ኢራን ጠቅላይ መሪዋን ልትሰይም ነው፤ እስራኤል መራጮቹን እና ተመራጩን እያደነች መሆኗን ገለጸች

ቀጣዩን የኢራን ጠቅላይ መሪ ለመሰየም እየመከረ ያለው የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ ከፍተኛ የሊቃውንት ጉባዔ ከስምምነት ላይ መድረሱ ተነገረ። ጉባዔው የመጨረሻውን ውሳኔ ለማሳለፍ የጋራ አቋም ላይ መድረሱ አንድ አባሉ ሲናገሩ፣ እስራኤል ደግሞ መራጮችን እና ተመራጩን ዒላማ ማድረጓን እንደምትቀጥል አስታወቀች።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ኢራን ምን ዓይነት ሚሳዔሎች አሏት?

    ኢራን በአሜሪካ እና በእስራኤል ጥቃት ከተከፈተባት በኋላ የአጸፋ ጥቃቶችን የአሜሪካ አጋር በሆኑ የመካከለኛው ምሥራቅ አገራት ላይ በሚሳዔል እና በድሮን እየፈጸመች ነው።

    አሜሪካ ጦርነት ከመጀመሩ በፊት በተደረጉ ደርድሮች ላይ ከኢራን የኒውክሌር መረሃ ግብር በተጨማሪ በሚሳዔል ትጥቋ ላይ ቁጥጥር እንዲደረግ ስትጠይቅ ነበር።

    ኢራን ግን የሚሳዔል ግንባታዋ ለድርድር የማይቀርብ "ቀይ መስመር ነው" ስትል ተቃውማው ነበር።

    ለመሆኑ ኢራን ምን ዓይነት እና ምን ያህል ርቀት ተጉዘው የሚመቱ ሚሳዔሎች አሏት?

    ግራፊክስ ምሥል
  2. በእስራኤል ጥቃት ከተፈጸመባቸው ነዳጅ ማጣሪያዎች የሚወጣው ጭስ የፈጠረው ከባድ ጭስ

    ቃጠሎ

    የፎቶው ባለመብት, Vahid Online / X

    እስራኤል ቅዳሜ ሌሊት ለእሁድ አጥቢያ ቴህራን ውስጥ በሚገኙ የነዳጅ ማጣሪያዎች ላይ በፈጸመችው ጥቃት የተፈጠረው ከባድ ጥቁር ጭስ ዋና ከተማዋን በመሸፈኑ “ፀሐይ ሙሉ ለሙሉ የጠፋች” እንደመሰለ ነዋሪዎች ተናገሩ።

    ቢቢሲ ቬሪፋይ ትክክለኛነቱን ያረጋገጠው እና በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ እየተዘዋወረ ያለ ቪዲዮ በዋና ከተማዋ ሰሜን ምዕራብ ክፍል ውስጥ ጎዳናዎች ሲቃጠሉ ያሳያል።

    እሳቱ የተነሳው በእስራኤል ጥቃት ተመትቷል ከተባለው የነዳጅ ማጣሪያ ሁለት ኪሜ ያህል ርቀው በሚገኙት ኩህሳር እና ሻህራን በሚባሉ አካበቢዎች ነው።

    በመንግሥት የሚተዳደረው የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ ብሮድካስቲንግ ተቋም እንደዘገበው በቴህራን እና አልቦርዝ በተባሉት ግዛቶች ውስጥ የሚገኙ የነዳጅ ማጠራቀሚያዎች ሌሊቱን ጥቃት ተፈጽሞባቸዋል።

    በኢራን ላይ ከተፈጸመው ጥቃት በተጨማሪ ኢራን በበኩሏ ኩዌት ውስጥ የሚገኝ ሰማይ ጠቀስ ሕንጻ ላይ የድሮን ጥቃት ፈጽማ ከባድ እሳት ተቀስቅሶ የነበረ ሲሆን፣ አሁን በቁጥጥር ስር መዋሉን ባለሥልጣናት አስታውቀዋል።

    በተመሳሳይ እስራኤል በሊባኖስ ላይ የምትፈጽመውን ጥቃት ቀጥላ አስካሁን 394 ሰዎች መገደላቸውን የአገሪቱ ጤና ሚኒስቴር ገልጿል።

    ከቃጠሎ በኋላ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

  3. የሊባኖስ ጤና ሚኒስትር በእስራኤል ጥቃት ወደ 400 የሚጠጉ ሰዎች ተገድለዋል አለ

    የሊባኖስ ጤና ሚኒስቴር እስራኤል በአገሪቱ ላይ ጥቃት መፈጸም ከጀመረችበት ጊዜ አንስቶ ወደ 394 መገደላቸውን ተናገረ።

    ራካን ናሴሬዲን እሁድ ዕለት በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ አሜሪካ እና እስራኤል ከኢራን ጋር የሚያደርጉትን ጦርነት ተከትሎ ሊባኖስ ዒላማ መሆኗን ገልጸው 83 ሕፃናት እና 42 ሴቶችን ጨምሮ 394 ሰዎች መገደላቸውን ተናግረዋል።

    ናሴሬዲን አክለውም ዘጠኝ የሕይወት አድን ሠራተኞችም በጥቃቱ ከተገደሉት መካከል መሆናቸውን ገልጸዋል።

    የጤና ሚኒስትሩ ቅዳሜ ዕለት 294 ሰዎች መገደላቸውን ተናግረው የነበረ ሲሆን ከዚያ ወዲህ ቁጥሩ በከፍተኛ ሁኔታ ጨምሯል።

  4. ጦርነቱ ከተጀመረ አንስቶ ወደ 2,000 የሚጠጉ ሰዎች ቆስለው ሆስፒታል ገብተዋል- የእስራኤል ጤና ሚኒስቴር

    በእስራኤል ከኢራን ጋር ጦርነት ከጀመረችበት ጊዜ አንስቶ 1,929 ሰዎች ቆስለው ወደ ሆስፒታሎች መግባታቸውን የአገሪቱ ጤና ሚኒስቴር አስታወቀ።

    ከእነዚህውስጥ 122ቱ አሁንም በሆስፒታል ውስጥ የሚገኙ ሲሆን፣ ዘጠኙ ደግሞ “በከባድ ሁኔታ” ላይ መሆናቸወን ሚኒስቴሩ አስታውቋል።

    ከቆሰሉት መካከል አንዳንዶቹ በቀጥታ “ከሚሳዔል ጥቃቶች” ጋር በተያያዘ ጉዳት አንዳልደረሰባቸው ሚኒስቴሩ በመግለጫው ላይ ጠቅሷል።

