ቀጥታ, ከፕሬዝዳንት ትራምፕ ጋር የተወዛገቡት ጠቅላይ ሚኒስትር ኔታኒያሁ ኢራን “በእሳት እየተጫወተች ነው” አሉ

ከፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ጋር በስልክ በተደረገ ውይይት ወቅት መወዛገባቸው የተነገረው የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ በእሳት እየተጫወተች ነው ያሏት ኢራን ያላትን የዩራኒየም ክምችት ለማስወገድ እንዳልተስማማች፤ ነገር ግን የሚደርስባት ጫና እየበረታ መሆኑን ተናገሩ።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ከፕሬዝዳንት ትራምፕ ጋር የተወዛገቡት ጠ/ሚኒስትር ኔታኒያሁ ኢራን “በእሳት እየተጫወተች ነው” አሉ

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ እና ጠ/ሚኒስትር ኔታኒያሁ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ፕሬዝዳንት ትራምፕ እና ጠ/ሚኒስትር ኔታኒያሁ

    የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ በእሳት እየተጫወተች ነው ያሏት ኢራን ያላትን የዩራኒየም ክምችት ለማስወገድ እንዳልተስማማች ነገር ግን የሚደርስባት ጫና እየበረታ መሆኑን ተናገሩ።

    ከአሜሪካው ፕሬዝዳንት ጋር መወዛገባቸው የተነገረው ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከትራምፕ ጋር በኢራን ጉዳይ ተመሳሳይ አቋም እንዳቸላው ተናግረዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለሲኤንቢሲ በሰጡት ቃለ ምለልስ ኢራን ከአሜሪካ ጋር የምታደርገው ድርድር ካለስኬት ቢቋጭ ብዙም እንደማያሳስባቸው እና የኢራን ጉዳይ ያላበቃ ቢሆንም ግን በከፍተኛ ሁኔታ መዳከሟን ገልጸዋል።

    ከኢራን ጋር ዳግም ወደ ሙሉ ጦርነት የመግባቱ ጉዳይ በፕሬዝዳንት ትራምፕ የሚወሰን መሆኑን እና ”የአሜሪካ እና የእስራኤል ኃይሎች ዝግጁ ናቸው። ኢራንም ይህንን ማወቅ አለባት፤ እነሱም ያውቃሉ ብዬ አስባለሁ። ነገር ግን በግልጽ እንደሚታየው በእሳት እየተጫወቱ ነው” ብለዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ኔታኒያሁ እና ፕሬዝዳንት ትራምፕ እስራኤል በሊባኖስ ውስጥ እያካሄደችው ካለው ጦርነት ጋር በተያያዘ ባለፉት ቀናት ሲዘገብ እንደነበረው በሁለቱ መሪዎች መካከል ጠንከር ለያ ንግግር መደረጉ ተገልጿል።

    ፕሬዝዳን ትራምፕ “ፖድ ዋን ፎርስ” ከተባለ ፖድካስት ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ ከኔታኒያሁ ጋር የጋለ ምልልስ ማድረቸጋውን አረጋግጠዋል።

    “አዎ [ጠንካራ ውይይት] አድርገናል። በጣም ተናድጄ ነበር፤ ሊባኖስ ውስጥ [ኔታኒያሁ] እያካሄደው ባለው ያልተቋረጠ ጦርነት ተረብሼ ነበር” በማለት ውይይታቸው ጠንከር ያለበትን ምክንያት አስረድተዋል።

    የኔታኒያሁ ጽህፈት ቤት ከፕሬዝዳንት ትራምፕ ጋር ስለተደረገው የስልክ ምልልስ በይፋ ከመናገር ቢቆጠብም ጠቅላይ ሚኒስረሩ ግን “እንደ ጥሩ ቤተሰብ አንዳንድ ጊዜ ስልታዊ ልዩነቶች አሉን” በማለት ጉዳዩን በማጣጣል የጋራ ዘላቂ አላማ እንዳላቸው አመልክተዋል።

