረቧን እና እንደሚመለከቱት ተናገረው ነበር

    ትራምፕ ለሮይተርስ የዜና ወኪል አርብ ዕለት እንደተናገሩት ኢራን “የስምምነት ሃሳቦችን አቅርባለች እናም እናየዋለን” ቢሉም የስምምነት ነጥቦቹ ምን እንደሆኑ እንደማያውቁ ተናግረዋል።

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት አክለውም ኢራን ከስምምነት ላይ መድረስ የሚያስችላትን መንገድ ለመፈተሽ እና ለመነጋገር እንዲሁም የአሜሪካን ፍላጎቶች የሚያሟላ የስምምነት ሃሳቦችን እያዘጋጀች ነው ብለዋል።

  14. ቱርክ ከአሜሪካ እና ኢራን የሰላም ስምምነት በኋላ ሆርሙዝን ከፈንጂ ማጽዳት ላይ ልትሰማራ እንደምትችል ገለጸች

    በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ የሚቀዝፉ መርከቦች

    የፎቶው ባለመብት, REUTERS

    የቱርክ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሃካን ፊዳን በቴህራን እና ዋሽንግተን ሊደረስ ከሚችል የሰላም ስምምነት በኋላ አገራቸው የሆርሙዝ ወሽመጥን ከፈንጂ የማጽዳት ሥራ ላይ መሳተፍ እንደምትችል አስታወቁ።

    ፊዳን አርብ ምሽት ለጋዜጠኞች እንደተናገሩት ከማንኛውም ስምምነት በኋላ የቴክኒክ ቡድን በወሽመጡ የተጠመዱ ፈንጂዎችን ማምከን ሥራ ላይ ለመሠማራት እየጠበቀ መሆኑን ተናግረዋል።

    አክለውም ቱርክ እንዲህ ዓይነት ጥረቶችን እንደ ሰብዓዊ ግዴታ እንደምትመለከተው ገልጸዋል።

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ማንኛውም የፈንጂ የማምከን ሥራ የሚሠራው ከተለያዩ አገራት በተውጣጡ ቴክኒካል ቡድን መሆንን ገልጸው ከኢራን እና የአሜሪካ የሰላም ስምምነት በኋላ የሚመሠረት መሆኑን አስታውቀዋል።

    ቱርክ በእነዚህ ሁኔታዎች ውስጥ በፈንጂ ማምከን ሥራዎች ላይ በመሳተፍ ረገድ "ችግር የለባትም" ብለዋል።

    ፊዳን ወደፊት ከተለያዩ አገራት ተውጣጥቶ የሚመሰረተው የቴክኒክ ባለሙያዎች ጥምረት የአዲስ ግጭት አካል የሚሆን ከሆነ ቱርክ አቋሟን መልሳ እንደምትመለከት አስጠንቅቀዋል።

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ፊዳን ከኢራን የኒውክሌር መርሃ ግብር ጋር የተያያዙ ጉዳዮች በፓኪስታን በሚደረገው ቀጣይ ዙር ውይይት ሊፈቱ ይችላሉ ብለው እንደሚያምኑ ተናግረዋል።

  15. የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚንስትር ከፓኪስታን ጦር አዛዥ ጋር ተገናኙ

    ዛሬ ማለዳ የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እና የፓኪስታኑ መከላከያ አዛዥ በኢዝላማባድ ተገናኝተው ተወያይተዋል

    የፎቶው ባለመብት, Iranian Ministry of Foreign Affairs

    የምስሉ መግለጫ, ዛሬ ማለዳ የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እና የፓኪስታኑ መከላከያ አዛዥ በኢዝላማባድ ተገናኝተው ተወያይተዋል

    ትናንት ምሽት ኢስላማባድ የደረሱት የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ ከፓኪስታኑ ጦር አዛዥ ፊልድ ማርሻል ጋር ተገናኝተው ተወያዩ።

    አራጋቺ ከፓኪስታን ባለሥልጣናት ጋር ከተወያዩ በኋላ ወደ ኦማን እና ሩሲያ እንደሚጓዙ አስታውቀዋል።

    በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ባጋሩት ጽሑፍ “ከአጋሮቻችን ጋር በሁለትዮሽ ጉዳዮች ጋር ለመተባበር እና በቀጠናዊ ጉዳዮች” ላይ እንደሚወያዩ አስታወቀው ነበር።

    ምንም እንኳ ቴህራን በኢራን እና አሜሪካ መካከል የታቀደ ቀጥተኛ ንግግር የለም ብትልም የአሜሪካ ልዑካን ወደ ኢስላማባድ እንደሚጓዙ ይጠበቃል።