    ባለፉት 24 ሰዓታት ውስጥ 157 ሰዎች ሕክምና እንደተደረገላቸውም ተገልጿል።

    ሚኒስቴሩ መግለጫውን ያወጣው ዛሬ ማለዳ ሲሆን፣ ኢራን ወደ አገሪቱ የምታስወነጭፈው ሚሳዔል መቀጠሉም ተነግሯል።

    የእስራኤልየመከላከያ ሠራዊት በቴሌግራም ቻናሉ ላይ የሚሳዔል "የመከላከያ ሥርዓቶች አደጋውን ለመግታት እየጣሩ ነው" ሲል አስታውቋል።

    አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ ጥቃት መፈጸም ከጀመሩበት ከአንድ ሳምንት በፊት አንስቶ እስከ ዛሬ ድረስ በኢራን ውስጥ የሞቱ ሰዎች ቁጥር ከ1000 አልፏል።

  5. ኢራን ጠቅላይ መሪዋን ልትሰይም ነው፤ እስራኤል መራጮቹን እና ተመራጩን እያደነች መሆኗን ገለጸች

    የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ ከፍተኛ የሊቃውንት ጉባዔ አባል ሞሐመድ መህዲ ሚርባጌሪ

    የፎቶው ባለመብት, Telegram via Mehr News Agency

    የምስሉ መግለጫ, የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ ከፍተኛ የሊቃውንት ጉባዔ አባል ሞሐመድ መህዲ ሚርባጌሪ

    ቀጣዩን የኢራን ጠቅላይ መሪ ለመሰየም እየመከረ ያለው የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ ከፍተኛ የሊቃውንት ጉባዔ ከስምምነት ላይ መድረሱ ተነገረ።

    ጉባዔው የመጨረሻውን ውሳኔ ለማሳለፍ የጋራ አቋም ላይ መድረሱ አንድ አባሉ ሲናገሩ፣ እስራኤል ደግሞ መራጮችን እና ተመራጩን ዒላማ ማድረጓን እንደምትቀጥል አስታወቀች።

    ሞሐመድ መህዲ ሚርባጌሪ ለኢራን ዜና አገልግሎት እንደተናገሩት “ጽኑ እና የጋራ ስምምነት ላይ ተደርሷል” በማለት አንዳንድ መቋጫ የሚሹ ነገሮች ብቻ መቅረታቸውን አመልክተዋል።

    የሊቃውንቱ ጉባዔ ትኩረት ሰጥቶ ያለማቋረጥ የሚጠበቅበትን እያከናወነ መሆኑን ጠቅሰው፤ ነገር ግን "በዚህ አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ እንቅፋቶች አሉ። ለዚህም ሥራዎች በጥንቃቄ ተሠርተው በመግባባት ለታሪክ እንዲቀመጡ ይደረጋል” ብለዋል።

    አስካሁን ባለው ሂደት "ግልጽ እና አስተማማኝ የጋራ የሃሳብ አንድነት ላይ ተደርሷል” ያሉት የጉባዔው አባል “እንቅፋቶች” ያሏቸው ጉዳዮችም በፍጥነት እንደሚወገዱ ተስፋቸውን ገልጸዋል።

    የኢራን ከፍተኛ ሊቃውንት ቀጣዩን መሪ ለመምረጥ የሚያከናወኑትን ተግባር በቅርበት እየተከታተለ መሆኑን የገለጸችው እስራኤል ደግሞ የአያቶላህ አሊ ኻሜኒን የሚተካውን መሪ ማደኗን እንደምትቀጥል አስጠንቅቃለች።

    የእስራኤል ጦር በፋርስ ቋንቋ [የኢራን ብሔራዊ ቋንቋ] በኤክስ ላይ ባሰፈረው ጽሑፍ “ለአስርታት ተሰብስቦ የማያውቀው የኢራን የሊቃውንት ጉባዔ፣ በቆም ከተማ ውስጥ በቅርቡ ስብሰባውን ያደርጋል።

    "ልንነግራችሁ የምንፈልገው ጠቅላይ መሪውን ለመተካት የሚፈልገውን እና ተተኪውን ለመሰየም የሚጥሩትን ሰዎች በሙሉ እስራኤል ማደኗን ትቀጥላላች።

    "ተተኪውን መሪ ለመምረጥ በሚደረገው ስብሰባ የሚሳተፉትን በሙሉ ዒላማ ከማድረግ ወደ ኋላ እንደማንል ልናስጠነቅቃችሁ እንፈልጋለን። ይህ ማስጠንቀቂያ ነው!” በማለት የሚመረጠውን መሪ ብቻ ሳይሆን በምርጫው የሚሳተፉትን ከማጥቃት ወደኋላ እንደማትል እስራኤል አስታውቃለች።

    ባለፈው ሳምንት ቅዳሜ እስራኤል እና አሜሪካ በኢራን ላይ ጥቃት በጀመሩ በመጀመሪያው ሰዓት ላይ ነበር የአገሪቱ ጠቅላይ መሪ አያቶላህ ኻሜኒ እና ሌሎች ከፍተኛ ባለሥልጣናት የተገደሉት።

  6. አርባ ሁለት የኢራን ባሕር ኃይል መርከቦች መስመጣቸውን ፕሬዝዳንት ትራምፕ ተናገሩ

    ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ ከሳምንት በፊት በፈጸሙት ጥቃት 42 የባሕር ኃይል መርከቦችን መምታታቸውን እና በአገሪቱ ሠራዊት እንዲሁም በአመራሩ ላይ ከፍተኛ ጉዳት ማድረሳቸውን ፕሬዝዳንት ትራምፕ ተናገሩ።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ በአሜሪካ የቢቢሲ አጋር ለሆነው ሲቢኤስ ቴሌቪዥን በስልክ በሰጡት ቃለ ምልልስ ባለፉት ስምንት ቀናት በተፈጸመው ጥቃት የኢራን ባሕር እና አየር ኃይል ከጥቅም ውጪ መሆኑን ገልጸዋል።

    "አሁን እየተነጋገርን ፋብሪካዎቻቸው እየፈነዱ ነው። ባሕር ኃይላቸው የለም፤ ሰምጦ ከባሕር ባታች ነው። በስድስር ቀናት ውስጥ 42 መርከቦች፣ አርባ ሁለት መርከቦች [ተመትተዋል]። ባሕር ኃይላቸው የለም። አየር ኃይላቸውም ጠፍቷል። እያንዳንዱ የጦር ሠራዊታቸው ክፍል ተመትቷል። መሪዎቻቸው ተደምስሰዋል። የቀራቸው ነገር የለም።

    "ከዚህ በፊት ታይቶ በማያውቅ ሁኔታ እና ፍጥነት እያሸነፍን ነው” ሲሉ ፕሬዝዳንቱ የበላይነት መያዛቸውን ገልጸዋል።

    ነገር ግን ጦርነቱ በቀጠለበት በአሁኑ ወቅት ኢራን በእስራኤል እና በሌሎች የመካከለኛው ምሥራቅ አገራት ላይ ያልተቋረጠ የድሮን እና የሚሳዔል ጥቃቶችን እየፈጸመች ነው።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ ፕሬዝዳንት ትራምፕ አንድ የኢራን ከፍተኛ ባለሥልጣን እስራኤል እና አሜሪካ በአገራቸው ላይ ለፈጸሙት ጥቃት ዋጋ ይከፍላሉ ማለታቻውን አጣጥለውታል።