    ኔታኒያሁ ጨምረውም ከኢራን ጋር በተያያዙ ጉዳዮች ላይ ከፕሬዝዳንት ትራምፕ ጋር ዘወትር ስመምነት እንዳላቸው ተናግረዋል።

  2. ኢራን በኩዌት አውሮፕላን ማረፊያ ላይ የድሮን ጥቃት ፈጽማ አንድ ሰው መገደሉ ተነገረ

    በአውሮፕላን ማረፊያው ላይ ጥቃቱ በደረሰበት ጊዜ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, በአውሮፕላን ማረፊያው ላይ ጥቃቱ በደረሰበት ጊዜ

    በኩዌት ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ላይ በተፈጸመ የኢራን የድሮን ጥቃት አንድ ሰው መገደሉን እና 60 ሰዎች መቁሰላቸውን አንድ የአገሪቱ ባለሥልጣን ተናገሩ።

    የኩዌት የመከላከያ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ጥቃቱን “የኢራን የወንጀል ድርጊት” ሲሉ የአገሪቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ደግሞ በጥቃቱ የዲፕሎማቲክ ተቋማት ላይ ጉዳት ደርሷል ብሏል።

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ጥቃቱ አሜሪካ ዛሬ ጠዋት በኢራን የነዳጅ ጫኝ መርከብ እና በቄሽም ደሴት ላይ ለፈጸመችው ጥቃት አጸፋ መሆኑን ገልጿል። ኢራን ቀደም ብላ በባሕረ ሰላጤው የሚገኙ የአሜሪካ ወደታራዊ ሰፈሮችን ዒላማ ማድረጓን አሳውቃ ነበር።

    አሜሪካ ጠዋት ላይ “ራስን የመከላከል” እርምጃ በኢራን ላይ መውሰዷን እና ወደ ኩዌት እና ባህሬን የተወነጨፉ የኢራን ሚሳኤሎችን መትታ ማክሸፏን ገልለጻች።

    በኩዌት አየር ማረፊያ ላይ በተፈጸመው የኢራን የድሮን ጥቃት የተገደለው ግለሰብ ሕንዳዊ ዜግንት ያለው መሆኑ ታውቋል።

    የሕንድ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ ጥቃቱን በማውገዝ በተጨማሪም ሌሎች በርካታ ዜጎቹ በጥቃቱ ጉዳት እንደደረሰባቸው ገልጿል።

    ዛሬ በኢራን እና በአሜሪካ መካከል የተካሄደው የአጸፋ ጥቃት መቋጫ ያላገኘው የሁለቱን አገራት ድርድር እንዲቋረጥ ሊያደርገው ይችላል የሚል ስጋት ፈጥሯል።

  3. ሩሲያ በምትቆጣጠረው የዩክሬን ግዛት በአውቶብስ ላይ በተፈጸመ የድሮን ጥቃት ሰባት ሰዎች ተገደሉ

    በዩክሬን የተሰራው እና ቫምፓየር በመባል የሚጠራው ድሮን

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, በዩክሬን የተሰራው እና ቫምፓየር በመባል የሚጠራው ድሮን

    ሩሲያ በምትቆጣጠረው የዩክሬን ግዛት አውቶብስ ላይ በተፈጸመ ጥቃት ሰባት ሰዎች መገደላቸውን እና አስራ አንድ መቁሰላቸውን ባለሥልጣናት አስታወቁ።

    ክሬምሊን በዩክሬን ምሥራቃዊ ዶኔትስክ ክልል የሾመቻቸው ዴኒስ ፑሺሊን ጥቃቱ ከሞስኮ ወደ ክሬሚያ ሲምፎሮፖል ይጓዝ በነበረ አውቶቡስ ላይ ረቡዕ ማለዳ መድረሱን ገልጸዋል።

    በተያያዘ ዜና ረቡዕ ማለዳ በሴይንት ፒተርስበርግ ጭስ የታየ ሲሆን፣ የዩክሬን ፕሬዝዳንት ቮሎድሚር ዜሌንስኪ የከተማዋ የነዳጅ ማከማቻ ላይ ጥቃት መፈጸማቸውን አረጋግጠዋል።

    ጥቃቱ የተፈጸመው ሩሲያ ዓለም አቀፉን የኢኮኖሚክ ፎረም በምታዘጋጅት ወቅት ነው።

    ሩሲያ ትናንት ማክሰኞ በዩክሬን ከተሞች ላይ በርካታ የድሮን ጥቃቶች ፈጽማ ሕጻናት እና ሴቶችን ጨምሮ ቢያንስ 22 ሰዎች ተገድለዋል።