    ፓኪስታን በከተማዋ ያለውን የጸጥታ ሁኔታ እንዳጠናከረች ሲሆን እስካሁን ድረስ ግን በሁለቱ አገራት መካከል ስለሚደረግ ሁለተኛ ዙር የፊት ለፊት ውይይት የታወቀ ነገር የለም።

    ፓኪስታን በቴህራን እና በዋሺንግተን መካከል ሁለተኛው ዙር የሰላም ውይይት ይደረጋል ተብሎ ከታቀደበት ጊዜ አንስቶ የከተማዋን ጸጥታ አጠናክራለች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ፓኪስታን በቴህራን እና በዋሺንግተን መካከል ሁለተኛው ዙር የሰላም ውይይት ይደረጋል ተብሎ ከታቀደበት ጊዜ አንስቶ የከተማዋን ጸጥታ አጠናክራለች
  16. ስዊዘርላንድ “ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶች” ለማገዝ ቴህራን ውስጥ የሚገኘው ኤምባሲዋን በድጋሚ ከፈተች

    ስዊዘርላንድ በኢራን ዋና ከተማ ቴህራን ውስጥ የሚገኘውን ኤምባሲዋን በሂደት በድጋሚ እየከፈተች መሆኑን የአገሪቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታወቀ።

    ኤምባሲው ኢራን ውስጥ የአሜሪካን ፍላጎቶች በመወከል እንደሚንቀሳቀስ ተነግሯል። አሜሪካ በአውሮፓውያኑ 1979 የኢራን አብዮት ፈንድቶ የኤምባሲ ሠራተኞቿ ታግተው ከተወሰዱ በኋላ ቴህራን ውስጥ በዲፕሎማሲያዊ መንገድ የሚወክላት ተቋም የላትም።

    የስዊዘርላንድ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር እንዳስታወቀው ኤምባሲውን የመክፈት ውሳኔ የተላለፈው ከኢራን እና ከአሜሪካ ጋር ምክክር ከተደረገ በኋላ ነው። አውሮፓዊቷ አገር "ግጭትን ለማርገብ እና ዘላቂ ሰላም ለማምጣት ለሚደረጉ ማናቸውም ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶች" መስሪያ ቤቶቿን ለድጋፍ ለማዋል ዝግጁ መሆኗን ገልጻለች።

  17. የእስራኤል ጦር እና ሄዝቦላህ የተኩስ አቁሙን በመጣስ እርስ በእርሳቸው ተካሰሱ

    ታንክ ላይ የቆሙ የእስራኤል ወታደሮች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በእስራኤል እና በሊባኖስ መካከል የተኩስ አቁም ስምምነት ለሦስት ሳምንታት መራዘሙን ይፋ ካደረጉ በኋላ ባሉት ቀናት የእስራኤል ጦር እና የሄዝቦላህ ታጣቂዎች የተኩስ አቁሙን በመጣስ ተካሰሱ።

    የእስራኤል የመከላከያ ሠራዊት ሄዝቦላህ በደቡባዊ ሊባኖስ በሚገኙ ወታደሮቹ ላይ አጥፍቶ ጠፊ ድሮኖችን በመላክ ጥሰት መፈጸሙን አስታውቋል።

    “ይህ ክስተት የተኩስ አቁም ስምምነትን በግልጽ የሚጥስ ነው” ሲል የመከላከያ ሠራዊት አባላት ላይ ምንም ዓይነት ጉዳት እንዳልደረሰ ገልጿል።

    ሄዝቦላህ በበኩሉ እስራኤል "የተኩስ አቁም ስምምነቱን በመጣሷ" ምክንያት አርብ ዕለት ከሰዓት በኋላ እና ማታ የእስራኤልን ወታደሮች እና ድሮኖች ላይ አምስት ያህል ጥቃቶችን መሰንዘሩን አስታውቋል።

  18. አሜሪካ የኢራን ነዳጅ ንግድ ላይ አዲስ ማዕቀቦችን መጣሏን አስታወቀች

    የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማርኮ ሩቢዮ

    የፎቶው ባለመብት, EPA/Shutterstock

    የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት “የኢራንን ሕገ ወጥ የነዳጅ ንግድ ማስተጓጎል የሚያስችል ቆራጥ እርምጃ” እየወሰደ መሆኑን ገለጸ።