    የኢራን ከፍተኛ የብሔራዊ ደኅንነት አማካሪ የሆኑት አሊ ላሪጃኒ በማኅበራዊ ሚዲያ ባሰፈሩት መልዕክት በአገራቸው ላይ ጥቃት የፈጸሙት አገራት “ዋጋ ይከፍላሉ” ብለው ነበር።

    "ምን እያለ እንደሆነ እና እሱ ራሱ ማን እንደሆነ አላውቅም። ምንም አያሳስበኝም፤ ግድም አይሰጠኝም" ሲሉ የተናገሩት ፕሬዝዳንት ትራምፕ "ተሸንፏል እኮ" በማለት ዛቻውን አጣጥለውታል።

    ፕሬዝዳንቱ በመካከለኛው ምሥራቅ አሜሪካ እየተከተለችው ያለው ፖሊሲ እና ስትራቴጂ ላይ ያላቻውን ከፍተኛ መተማመን በመጥቀስ "እስካሁን የተከናወነው ተግባር የሚያስደንቅ ነው። ሚሳዔሎቻውም ብትንትናቸው ወጥቷል” ሲሉ ኢራን ላይ ከባድ ጉዳት መድረሱን ተናግረዋል።

  7. እስራኤል በኢራን ላይ ሌላ ዙር የጥቃት ማዕበል መክፈቷን አስታወቀች

    አሜሪካ እና አስራኤል በኢራን ላይ የከፈቱት ጦርነት ሁለተኛ ሳምንቱን በጀመረበት በዛሬው ዕለት እስራኤል “በመላዋ ኢራን ሌላ ዙር የጥቃት ማዕበል መክፈቷን” ሠራዊቷ አስታወቀ።

    የእስራኤል ጦር በኤክስ ገጹ ላይ እንደገለጸው ጥቃቶቹ መሠረተ ልማቶችን ዒላማ ያደረጉ ሲሆን፣ ሌሊት ላይ በዋና ከተማዋ ቴህራን የሚገኙ ነዳጅ ማጣሪያዎች ተመትተዋል።

    በአጸፋውም ከኢራን በኩል ሚሳዔሎች መተኮሳቸውን የገለጸው የእስራኤል ጦር ጥቃቶቹ ጉዳት ሳያደርሱ ለማክሸፍ ጥረት እያደረገ መሆኑን አሳውቋል።

    ሌሊት ላይ እስራኤል በኢራን የነዳጅ ማጣሪያዎች ላይ በፈጸመችው ጥቃት ከባድ ጭስ በከተማዋ ሰማይ ላይ የፈጠረ ሲሆን፣ አንድ ነዋሪ ጥቃቱ የፈጠረው እሳት “ሌሊቱን ቀን አስመስሎት ነበር” በማለት የድብደባውን ከፍተኛነት ገልጾታል።

    የኢራኑ ፕሬዝዳንት ቅዳሜ ዕለት ሠራዊታቸው ጥቃት የፈጸመባቸውን የአካባቢው አገራትን ይቅርታ ቢጠይቁም ዛሬም ጥቃቶቹ ቀጥለዋል።

    የኩዌት መከላከያ ሚኒስቴር እሁድ ጠዋት እንዳስታወቀው ከኢራን በኩል የተወነጨፈ ድሮን ተመትቶ ሲወድቅ በስብርባሪዎቹ ሰላማዊ ተቋማት ላይ ጉዳት ደርሰዋል፤ ይህንንም የሚያሳዩ ቪዲዮዎች እየወጡ ነው።

    ከኩዌት በተጨማሪ በተበባሩት አረብ ኤምሬትስ እና በሌሎችም የባሕረ ሰላጤው አገራት ላይ ከኢራን በኩል የሚሰነዘረው ጥቃት መቀጠሉን የሚያመለክቱ ዘገባዎች እየወጡ ነው።

  8. በለንደን የኢራን አምባሳደር ዩኬ ወደ ጦርነቱ እንዳትገባ አስጠነቀቁ

    በለንደን የሚገኙት የኢራን አምባሳደር ሰይድ አሊ ሙሳቪ
    የምስሉ መግለጫ, በለንደን የሚገኙት የኢራን አምባሳደር ሰይድ አሊ ሙሳቪ

    በለንደን የሚገኙት የኢራን አምባሳደር ዩናይትድ ኪንግደም በጦርነቱ ውስጥ የበለጠ ተሳትፎ እንዳታደርግ አስጠነቀቁ።

    ሰይድ አሊ ሙሳቪ እሁድ እለት ከቢቢሲ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ አሜሪካ እና እስራኤል ከኢራን ጋር የጀመሩትን ጦርነት ዩኬ የምትቀላቀል ከሆነ አገራቸው "ራሷን የመከላከል መብት" እንደላት ተናግረዋል።

    ኢራን የብሪታኒያ መንግሥት እና ሌሎችም በድርጊታቸው "በጣም ጥንቁቅ" ይሆናሉ ብላ እንደምትጠብቅ በመግለጽ አስጠንቅቀዋል።

    ዩናይትድ ኪንግደም ለሚፈጸሙባት የመከላከል ጥቃቶች አሜሪካ የጦር ሠፈሮቿን እንድትጠቀም ፈቃድ ሰጥታለች፣ ነገር ግን በምንም ዓይነት ቀጥተኛ ጥቃቶች ላይ እስካሁን አልተሳተፈችም።

    አምባሳደሩ ዩኬ "በዚህ ጥቃት ውስጥ ባትሳተፍ" ጥሩ እንደሆነ ተናግረው፤ የብሪታኒያ መንግሥት እአአ በ2003 ኢራቅን ከወረረበት ጊዜ ትምህርት እንደወሰደ አምናለሁ ብለዋል።

    የኢራን ፕሬዝዳንት ቅዳሜ ዕለት የባሕረ ሰላጤው አገራትን ይቅርታ ቢጠይቁም፣ ሙሳቪ አገራቸው ላይ የሚሰነዘረው ጥቃት ከቀጠለ የአሜሪካን ጦር ሰፈሮች ማጥቃቷን እንደምትቀጥል ግልጽ አድርገዋል።

    በመካከለኛው ምሥራቅ እየተካሄደ ያለው ጦርነት በበርካታ አገራት ላይ የተለያየ መጠን ያላቸው ጉዳቶችን አስከትሏል።

    ሙሳቪ "የኢራንን ሕዝብ ለማጥቃት ተቋማት ወይም ንብረቶች ወይም መሠረተ ልማቶች ጥቅም ላይ ከዋሉ" እንደ "ሕጋዊ ዒላማዎች" ይቆጠራሉ ሲሉ ተናግረዋል።