    ፑሽሊን በድሮን ጥቃት በደረሰበት አውቶብስ ሰባት ሰዎች መግደላቸውን ገልጸው ጉዳት የደረሰባቸው 11 ሰዎች የሕክምና ክትትል እየተደረገላቸው ነው ብለዋል።

    ዩክሬን በአውቶቡስ ላይ ስለተፈጸመው የድሮን ጥቃት እስካሁን ያለችው ነገር የለም።

    ሩሲያ ሌሊቱን ከዩክሬን የተነሱ 350 ድሮኖችን መትታ መጣሏን አስታውቃለች።

  4. ኢራን በኩዌት አውሮፕላን ማረፊያ ላይ በፈጸመችው የድሮን ጥቃት በርካቶች መጎዳታቸው ተገለጸ

    የኩዌት ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ የመንገደኞች ማስተናገጃ በኢራን ድሮኖች ጥቃት ተፈጽሞበት በርካታ መንገደኞች ጉዳት ደርሶባቸዋል

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የኩዌት ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ የመንገደኞች ማስተናገጃ በኢራን ድሮኖች ጥቃት ተፈጽሞበት በርካታ መንገደኞች ጉዳት ደርሶባቸዋል

    የኢራን ድሮኖች የኩዌት አውሮፕላን ማረፊያ ላይ ረቡዕ ማለዳ ጥቃት መፈጸማቸውን ተከትሎ በረራዎች መቋረጣቸው ተገለጸ።

    በኩዌት የአውሮፕላን ማረፊያ ላይ ጥቃት የተፈጸመው ቴህራን እና ዋሺንግተን አንዳቸው በሌላኛቸው ላይ ጥቃት ከፈጸሙ በኋላ ሲሆን በርካታ ሰዎች መጎዳታቸውም ተገልጿል።

    ሁለት የኢራን ዜና ወኪሎች ቴህራን የተኩስ አቁሙን ለማራዘም ከአሜሪካ ጋር የምታደርገውን ንግግር ማቋረጧን ማክሰኞ ዕለት ዘግበዋል።

    ትራምፕ ግን ዘገባውን አጣጥለው ንግግሮች እየተካሄዱ ናቸው ብለዋል።

    የኩዌት መከላከያ ቃል አቀባይ ብርጋዴር ጄነራል ሳዑድ አብዱላዚዝ አል ኦታእቢ “በርካታ ጥቃት ፈጻሚ ድሮኖች” የኩዌት ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ የመንገደኞች ማስተናገጃን ዒላማ ማድረጋቸውን ጠቅሰዋል።

    በጥቃቱ የመንገደኞች ማስተናገጃው ክፉኛ መጎዳቱን የገለጹ ሲሆን “በርካታ ሰዎችን” አቁስሏል ብለዋል።

    የአውሮፕላን ማረፊያው በኢራን ጦርነት ምክንያት ተዘግቶ ከቆየ በኋላ ለአገልግሎት ክፍት የሆነው ከሁለት ቀናት በፊት ግንቦት 24/2018 ዓ.ም. ነበር።

    ባለፈው ሳምንት ማክሰኞ የአሜሪካ ጦር ኢራን በኩዌት እና ባህሬን ላይ ጥቃት መፈጸሟን ጠቅሶ በወታደራዊ ተቋማቷ ላይ የአጸፋ ምላሽ ድብደባ ማካሄዱን አስታውቋል።

    የአሜሪካ ጦር አክሎም በኩዌት የሚገኙ የጦር ሰፈሮቹን ዒላማ ያደረጉ “በርካታ ድሮኖችን መትተን ጥለናል” ሲል አስታውቋል።

    የኢራን ፈጥኖ ደራሽ አብዮታዊ ዘብ በባህሬን የሚገኝ የአሜሪካ ባሕር ኃይል ዋና ማዘዣ እና ኩዌትን በስም ሳይጠቅስ ሌላ አገር ላይ ጥቃት መፈጸሙን ገልጿል።

    አክሎም ጥቃቱን የፈጸመው የአሜሪካ ጦር የጣለውን እገዳ ለማለፍ እየተንቀሳቀሰች የነበረች ነዳጅ ጫን መርከብ ሞተር ላይ ጥቃት መፈጸሙን ተከትሎመሆኑን ጠቅሷል።