    የአገሪቱ ግምጃ ቤት የዚህ እርምጃ አካል የሆኑ አዲስ ማዕቀቦችን ኢራን ላይ ጥሏል። ማዕቀቡ የተጣለው “ዋና፣ እና ገለልተኛ የቻይና የነዳጅ ማጣሪያ” ላይ እንዲሁም “በሌሎች 40 ገደማ ዒላማዎች" ላይ እንደሆነ ተገልጿል።

    በግምጃ ቤቱ ድረ ገጽ ላይ የወጣው መረጃ እንደሚያሳየው ከቻይናው ነዳጅ ማጣሪያ በተጨማሪ ሌሎች 40 ገደማ የሚሆኑ ተቋማት እና የነዳጅ ጫኝ መርከቦችም ማዕቀብ ዝርዝሩ ውስጥ ተካትተዋል።

    አዲሶቹ ማዕቀቦች "ለኢራን የነዳጅ ኤክስፖርት ወሳኝ የሕይወት መስመሮች" እንደሆኑ ግምጃ ቤቱ ገልጿል።

    የግምጃ ቤት ኃላፊው ስኮት ቤሰንት በኤክስ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት ጽሑፍ፤ አሜሪካ "[ከኢራን] አገዛዝ ጋር የተገናኙ ማናቸውንም የፋይናንስ መስመሮች ዒላማ ታደርጋለች" ብለዋል። ከዚህ ጋር በተያያዘው ግምጃ ቤቱ 344 ሚሊዮን ዶላር የሚያወጣ ዲጂታል ገንዘብ (ክሪፕቶከረንሲ) ማገዱን ገልጿል።

    የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤቱም በበኩሉ እነዚህ ማዕቀቦች የኢራን አገዛዝ "በመካከለኛው ምሥራቅ ለሚያከናውናቸው ቀጣናዊ መረጋጋትን የሚያናጉ ተግባራት" የሚውሉ የገቢ ምንጮችን ያቋርጣሉ ብሏል።

  19. የአሜሪካ ተደራዳሪዎች ለሰላም ንግግር ወደ ፓኪስታን ሊጓዙ ነው፤ ኢራን የታቀደ ቀጥተኛ ንግግር እንደሌለ ገልጻለች

    የትራምፕ አማች ጃሬድ ኩሽነት (በስተግራ) እና የፕሬዝዳንቱ ልዩ መልዕክተኛ ስቲቭ ዊትኮፍ (በስተቀኝ) ቅዳሜ ወደ ኢዝላማባድ እንዲሚጓዙ ተገልጿል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የትራምፕ አማች ጃሬድ ኩሽነት (በስተግራ) እና የፕሬዝዳንቱ ልዩ መልዕክተኛ ስቲቭ ዊትኮፍ (በስተቀኝ) ቅዳሜ ወደ ኢዝላማባድ እንዲሚጓዙ ተገልጿል

    የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ ትናንት ምሽት ፓኪስታን የደረሱ ሲሆን የፕሬዝዳንት ትራምፕ አስተዳደርም ሁለት ተደራዳሪዎቹን ወደ ዋና ከተማዋ ኢዝላማባድ እንደሚልክ ገልጿል።

    እንደ ዋይት ሐውስ ገለጻ የትራምፕ ልዩ መልዕክተኛ ስቲቭ ዊትኮፍ እና አማቻቸው ጃሬድ ኩሽነር ቅዳሜ ወደ ኢዝላማባድ የሚበርሩት ኢራን “በአካል” መነጋገር ስለፈለገች ነው።

    ንግግሩ ውጤታማ የሚሆን ከሆነ የተደራዳሪው ቡድን መሪ የሆኑት የአሜሪካ ምክትል ፕሬዝዳንት ጄዲ ቫንስ ወደ ፓኪስታን ለመጓዝ “ዝግጁ” መሆናቸውን የዋይት ሐውስ ፕሬስ ኃላፊ ካሮሊን ሌቪት ተናግረዋል።

    በኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በኩል የወጣው መረጃ ግን ከዚህ የተለየ ነው። ከኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ ጋር አርብ ምሽት ኢዝላማባድ መድረሳቸውን የገለጹት የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ቃል አቀባይ ኢስማኢል ባቃኢ፤ ሚኒስሩ “ከፓኪስታን ከፍተኛ አመራሮች ጋር” እንደሚነጋገሩ ገልጸዋል።

    አክለውም “በኢራን እና አሜሪካ መካከል እንዲካሄድ የታቀደ ስብሰባ የለም። የኢራን ምልከታዎች ለፓኪስታን ይቀርባሉ” ሲሉ የቴህራን ባለሥልጣናት ከአሜሪካ ተደራዳሪዎች ጋር በቀጥታ እንደማይነጋገሩ አመልክተዋል።