    አሜሪካ እና እስራኤል ከኢራን ጋር የጀመሩት ጦርነት ሁለተኛ ሳምንቱን በጀመረበት ጥቂት ሰዓታት ውስጥ ኳታርን እና የተባበሩት አረብ ኤምሬትስን ጨምሮ የባሕረ ሰላጤ አገራት በኢራን ጥቃት ተፈጽሞባቸዋል።

  9. “ጦርነቱን ካሸነፍን በኋላ ድጋፍ አንፈልግም” ፕሬዝዳንት ትራምፕ

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ እና ጠቅላይ ሚኒስትር ስታርመር

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ፕሬዝዳንት ትራምፕ እና ጠቅላይ ሚኒስትር ስታርመር

    አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ ጦርነት ከመጀመራቸው እና ከጀመሩም በኋላ በቀጥታ ተሳታፊ ከመሆን የተቆጠበችው ዩናይትድ ኪንግደም አሁን ግዙፍ የጦር መርከቦችን ወደ ባሕረ ሰላጤው አካባቢ ለመላክ ወስናለች።

    ነገር ግን ይህ “የዘገየ ውሳኔ” ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕን አላስደሰታቸውም፤ እንዲያውም ጦርነቱን በአሸናፊነት እያጠናቀቁ መሆናቸውን በመግለጽ የዩናይትድ ኪንግደምን (ዩኬ) ተሳትፎ እንደማይፈልጉት አሳውቀዋል።

    ፕሬዝዳንቱ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት ጽሑፍ “ዩናይትድ ኪንግደም በአንድ ወቅት ምናልባትም ከሁሉም የላቀች ታላቅ አጋራችን ነበረች፤ አሁን ግን ሁለት የጦር አውሮፕላኖችን ወደ መካከለኛው ምሥራቅ ለመላክ ብዙ ካሰበች በኋላ ወስናለች።”

    "ጠቅላይ ሚኒስትር ስታርመር፣ መርከቦቹን ከዚህ በኋላ አንፈልጋቸውም፤ ነገር ግን የሆነውን አንረሳም” በማለት ቅሬታቸውን በቀጥታ አስፍረዋል።

    ጨምረውም "ጦርነቶችን በድል ካጠናቀቅን በኋላ አብረውን ሊሰለፉ የሚመጡ ሰዎችን አንፈልግም” ሲሉ ከዩኬ በኩል የሚመጣ ድጋፍን እንደማይሹ ገልጸዋል።

    የዩኬ መንግሥት በኢራን ላይ በተከፈተው ዘመቻ ላይ ተሳትፎም የሌለው ሲሆን፣ እንደሚተባበርም ቃል ሳይገባ ቆይቷል። አሁን ግን ሁለት ተዋጊ ጄቶችን የሚሸከሙ የጦር መርከቦች ወደ ቀጣናው ለማምራት በመጨረሻው የዝግጅት ደረጃ ላይ ይገኛል።

    ዩኬ ያሏትን የጦር ሰፈሮች አሜሪካ ጥቃት ለመፈጸም ሳይሆን ጥቃትን ለመከላከል ብቻ እንድትጠቀምበት ጠቅላይ ሚኒስትር ሰር ኪር ስታርመር በማዘዛቸው አሜሪካ ደስተኛ አይደለችም።

    በተጨማሪም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ወደ ጦርነት ከመግባት ይልቅ ውጥረትን ለማርገብ ጥረት እንዲደረግ ያቀረቡትን ጥሪ ፕሬዝዳንት ትራምፕ ስታርመርን እንደ ዊኒስተን ቸርችል አይደሉም” ሲሉ ተችተዋቸዋል።

  10. ቪዲዮ፡ በዱባይ አውሮፕላን ማረፊያ አቅራቢያ የድሮን ጥቃት

    አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ የሚፈጽሙት ጥቃት ሰባተኛ ቀኑን ይዟል። ኢራንም በአጸፋው በእስራኤል እና የአሜሪካ አጋር ናቸው ባለቻቸው በሌሎች የመካከለኛው ምሥራቅ አገራት ላይ የሚሳዔል እና የድሮን ጥቃት እየፈጸመች ነው። ይህ ቪዲዮ በተባበሩት አረብ ኤምሬትስ ዱባይ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ አቅራቢያ የተፈጸመን ጥቃት ያሳያል።

  11. የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች በዛሬው ዕለት 16 ባለስቲክ ሚሳዔል እና 119 ድሮን እንደተተኮሰባት ገለጸች

    በዛሬው ዕለት ዱባይ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ቅጥር ውስጥ ጥቃት ተፈጽሟል

    የፎቶው ባለመብት, X

    የምስሉ መግለጫ, በዛሬው ዕለት ዱባይ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ቅጥር ውስጥ ጥቃት ተፈጽሟል

    የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች፤ የኢራን ፕሬዝዳንት ማስዑድ ፔዜሽኪያን ቀድመው በማያጠቁ ጎረቤት አገራት ላይ ጥቃት እንደማይፈጸም በገለጹበት በዛሬው ዕለት የተተኮሱባትን 15 ባለስቲክ ሚሳዔሎች እና 119 ድሮኖች ማክሸፏን ገለጸች።

    በሌላ በኩል በዱባይ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ቅጥር ውስጥ በድሮን የተፈጸመ የሚመስል ጥቃትን የሚያሳይ ቪዲዮ ተሰራጭቷል።

    የአገሪቱ መከላከያ ሚኒስቴር ባወጣው መረጃ፤ የአየር መከላከያ ስርዓቱ 16 ባለስቲክ ሚሳዔሎችን እንደለየ እና ከዚያ ውስጥ 15 ያህሉ ተጠልፈው ባሕር ላይ መውደቃቸውን አስታውቋል።

    ባለስቲክ ሚሳዔሎች በአብዛኛው በሮኬት የሚታገዙ የረጅም ርቀት መሣሪያዎች ሲሆኑ ለማምረትም በሚሊዮኖች የሚቆጠር ዶላር ይጠይቃሉ። ዝቅ ብለው የሚበርሩት ሰው አልባዎቹ ድሮኖች ደግሞ በጣም ባነሰ ዋጋ ይመረታሉ።

    የኢራን ጦርነት ከተጀመረ አንስቶ ባለው የአንድ ሳምንት ጊዜ ውስጥ ዩናይትድ አረብ ኤምሬት ውስጥ በተፈጸሙ የድሮን ጥቃቶች ሦስት ሰዎች የተገደሉ ሲሆን 112 ሰዎች ቀላል ጉዳት ደርሶባቸዋል።