    አብዮታዊ ዘቡ በመግለጫው “ከዚህ በፊት ለማንኛውም ጥቃት የምንሰጠው ምላሽ የተለየ እና የከፋ እንደሚሆን ተናግረን በነበረው መሠረተ እረምጃውን ወስደናል” ብሏል።

    የኩዌት ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ የመንገደኞች ማስተናገጃ በኢራን ድሮኖች ጥቃት ተፈጽሞበት በርካታ መንገደኞች ጉዳት ደርሶባቸዋል

    የፎቶው ባለመብት, reuters

  5. አሜሪካ የኢራን ግዙፍ የክሪፕቶ መገበያያ ከአብዮታዊ ዘቡ ጋር ግንኙነት አለው በሚል ማዕቀብ ጣለች

    የኢራንን ባንዲራ ያዘ ሰው

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    አሜሪካ ማክሰኞ ዕለት የኢራን ግዙፍ የክሪፕቶከረንሲ መገበያያ የቴህራን መንግሥት እና ስማቸው በጥቁር መዝገብ ላይ የሰፈሩ ኩባንያዎች የምዕራባውያንን ማዕቀብ ለማለፍ ያገለግላል በሚል ማዕቀብ ጣለች።

    ሮይተርስ የዜና ወኪል በግንቦት ወር ኖቢቴክስ (Nobitex) የሚባለው የክሪፕቶከረንሲ መገበያያ ከአገሪቱ ሕጋዊ የገንዘብ ሥርዓት ጋር በትይዩነት ለማዕከላዊ ባንኩ እና ለአብዮታዊ ዘቡ እያገለገለ መሆኑን በመጥቀስ ዘግቦ ነበር።

    ዘገባው አክሎም ኖቢቴክስ ኢንተርኔት በተዘጋበት ወቅትም አገልግሎት ሲሰጥ መቆየቱን አመልክቶ በሚሊዮን ዶላሮች የሚቆጠሩ ግብይቶችን ማካሄዱን አሳይቷል።

    የአሜሪካ ግምጃ ቤት ኃላፊ ስኮት ቤሴንት ማክሰኞ ዕለት ባወጡት መግለጫ “የኢራን ኢኮኖሚ እየተንኮታኮተ ባለበት ወቅት አገዛዙ ለራሱ እኩይ አጀንዳው የዲጂታል መገበያያዎችን ማዕቀብ ለማምለጥ እና ሃብት ከአገር ውጭ ለማሻገር መጠቀም መርጧል” ብለዋል።

    የሮይተርስ ዘገባ እንደሚያሳየው ኖቢቴክስ ከኢራናውያን ቤተሰቦች በተገኙ ወንድማማቾች የተመሠረተ ሲሆን፣ ከአዲሱ ጠቅላይ መሪ ጋር ጥብቅ ቁርኝት አላቸው።

    የአሜሪካ ግምጃ ቤት ሁለቱ ወንድማማቾች ላይ ማዕቀብ መጣሉን ማክሰኞ ዕለት አስታውቋል።

    ኖቢቴክስ ለኢራን መንግሥት “ጠንካራ ድጋፍ” እየሰጠ ነው፤ እንዲሁም ለአብዮታዊ ዘቡ እና ለአገሪቱ ማዕከላዊ ባንክ “በርካታ ቁጥር ያለው” የዲጂታል ግብይቶችን አመቻችቷል ብሏል።

    "በኢራን ውስጥ አሜሪካ ጦርነት መክፈቷን ተከትሎ ኖቢቴክስ የኢንተርኔት አገልግሎት ቢቋረጥም የአገዛዙን ሀብት ለመከላከል በኢራን ውስጥ ንብረቶችን እና ገንዘቦችን ለማንቀሳቀስ ሚና ተጫውቷል።"

  6. እስራኤል ከሄዝቦላህ ጋር ከፊል ተኩስ አቁም ከተስማማች በኋላ በደቡባዊ ሊባኖስ ጥቃቶችን ፈጸመች

    እስራኤል በደቡባዊ ሊባኖስ የምትፈጽመውን ጥቃት ቀጥላለች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ኢራን ማክሰኞ ዕለት በደቡባዊ ሊባኖስ የምትፈጽመውን ጥቃት የቀጠለች ቢሆንም በኢራን ከሚደገፈው ሄዝቦላህ ጋር የደረሰችውን ከፊል ተኩስ አቁም ተከትሎ በዋና ከተማዋ ቤይሩት ላይ ጥቃት አለመፈጸሟን ተገለጸ።

