የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች የኒውክሌር ጣቢያ አቅራቢያ ጥቃት መፈጸሙ ተገለጸ

የፎቶው ባለመብት, AFP
የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች እሑድ ዕለት የኒውክሌር ኃይል ማመንጫዋ አቅራቢያ የተፈጸመው የድሮን ጥቃት እሳት እንዲነሳ ማድረጉን አስታወቀች።
ክስተቱን “አደገኛ [የግጭት] መባባስ” ስትል የጠራችው ኤምሬቶች፤ ባለሥልጣናት ጥቃቱ ከየት እንደተፈጸመ እየመረመሩ መሆኑን ገልጻለች።
የአገሪቱ መከላከያ ሚኒስቴር እንደገለጸው ድሮኖች ወደ ኤምሬቶች ግዛት የገቡት “በምዕራብ የድንበር አቅጣጫ" በኩል ነው።
ሁለቱ ድሮኖች እንደተጠለፉ እና ሦስተኛው ግን በአቡ ዳቢ የሚገኘው የባራካህ የኒውክሌር ኃይል ማመንጫ "ከውስጣዊው ቅጥር ግቢ ይዞታ ውጭ" የሚገኝ የኤሌክትሪክ ጄነሬተርን እንደመታ ተገልጿል። እሳቱም የተነሳው በዚሁ ምክንያት ነው ተብሏል።
በጥቃቱ ጉዳት አለመድረሱን የሚናገሩት ባለሥልጣናቱ፤ በአካባቢው የራዲዮሎጂካል ደኅንነት ደረጃ ላይም ተጽዕኖ አለማሳደሩን ገልጸዋል።
የኤምሬቶች የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ክስተቱን "ተቀባይነት የሌለው የጥቃት ድርጊት" በማለት ጠርቶታል። የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ለማንኛውም ጠበኛ ድርጊት ምላሽ የመስጠት መብት እንዳላት አስታውቋል።
ሚኒስቴሩ "ሰላማዊ የኒውክሌር ኃይል ተቋማትን ዒላማ ማድረግ ግልጽ የዓለም አቀፍ ሕግ፣ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ስምምነት እና የሰብአዊ ሕግ መርሆዎች ጥሰት ነው" ብሏል።
የኤምሬቶች መከላከያ ሚኒስቴር በበኩሉ "የአገሪቱን ደኅንነት ለማዳከም የሚደረጉ ማናቸውንም ሙከራዎች በጽናት እንደሚጋፈጥ" አስታውቋል።
የአገሪቱ ባለሥልጣናት ድሮኑ ከየት እንደተተኮሰ እስካሁን አልገለጹም። ከዚህ ቀደም ግን ኤምሬቶች ከጦርነቱ መነሳት ወዲህ በነዳጅ እና በኢኮኖሚ መሠረተ ልማቶቿ ላይ ከተፈጸሙ ጥቃቶች ጀርባ ኢራን እንዳለች በመግለጽ በተደጋጋሚ ከስሳለች።
የተባበሩት መንግሥታት የኒውክሌር ተቆጣጣሪ ተቋም ሁኔታውን በቅርበት እየተከታተለ መሆኑን ገልጿል። የተቋሙ ዋና ዳይሬክተር ራፋኤል ግሮሲ በክስተቱ “ከፍተኛ ስጋት” እንደገባቸው ተናግረዋል።
ዋና ዳይሬክተሩ በዓለም አቀፉ የአቶሚክ ኃይል ኤጀንሲ የኤክስ ገጽ በወጣው መግለጫቸው፤ "የኒውክሌር ደኅንነትን አደጋ ላይ የሚጥል ወታደራዊ እንቅስቃሴ ተቀባይነት የለውም" ብለዋል።