    ዛሬ በኤምሬትስ አየር መንገድ የተፈጸመውም የድሮን ጥቃት ሊሆን እንደሚችል ቢቢሲ ቬሪፋይ ያረጋገጠው ቪዲዮ አሳይቷል።

    በአየር ማረፊያው ደቡባዊ ክፍል ከሚገኘው የማምረቻ ስፍራ የተቀረጸው ቪዲዮ፤ ከአየር ማረፊያው ተርሚናል ሕንጻ አቅራቢያ ተፈጠረን ፍንዳታ ያሳያል። ቪዲዮውን የቀረጸው ሰው “ሌላ ድሮን” በማለት ሲናገር ይሰማል።

    ሰው አልባው በራሪ ከመጋጨቱ በፊት በድሮን ሞተር ከሚፈጠር ድምጽ ጋር ተመሳሳይነት ያለው ድምጽ ይደመጣል። ፍንዳታው ከመፈጠሩ አስቀድሞ አንድ ቁስ በከፍተኛ ፍጥነት ወደ ታች ሲወርድ የሚታይ ቢሆንም ምን እንደሆነ ማረጋገጥ አልተቻለም።

    ጥቃቱ በተፈጸመበት የአየር መንገዱ ስፍራ አቅራቢያ አራት አውሮፕላኖች እንደቆሙ ቪዲዮው ያሳያል።

    ኤምሬትስ አየር መንገድ ዛሬ ጠዋት ሥራ እንዳቋረጠ የሚገልጽ መረጃ ካሰራጨ በኋላ አጥፍቶታል። ቀጥሎም እንደገና አገልግሎት መጀመሩን የሚገልጽ ልጥፍ አጋርቷል።

  12. ፕሬዝዳንት ትራምፕ “ዛሬ ኢራን እጅግ በኃይለኛው ትመታለች” አሉ

    የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ “ዛሬ ኢራን እጅግ በኃይለኛው ትመታለች” ሲሉ ከዚህ ቀድም ዒላማ ያልነበሩ የቴህራን ባለሥልጣናት ላይ ጥቃት ሊፈጸም እንደሚችል ገለጹ።

    ፕሬዝዳንቱ ትሩዝ ሶሻል በተባለው የማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሑፍ፤ የኢራኑ ፕሬዝዳንት ማስዑድ ፔዜሽኪያን በሰዓታት በፊት ያደረጉትን ንግግር ጠቅሰዋል።

    ፔዜሽኪያን፤ በኢራን ጥቃት የተፈጸመባቸውን ጎረቤት አገራት ይቅርታ ጠይቀው፤ ከአሁን በኋላ ቀድመው ጥቃት ካልፈጸሙ በስተቀር ጎረቤቶችን እንደማያጠቁ ተናግረው ነበር።

    ትራምፕ በልጥፋቸው፤ “ኢራን ይቅርታ መጠየቋን እና በመካከለኛው ምሥራቅ ለሚገኙ ጎረቤቶቿ እጅ መስጠቷን፣ እንዲሁም ከአሁን በኋላ ወደ እነርሱ እንደማትተኩስ ቃል መግባቷን" ገልጸዋል።

    "ይህ ቃል የተገባው በማያቋርጠው የአሜሪካ እና እስራኤል ጥቃት ምክንያት ብቻ ነው" ብለዋል።

    ኢራን የመካከለኛው ምሥራቅ አገራትን እንደማታጠቃ ብትናገርም ወደ ጎረቤቶቿ የሚደርሱ ጥቃቶች ሙሉ በሙሉ አልቆሙም።

    በዱባይ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ አቅራቢያ የድሮን ጥቃት መፈጸሙን የሚያመለክት መረጃ የወጣ ሲሆን ኳታርም የተወነጨፈባትን ሚሳዔል ማክሸፏን ገልጻለች።

    ትራምፕ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሁፍ፤ “ዛሬ ኢራን እጅግ በኃይለኛው ትመታለች” ብለዋል። የአገሪቱ ጦርም ጥቃት የሚፈጸምባቸውን አዲስ ዒላማዎች እየለየ መሆኑን ገልጸዋል።

    ፕሬዝዳንቱ፤ “ሙሉ በሙሉ የሆነ ውድመት እና እርግጠኛ ሞት” የማድረስን ሀሳብ “በከፍተኛ ሁኔታ እያጤኑት” እንደሆነ ጠቅሰዋል።

    በአዲሱ እርምጃ ዒላማ የሚሆኑት "እስካሁን ድረስ ጥቃት ሊሰነዘርባቸው ያልታሰቡ አካባቢዎች እና በርካታ ሰዎች" እንደሆኑም ጠቁመዋል። ይህ የሚሆነው “በኢራን መጥፎ ባህሪ” ምክንያት ነው ያሉት ትራምፕ ተጨማሪ መረጃ አልሰጡም።

  13. የአሜሪካ ነዳጅ ተቋማት ሠራተኞቻቸውን ከኢራቅ ማስወጣት ጀመሩ

    የነዳጅ ተቋማት ሠራተኞች በሳፍዋን ድንበር በኩል ወደ ኩዌት እየተሻገሩ ነው

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የነዳጅ ተቋማት ሠራተኞች በሳፍዋን ድንበር በኩል ወደ ኩዌት እየተሻገሩ ነው

    በመካከለኛው ምሥራቅ የሚሠሩ የውጭ አገራት የነዳጅ ድርጅቶች ሠራተኞቻቸውን ከኢራቅ ማስወጣት እንደጀመሩ ተገለጸ።

    ሮይተርስ የዜና ወኪል ያገኛቸው ምሥሎች፤ የነዳጅ ተቋማት ሠራተኞች በሳፍዋን ድንበር በኩል ወደ ኩዌት ሲሻገሩ ያሳያሉ።

    ሄሊቡርቶን የተባለው የአሜሪካ ነዳጅ አምራች የፀጥታ ኃላፊ መሐመድ ታሜህ “በኢራቅ ባለው የደኅንነት ስጋት ምክንያት የውጭ አገራት ሠራተኞች እየወጡ ነው። ወደ የት እንደሚሄዱ በቅርቡ እናያለን” በማለት ለሮይተርስ ተናግረዋል።

    አንድ ሳምንት በዘለው ግጭት ነዳጅ አምራች እና አከፋፋይ ተቋማት የጥቃት ዒላማ ሆነዋል።

    ኤችኬኤን የተባለው የአሜሪካ ነዳጅ አምራች “በኢራቅ በሚንቀሳቀሱ ሕገ ወጥ ቡድኖች” ጥቃት እንደደረሰበት ከተገለጸ በኋላ በአገሪቱ ያከናውን የነበረውን ሥራ ለማቋረጥ ተገድዷል።

    ኢራን፤ አሜሪካ እና እስራኤል በጥምረት ለከፈቱባት ጦርነት እየሰጠች ባለችው የአጸፋ ምላሽ ጥቃት ከተፈጸመባቸው ተቋማት መካከል የጦር ሰፈሮች እና ነዳጅ አምራቾች ይጠቀሳሉ።