    ሊባኖስ የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ሰኞ አመሻሽ ላይ ይፋ ያደረጉትን ስምምነት ተከትሎ ሄዝቦላህ እስራኤል ላይ ጥቃት የማይፈጽም ከሆነ ጦሯ ቤይሩትን እንደማያጠቃ በማሳወቃቸው ድብዳው አልተፈጸመም ብላለች።

    ኢራን በበኩሏ እስራኤል በሊባኖስ ላይ ምትፈጽመው ጥቃት ከአሜሪካ ጋር ጦርነቱን ለማቆም የምታደርገውን ድርድር አደጋ ላይ የሚጥል መሆኑን አስታውቃለች።

    የተኩስ አቁሙ ይፋ ከሆነ በኋላ የእስራኤል ጦር ወደ አገሪቱ ሰሜናዊ ክፍል የተተኮሱ ተወንጫፊዎችን ማክሸፉን አስታውቋል።

    ሄዝቦላህ በደቡባዊ ሊባኖስ የሚገኙ የእስራኤል ኃይሎች ላይ ጥቃት መፈጸሙን የገለጸ ሲሆን፣ እስራኤል በበኩሏ ከባድ ጥቃት ማድረሷን አስታውቃለች።

    የሊባኖስ ጤና ሚኒስቴር እስራኤል በጃባል አመል ሆስፒታል አጠገብ የሚገን ሕንጻ ላይ ሰኞ ከሰዓት ጥቃት ከፈጸመች በኋላ አራት ሰዎች መገደላቸወን እና 127 መጎዳታቸውን አስታውቋል።

    ከተጎዱት መካከል 39 የሆስፒታል ሠራተኞች የሚገኙበት ሲሆን፣ አራቱ በአስጊ ሁኔታ ውስጥ ናቸው ተብሏል።

    የእስራኤል ጦር በአካባቢው የሚገኝ “የአሸባሪው ሄዝቦላህን መሠረተ ልማት” ማጥቃቱን ገልጾ፤ በሆስፒታሉ ላይ ጉዳት ቢደርስም “ዒላማ አልነበረም” ሲል አስተባብሏል።

    ሄዝቦላህ ሰላማዊ ሰዎች መሠረተ ልማቶች እና ሕዝብ በሚኖርባቸው ቦታዎች ላይ ይሸሸጋል ሲል ማስረጃ ሳያቀርብ ይወነጅላል።

    የሊባኖስ ጤና ሚኒስቴር በበኩሉ ባለፉት ሦስት ወራት ብቻ 128 የድንገተኛ አደጋ ሠራተኞች እና የጤና ባለሙያዎች መገደላቸውን በአምቡላንሶች እና በሕክምና ተቋማት ላይ ደግሞ 159 ጥቃቶች መፈጸማቸውን አስታውቋል።

    ሚኒስትሩ አክሎም ጦርነቱ ከተጀመረ ጊዜ አንስቶ 3,468 ሰዎች መገደላቸውነ የገለጸ ሲሆን፣ ቁጥሩን ግን ሰላማዊ ሰዎችን እና ተዋጊዎች አልለየም።

    የተባበሩት መንግሥታት በበኩሉ የእስራኤል ጦር ከአገሪቱ አንድ ስምንተኛ አካባቢ ነዋሪዎች ከመኖሪያቸው ለቅቀው እንዲወጡ ካስጠነቀቀ ወዲህ 1 ሚሊዮን ሰዎች መፈናቀላቸውን ገልጿል።

    እስራኤል 25 ወታደሮቿ እና አራት ሰላማዊ ሰዎች በዚህ ጦርነት ወቅት መገደላቸውን አስታውቃለች።

    የሊባኖስ ባለሥልጣናት እስራኤል በሆስፒታል አቅራቢያበፈጸመችው ጥቃት የሆስፖታሊ ሰራተኞች ክፉኛ መጎዳታቸውን ግለጸዋል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