    አርብ ዕለት ከጋዜጠኞች ጋር ቆይታ የነበራቸው የዋይት ሐውስ ቃል አቀባይ ሌቪት እንደተናገሩት ፕሬዝዳንት ትራምፕ ተደራዳሪዎቻቸውን ወደ ኢዝላማባድ የላኩት “ኢራናውያኑን ለመስማት” ነው። ትራምፕ “ሁሌም ለዲፕሎማሲ ዕድል ለመስጠት ፈቃደኛ” መሆናቸውን ጠቅሰዋል።

    “በእርግጠኝነት ባለፉት ሁለት ቀናት ከኢራን ወገን በኩል የተወሰነ መሻሻል ተመልክተናል” ብለዋል።

    በኢዝላማባድ የሚገኘው የኢራን ኤምባሲ ግን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አራግቺ በፓኪስታን ጉዟቸው ያቀዱት “የሁለትዮሽ ጉዳዮችን ለመገምገም” እና ቀጣናዊ ሁኔታዎችን ለመወያየት እንደሆነ ገልጿል። አራግቺ ከፓኪስታን በተጨማሪ ወደ ኦማን እና ሩሲያ እንደሚጓዙ አስታውቀዋል።

    ከዚህ አስቀድሞ አሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትርምፕ ባለሥልጣናቶቻቸው ኢራን ውስጥ “አሁን ኃላፊነት ላይ ካሉት ሰዎች ጋር” እየተደራደሩ መሆኑን ተናግረው ነበር።

    ኢራን “መደራደሪያ አቅርባለች፤ እንመለከተዋለን” ብለዋል፤ ቀርቧል ስላሉት የድርድር ነጥቦች ግን ዝርዝር መረጃ ሳይሰጡ ቀርተዋል።

  20. የአውሮፓ ሕብረት፤ ስምምነት ላይ የሚደረስ ከሆነ ኢራን ላይ የተጣሉ ማዕቀቦችን ለመቀነስ ክፍት መሆኑ ተገለጸ

    የአውሮፓ መሪዎች

    የፎቶው ባለመብት, EPA/Shutterstock

    የአውሮፓ ሕብረት መሪዎች ዛሬ ከግብጽ፣ ሶርያ እና ሊባኖስ መሪዎች ጋር ቆጵሮስ ውስጥ ስብሰባ አካሂደዋል።

    የጀርመን ቻንስለን ፍሬድሪክ መርዝ ሁሉን አቀፍ ስምምነት ላይ የሚደረስ ከሆነ የአውሮፓ ህብረት ኢራን ላይ የተጣሉ ማዕቀቦችን በሂደት ለመቀነስ ፍቃደኛ መሆኑን ለአገራቱ መሪዎች መናገራቸውን ሮይተርስ የዜና ወኪል ዘግቧል።

    የጀርመኑ መሪ “ይህንን ሂደት ለማገዝ ማድረግ ከምንችለው አስተዋፆ አንዱ ነው፤ ወደ ዘላቂ ተኩስ አቁም ይመራል የሚል ተስፋ አለን” ሲሉ ተናግረዋል።

    የአውሮፓ ሕብረት ምክር ቤት ፕሬዝዳንት አንቶኒዮ ኮስታ በበኩላቸው የሆርሙዝ ወሽመጥ “ያለምንም እገዳ እና ያለ ምንም ክፍያ በአፋጣኝ መከፈት አለበት” ማለታቸውን ኤኤፍፒ የዜና ወኪል ዘግቧል። የባሕር መተላለፊያው “ለመላው ዓለም ወሳኝ” መሆኑንም ጠቅሰዋል።

    ስብሰባው ከመጀመሩ አስቀድሞ አስተያየት የሰጡት የሕብረቱ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ኃላፊ ካጃ ካላስ በበኩላቸው ከኢራን ጋር የሚደረገው ንግግር በአውሮፓውያኑ 2015 የተደረሰው የኢራን የኒውክሌር ስምምነት አይነት ውጤት የማያስገኝ ከሆነ መላው ዓለም የበለጠ አደገኛ ሁኔታ ውስጥ እንደሚገባ አስገንዝበዋል።

    ከ10 ዓመት በፊት የተፈረመው የኒውክሌር ስምምነት የፈረሰው ፕሬዝዳንት ትራምፕ በመጀመሪያው የሥልጣን ዘመናቸው አሜሪካን ከውሉ ፈራሚነት ካስወጡ በኋላ ነበር።