    ቀደም ሲል የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ በሆርሙዝ ሰርጥ በኩል ሲጣልፍ የነበረ የነዳጅ ጫኝ መርከብ ላይ ጥቃት መፈጸሙን አስታውቋል።

  14. ኢራን በሆርሙዝ ወሽመጥ ሊያልፍ የነበረ ነዳጅ ጫኝ መርከብ መምታቷን አስታወቀች

    የኢራን ጦር መርከብ

    የፎቶው ባለመብት, AP

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ሲጣልፍ የነበረ የነዳጅ ጫኝ መርከብ ላይ ጥቃት መፈጸሙን አስታወቀ።

    አብዮታዊ ዘቡ በቴሌግራም ቻናሉ ባወጣው መረጃ፤ "ፕሪማ" የሚል ስያሜ ያለው ነዳጅ ጫኝ መርከብ በወሽመጡ በኩል “መተላለፍ እንደማይቻል” በባሕር ኃይሉ የተሰጠውን “ተደጋጋሚ ማስጠንቀቂያ ችላ በማለቱ በድሮን መመታቱን ገልጿል።

    “ከጠበኛ አገራት ጋር አጋር የሆኑ” ነዳጅ ጫኝ እና የንግድ መርከቦች በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ማለፍ እንደማይፈቀድላቸውም ወታደራዊ ኃይሉ አስገንዝቧል።

    በዓለም ላይ ካሉ ወሳኝ የኃይል ማጓጓዣ መስመሮች አንዱ የሆነው የሆርሙዝ ወሽመጥ፤ ከዓለም አቀፉ የነዳጅ እና ጋዝ አቅርቦት አንድ አምስተኛ የሚሆነው ይተላልፍበታል።

    በመካከለኛው ምሥራቅ እየተካሄደ ያለው ጦርነት የመርከብ መተላለፊያ መስመሩ ሙሉ እንዲቆም አድርጎታል። በዚህ ሳምንት መጀመሪያ የኢራን መንግሥት በመስመሩ ለመተላለፉ የሚሞክሩ መርከቦችን “በእሳት እንደሚያያይዝ” ዝቷል።

    ኢራን ይህንን ካለች በኋላ የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ “አስፈላጊ ከሆነ” የአሜሪካ ባሕር ኃይል በዚያ የሚያልፉ መርከቦችን እንደሚያጅብ ተናግረዋል።

    የኢራን አብዮታዊ ዘብ ቃል አቀባይ በበኩላቸው የአሜሪካ መርከቦች ለእጀባ ወደ አካባቢው እንዲልኩ አደፋፍረዋል።

    ቃል አቀባዩ አሊመሐመድ ናኢኒ፤ “ኢራን የነዳጅ ማመላለሻ መርከቦችን የማጀብ እርምጃን በደስታ ትቀበላለች። የአሜሪካ ኃይሎችም የሆርሙዝ ወሽመጥን ለመሻገር በዚያ ይገኛሉ። በነገራችን ላይ እኛም መምጣታቸውን እየተጠባበቅን ነው" ሲሉ ለአገሪቱ መንግሥት መገናኛ ብዙኃንን መናገራቸውን ሮይተርስ ዘግቧል።

    "አሜሪካውያን ማንኛውም ውሳኔ ላይ ከመድረሳቸው በፊት (በአውሮፓውያኑ) 1987 የአሜሪካው ግዙፍ የነዳጅ ጫኝ መርከብ 'ብሪጅተን' ላይ የተፈጠረውን እሳት እንዲሁም በቅርቡ ዒላማ የተደረጉ የነዳጅ ማመላለሻ መርከቦችን እንዲያስታውሱ እንመክራለን” ብለዋል።

  15. ኢራን በተቀናቃኞቿ ላይ ስጋትን የፈጠረችበት አጥፍቶ ጠፊ ድሮን

    አጥፍቶ ጠፊ ድሮን

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በአሜሪካ እና በእስራኤል የተከፈተባትን ጥቃት ተከትሎ ኢራን በእስራኤል እና በሌሎች የመካከለኛው ምሥራቅ አገራት ላይ የአጸፋ ጥቃት በሚሳዔል እና በድሮኖች እየፈጸመች ነው።

    በተለይ ደግሞ ራሷ የምትሠራቸው ድሮኖች በተቀናቃኞቿ ላይ ከፍተኛ ስጋትን ፈጥረዋል።

    እነዚህ ሻሂድ-136 የሚባሉት ካሚካዚ (አጥፍቶ ጠፊ) ድሮኖች በአንድ ላይ በብዛት ስለሚወነጨፉ ለመጥለፍ እና ለማምከን አስቸጋሪ ናቸው። ከሌሎች ወታደራዊ ድሮኖች በተለየ ኢራን በርካሽ የምታመርታቸው እነዚህ ድሮኖች የሚያደርሱት ጉዳት ቀላል የሚባል አይደለም። የሻሂድ-136 ድሮን ገጽታን በአጭሩ ምን ይመስላል?

    ሻሂድ-136 ድኦን
  16. የተመድ ዋና ጸሐፊ የመካከለኛው ምሥራቅ ግጭት “ከሁሉም ቁጥጥር ውጪ ሊሆን ይችላል” ሲሉ አስጠነቀቁ

    የተባበሩት መንግሥታት ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የተባበሩት መንግሥታት ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ፤ የመካከለኛው ምሥራቅ ሁኔታ “ከዚህ በላይ አሳሳቢ ሊሆን አይችልም” ሲሉ እየተባባሰ የመጣው ግጭት እንዲቆም ጠየቁ።

    ዋና ጸሐፊው ኤክስ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት መልዕክት፤ "በመካከለኛው ምሥራቅ እና ከዚያም ባሻገር የሚፈጸሙት ሕገ ወጥ ጥቃቶች በመላው ቀጣናው የሚገኙ ንጹኃን ላይ ከፍተኛ ስቃይ እና ጉዳይ እያደረሱ ነው” ብለዋል።

    የቀጣናው ሁኔታ፤ “ለዓለም ኢኮኖሚ፤ በተለይም ተጋላጭ በሆኑ ወገኖች ላይ አስከፊ ስጋት ደቅኗል" ሲሉም አሳስበዋል።

    "ሁኔታው ከሁሉም ቁጥጥር ውጪ በሆነ ሁኔታ ሊባባስ ይችላል። ውጊያውን አቁሞ ወደ ተጨባጭ የዲፕሎማሲ ንግግር ለመግባት ጊዜ አሁን ነው። [ሁኔታው] ከዚህ በላይ አሳሳቢ ሊሆን አይችልም” ሲሉም አስጠንቅቀዋል።