  7. የተኩስ አቁም ድርድሩ በተደናቀፈበት ሁኔታ አሜሪካ እና ኢራን ጥቃት መፈጸማቸውን አስታወቁ

    የአሜሪካ ጦር የለቀቀው ምስል

    የፎቶው ባለመብት, X/US Central Command

    የአሜሪካ ጦር በኢራን ደሴት ላይ ‘ራስን የመከላከል’ ጥቃት መፈጸሙን እና ወደ መርከቦች እና የባሕረ ሰላጤው አገራት የተተኮሱ ሚሳዔሎች እና ድሮኖችን መትቶ መጣሉን አስታወቀ።

    የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም) በሆርሙዝ ወሽመጥ እና ኣለይ በቄሸም ደሴት ላይ “ኢራን ወደ መካከለኛው ምሥራቅ አገራት ልትፈጽም የነበረውን የጥቃት ሙከራ ተከትሎ” ጥቃት መሰንዘሩን አስታውቋል።

    ኢራን ወደ ኩዌት ሁለት ሚሳዔሎችን ማስወንጨፏን ነገር ግን የታለመላቸውን ስፍራ ሳይደርሱ መውደቃቸውን እንዲሁም ሦስት ወደ ባሕሬን የተወነጨፉ ደግሞ በአየር ላይ እንዲከሽፉ መደረጋቸውን ገልጿል።

    የኢራን አብዮታዊ ዘብ በበኩሉ በቄሸም ደሴት በሚገኝ የግንኙነት ማማ ላይ ለተፈጸመ ጥቃት በሰጠው ምላሽ በቀጣናው የሚገኙ የአሜሪካ የጦር ሰፈሮችን እና ሂሊኮፕተሮችን ማጥቃቱን በአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን በኩል አስታውቋል።

    ሴንትኮም በቄሸም ደሴት ላይ የተፈጸመው ጥቃት የኢራን ጦር የምድር መቆጣጠሪያ ጣቢያ፣ ኢራን “በቀጣናው ውሃዎች ላይ የማለፍ መብት ያላቸው ሰላማዊ ባሕረተኞች” ላይ የተኮሰቻቸውን ሦስት ድሮኖችን መትቶ መጣሉን አስታውቋል።

    አብዮታዊ ዘቡ “የሆርሙዝ ወሽመጥን ደኅንነት ማወክ ጠብ አጫሪውን የአሜሪካ ጦር ከባድ ዋጋ ያስከፍለዋል” ሲል በመግለጫው ላይ አስታውቋል።

    ኢራን በተደጋጋሚ የአሜሪካ ጦር ሰፈሮች በሚገኙባቸው ባሕሬን እና ኩዌት ላይ ጥቃቶቸን ፈጽማለች።

    ቀደም ሲል ሴንቲኮም አሜሪካ የጣለችውን እገዳ ተከትሎ ወደ ኢራን እየቀዘፈ የነበረ ነዳጅ ጫኝ መርከብን ማጥቃቱን እና እንዳይንቀሳቀስ ማድረጉን አስታውቋል።

    የአሜሪካ አየር ኃይል የቦትስዋናን ሰንደቅ ዓላማ የሰቀለ ነዳጅ ጫኝ መርከብ በተደጋጋሚ የተሰጠውን ማስጠንቀቂያ ችላ ማለቱን ተከትሎ በሞተሩ ላይ ጥቃት መፈጸሙን ተገልጿል።

    ሴንቲኮም ማክሰኞ ዕለት መርከቦ ላይ ጥቃት ሲፈጽም የሚያሳይ ተንቀሳቃሽ ምሥል ያሠራጨ ሲሆን የኢራን ጦር በይፋ የሰጠው ምላሽ የለም።

    ዕዙ በመግለጫው ከአውሮፓውያኑ ሚያዝያ 13 ጀምሮ አሜሪካ ወደ ኢራን ወደቦች የሚደረጉ እንቅስቃሴዎችን ማገዷን አስታውሶ፣ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ 122 መርከቦች አቅጣጫቸውን አንዲቀይሩ እና እንዲመለሱ መደረጋቸውን አሻፈረኝ ያሉትም ሞተራቸው እነዳይሠራ መደረጉን አስታውቋል።