    የተባበሩት መንግሥታት የሰብአዊ ጉዳዮች እና የአደጋ ጊዜ እርዳታ ምክትል ዋና ጸሐፊ የሆኑት ቶም ፍሌቸር በበኩላቸው፤ ለጦርነቱ እየዋለ ስላለው “ከፍተኛ መጠን ያለው ገንዘብ” አንስተዋል።

    "ፖለቲከኞች እርዳታ ለሚሹ ወገኖች የሚውለውን በጀት በማቋረጥ በሚወስዱት እርምጃ መኩራራታቸውን” የጠቀሱት ፍሌቸር፤ መሪዎቹ ለጦርነት ገንዘብ እያዋሉ መሆኑን በማንሳት ወቅሰዋል።

    አክለውም፤ "ገዳይ የሆነ ቴክኖሎጂ ላይ እና ያለ ተጠያቂነት የሚፈጸመው ግድያን በተመለከተ ያለው ኅብረት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መሆኑን እየተመለከትን ነው” ብለዋል።

  17. ኢራን ከአሁን በኋላ “አስቀድመው ካላጠቁ” በስተቀር ጎረቤቶቿ ላይ ጥቃት እንደማትፈጸም አስታወቀች

    የኢራን ፕሬዝዳንት ማስዑድ ፔዜሽኪያን

    የፎቶው ባለመብት, IRNA

    የኢራን ፕሬዝዳንት ማስዑድ ፔዜሽኪያን በአገሪቱ ብሔራዊ ቴሌቪዥን በቪዲዮ ባስተላለፉት መልዕክት፤ ጥቃት የተፈጸመባቸውን ጎረቤት አገራት ይቅርታ ጠየቁ።

    “ጥቃት የደረሰባቸውን አገራት ይቅርታ መጠየቅን አስፈላጊ ሆኖ አግኝቼዋለሁ” ሲሉ ፕሬዝዳንቱ ተናግረዋል።

    “ጎረቤት አገራትን የመውረር ሐሳብ የለንም” ያሉት ፕሬዝዳንቱ፤ “ሰላም እና መረጋጋትን ለማስፈን” ሲባል ቀጣናዊ ትብብር እንዲኖር ጠይቀዋል።

    ፔዜሽኪያን አክለውም የአገሪቱ አመራር ጎረቤቶች ላይ የሚፈጸመው ጥቃትን በተመለከተ ውሳኔ ማሳለፉን ተናግረዋል። የአገሪቱ ጦር ኃይሎች “ከአሁን በኋላ ቀድመው ካላጠቁ በስተቀር ጎረቤት አገራት ላይ ጥቃት እንዳይፈጽሙ” እንደታዘዙ አስታውቀዋል።

    “ከአሁን ጀምሮ፣ እነዚያ አገራት ካልተጠቃን በስተቀር ጎረቤት አገራትን ማጥቃት ወይም ሚሳዔል መተኮስ የለባቸውም። ይህንን በዲፕሎማሲ መፍታት አለብን ብዬ አስባለሁ” ብለዋል።

    ፕሬዝዳንቱ አክለው ጥቃቶቹ የተፈጸሙት በወታደራዊ አመራሮች መካከል በተፈጠረ የመረጃ ልውውጥ ስህተት ምክንያት እንደሆነ ገልጸዋል።

    ይሁን እንጂ ይህ የፕሬዝዳንቱ ንግግር የተላለፈው ኢራን ቅዳሜ ጠዋት ላይ በባህሬን፣ ሳዑዲ አረቢያ እና የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ላይ ተደጋጋሚ ጥቃት ከፈጸመች በኋላ እንደሆነ የዜና ወኪሉ አሶሺዬትድ ፕሬስ ዘግቧል።

    በተጨማሪም የኢራኑ ፕሬዝዳንት “ይህንን አጋጣሚ በመጠቀም ኢራን ላይ ጥቃት ለመፈጸም እያሰቡ ያሉ [አካላት] የኢምፔሪያሊዝም አሻንጉሊት እንዳይሆኑ” ሲሉ ተናግረዋል። እስራኤል እና አሜሪካን መደገፍ “የክብር እና የነጻነት መንገድ አይደለም” ሲሉም ተደምጠዋል።

  18. እስራኤል በሊባኖስ የሚገኝ የተመድ ይዞታ ላይ በፈጸመችው ጥቃት ሰላም አስከባሪዎች ቆሰሉ

    በዋና ከተማዋ ቤይሩት ደቡባዊ ክፍሎች የአየር ጥቃት ተፈጽሟል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, በዋና ከተማዋ ቤይሩት ደቡባዊ ክፍሎች የአየር ጥቃት ተፈጽሟል

    ሊባኖስ ውስጥ የምትፈጽመውን ጥቃት ያጠናከረችው እስራኤል፤ በደቡባዊ የአገሪቱ ክፍል የሚገኝ የተባበሩት መንግሥታት ሰላም አስከባሪ ኃይል ይዞታን መምታቷን የሊባኖስ ፕሬዝዳንት ጆሴፍ አውን ገለጹ።

    በጥቃቱ ሰላም አስከባሪ ኃይሉ ውስጥ እያገለገሉ ያሉ ጋናውያን ወታደሮች መጎዳታቸውን ፕሬዝዳንቱ በመግለጫቸው አስታውቀዋል።

    የጋና ጦር ኃይል በበኩሉ ሁለት ወታደሮች በጥቃቱ ከፍተኛ አካላዊ እና ሥነ ልቦናዊ ጉዳት እንደደረሰባቸው ተናግሯል። የሰላም አስከባሪዎቹ መመገቢያ ማዕከል በጥቃቱ ሙሉ በሙሉ እንደተቃጠለም ተገልጿል።

    የፈረንሳይ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን እስራኤል የተባበሩት መንግሥታት ይዞታ ላይ ጥቃት መፈጸሟን አውግዘዋል።

    “የተባበሩት መንግሥታት ኃይሎች በደቡባዊ ሊባኖስ መረጋጋት ለማምጣት ቁልፍ ሚና ይጫወታሉ፤ ዛሬ የአስከባሪው አባላት ላይ የተፈጸመውን ተቀባይነት የሌለው ጥቃት አወግዛለሁ ብለዋል።

    ከሊባኖሱ ፕሬዝዳንት ጋር የተነጋገሩት የሶርያው መሪ አሕመድ አልሻራ በበኩላቸው የሁለቱም አገራት “ሉዓላዊነት እና የግዛት አንድነት” መከበር እንዳለበት አጽንኦት ሰጥተዋል።

    እስራኤል፤ በሊባኖስ የሚገኘው ሄዝቦላህ ላይ የከፈተችውን ጥቃት ተከትሎ በዋና ከተማዋ ቤይሩት ውስጥ ከፍተኛ ፍንዳታዎች ተሰምተዋል። የአየር ጥቃቱን ተከትሎ በመቶ ሺህዎች ሚቀጠሩ ነዋሪዎች ደቡባዊውን የከተማውን ክፍል ለቅቀው እንዲወጡ በእስራኤል ትዕዛዝ ተሰጥቷቸዋል።

    እስራኤል ከሰኞ አንስቶ ሊባኖስ ውስጥ በፈጸመቻቸው ጥቃቶች 217 ሰዎች እንደተገደሉ እና 798 ሰዎች እንደቆሰሉ የአገሪቱ ጤና ሚኒስትር አስታውቋል።

    በሊባኖስ ዋና ከተማ የተፈጸመው ጥቃት

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, በሊባኖስ ዋና ከተማ የተፈጸመው ጥቃት
  19. ሚሳዔሎች የጫነ የአሜሪካ የጦር አውሮፕላን ዩናይትድ ኪንግደም ደረሰ

    የአሜሪካ የጦር አውሮፕላን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    24 ሚሳዔሎች የጫነ ግዙፍ የአሜሪካ የጦር አውሮፕላን ዩናይትድ ኪንግደም ደረሰ። ‘ቢ-1 ላንሰር’ የተባለው የአሜሪካ ቦምብ እና ሚሳዔል ጫኝ የጦር አውሮፕላን ዩኬ፣ ግላውስታሼር በሚገኘው የአሜሪካ አየር ኃይል ያረፈው ትናንት አርብ ነው።

    አሜሪካ በዩኬ የጦር አውሮፕላኗን እንድታሳርፍ ጠቅላይ ሚኒስትር ኪር ስታርመር ፈቅደዋል።

    ሮያል ኤርፎርስ ኤርፊልድ በተባለው ጦር ሰፈር ያረፈው የአሜሪካ የጦር አውሮፕላን ጥቅም ላይ መዋል የሚችለው የኢራንን የሚሳዔል ጥቃት ለመከላከል ብቻ እንደሆነ ዩኬ አስታውቃለች።

    የጦር አውሮፕላኑ አራት አብራሪዎች ያሉት ሲሆን 41.8 ሜትር ርዝመት እና 86 ቶን ክብደት አለው። ቦይንግ እንደሚለው፤ አሜሪካ ካሏት የአየር መሣሪያዎች ፈጣኑ ሲሆን፤ በሰዓት 1,448.4 ኪሎሜትር ይበራል።

    የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ፒት ሄግሴት “በኢራን ላይ የሚፈጸመው ጥቃት እጅጉን ሊባባስ ነው” ሲሉ ያለፈው ሐሙስ አስጠንቅቀዋል።

    “ተጨማሪ ተዋጊ ጀቶች ይሰማራሉ፤ የመከላከል ሥራውንም ያጠናክራሉ። ጥቃት የሚፈጽሙበት ፍጥነት እና ጊዜም ይጨምራል” ብለዋል።

  20. ሩሲያ የአሜሪካ ጦርን ለማጥቃት የሚውል መረጃ ለኢራን ማቅረቧ ተዘገበ

    ሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ እና ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ሩሲያ፤ በመካከለኛው ምሥራቅ የሚገኙ የአሜሪካ ጦር መርከቦች እና ሌሎች ወታደራዊ ይዞታዎች ላይ ጥቃት ለመፈጸም ሊውል የሚችል መረጃ ለኢራን ማቅረቧን ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ባለሥልጣናት እንደነገሩት የዜና ወኪሉ አሶሺዬትድ ፕሬስ ዘገበ።

    በአሜሪካ የቢቢሲ አጋር ሆነው ሲቢኤስ ኒውስ ያነጋገራቸው ሌላ የአሜሪካ ባለሥልጣንም፤ ሩሲያ ዋሽንግተን በቀጣናው ያላትን ይዞታ የተመለከተ መረጃ ለኢራን እያቀረበች መሆኑን ተናግረዋል።

    ስለዚህ ጉዳይ የተጠየቁት አሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ፒት ሄግሴት በበኩላቸው፤ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ “ማን ማንን እያናገረ እንደሆነ ያውቃሉ” ብለዋል።

    ኤፒ ያነገጋገራቸው ምንጮች ይህንን ቢናገሩም፤ ሩሲያ መረጃ በማቅረብ የኢራንን እርምጃ እየመራች ነው የሚለው በአሜሪካ የስለላ መረጃ የተረጋገጠ እንዳልሆነ አክለዋል ተብሏል።

    ይህ መረጃ፤ ሩሲያ ከሳምንት በፊት አሜሪካ እና እስራኤል ኢራን ላይ በከፈቱት ጥቃት ውስጥ የመሳተፍ ፍላጎት እንዳላት የሚጠቁም የመጀመሪያ ምልክት ተደርጎ መወሰዱን ዘገባው ያመለክታል።

    በኒውክሌር ፕሮግራሟ ምክንያት ለረዥም ጊዜ መገለል ከደረሰባት ኢራን ጋር ወዳጅነታቸውን ካስቀጠሉ አገራት አንዷ ሩሲያ ነች።

    የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ሄግሴት ከሲቢኤስ ኒውስ ’60 ሚኒትስ’ የተሰኘው ፕሮግራም ጋር ባደረጉት ቃለ መጠይቅ፤ ሩሲያ በቀጣናው ስለሚገኘው የአሜሪካ ጦር እንቅስቃሴ ለኢራን መረጃ እያቀረበች ነው ስለመባሉ ተጠይቀዋል።

    ሚኒስትሩ ምላሽ ሲሰጡ አሜሪካ “ሁሉንም ነገር እየተከታተለች” እንዲሁም በውጊያ ዕቅዷ ውስጥ እያካተተች እንደሆነ ተናግረዋል።

    “የአሜሪካ ሕዝብ፤ የጦር ኃይሎች ጠቅላይ አዛዡ ማን ማንን እያነጋገረ እንደሆነ እንደሚያውቁ እርግጠኛ መሆን ይችላል” ብለዋል። “በይፋ የሚደረግም ሆነ በጀርባ የሚከወን፤ መፈጠር የሌለበትን ማንኛውም ነገር እየተጋፈጥን ነው፣ በኃይል እየተጋፈጥነው ነው” ሲሉም ለሲቢኤስ ኒውስ ምላሽ ሰጥተዋል።

    በሌላ በኩል የሩሲያ ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን ከኢራኑ ፕሬዝዳንት ማስዑድ ጋር መነጋገራቸው እና ሐዘናቸውን መግለጻቸውን ክሬምሊን አስታውቋል። ሩሲያ የኃይል እርምጃዎች መቆም አለባቸው የሚል አቋም እንዳላትም ገልጸዋል ተብሏል።

    የፑቱን ጽሕፈት ቤት ያወጣው መረጃ እንደሚያመክተው፤ ሁለቱ አካላት ግንኙነታቸውን ለማስቀጠል ተስማምተዋል።