    ቢቢሲ የቦትስዋናን መንግሥት አስተያየት ለማግኘት ቢሞክርም አልተሳካም።

    አሜሪካ ይህንን ጥቃት የፈጸመችው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ማርኮ ሩቢዮ በአገሪቱ ምክር ቤት ለመጀመሪያ ጊዜ ቀርበው ስለ ኢራን ጦርነት ከተጠየቁ በኋላ ነው።

  8. ኢራን ሠራዊቷ መጠናከሩን ስትገልጽ፣ እስራኤል ደግሞ የኢራን መንግሥት መሠረቱ ተናግቷል አለች

    የኢራን ጠቅላይ መሪ ሞጅታባ ኻሜኒ እና የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታኒያሁ
    የምስሉ መግለጫ, የኢራን ጠቅላይ መሪ ሞጅታባ ኻሜኒ እና የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታኒያሁ

    ኢራን የጦር ሠራዊቷ ከጦርነቱ በኋላ የበለጠ መጠናከሩን ስትገልጽ፣ እስራኤል ደግሞ የኢራን መንግሥት ክፉኛ ተዳክሞ ሊወድቅ መቃረቡን ጠቅላይ ሚኒስትሯ ተናገሩ።

    የኢራን ሠራዊት የተኩስ አቁም በተደረገበት ጊዜ በሁሉም መስኩ ለውጊያ ዝግጁ የሚያደርጉ ሥራዎችን ሲያከናውን መቆየቱን የአብዮታዊው ዘብ ቃል አቀባይ ገለጹ።

    ሁሴን ሞሄቢ እንደተናገሩት "በተኩስ አቁሙ ወቅት የሠራዊታችን ተልዕኮ የመፈጸም አቅም ጨምሯል፣ በተፈጠረው ዕድልም የውጊያ አቅሙ፣ ጥንካሬው፣ ዝግጁነቱ እና አደጋን የመቋቋም ብቃቱ ተጠናክሯል። በአሁኑ ወቅትም ጦሩ ቀደም ሲል ከነበረው አቋም በተሻላ ሁኔታ ላይ ይገኛል” ብለዋል።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታኒያሁ የኢራን መንግሥት በደረሰበት ጥቃት መሠረቱ መናጋቱን እና መውደቁ የማይቀር መሆኑን በኤክስ ገጻቸው ላይ ጽፈዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ "የዚህ የሽብር አገዛዝ መሠረቱ ተናግቷል” በማለት “አገዛዙ ከዚህ በኋላ ቀድሞ ወደነበረበት ደረጃ ፈጽሞ አይመለስም፤ መውደቁ እንደማይቀር እነግራችኋለው” ሲሉ የኢራን መንግሥት መዳከሙን አመልክተዋል።

    የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ይህንን አስተያየት የሰጡት የኢራን ጠቅላይ መሪ ሞጅታባ ኻሜኒ በተመሳሳይ እስራኤል ክፍኛ መዳከሟን ከተናገሩ በኋላ ነው።

    ጠቅላይ መሪው በቅርቡ ባስተላለፉት መልዕክት “አስራኤል መጪዎቹን 15 ዓመታት አታይም” በማለት ትጠፋለች የሚል አስተያየት ሰንዝረዋል።

    እስራኤል በኢራን ላይ ሁለት ጊዜ ጥቃቶችን የፈጸመች ሲሆን፣ ኢራን በበኩሏ ከባድ የአጸፋ ምላሽ በሚሳዔሎች እና በድሮኖች ፈጽማለች።

    ባለፈው የካቲት እስራኤል ከአሜሪካ ጋር አብራ በኢራን ላይ በፈጸመችው ጥቃት የኢራን ጠቅላይ መሪን ጨምሮ በርካታ የአገሪቱ ባለሥልጣናት ተገድለዋል።

    ኢራንም በበኩሏ በእስራኤል እና በአካባቢው ባሉ የአሜሪካ አጋሮች ላይ ተከታታይ የሚሳዔል እና የድሮን ጥቃቶችን በመፈጸም ከባድ ጉዳትን አድርሳለች።

  9. ፕሬዝዳንት ሩቶ በአሜሪካ የሚቋቋመውን የኢቦላ ህክምና ማዕከልን ሲደግፉ ፍርድ ቤት ዕግዱን አራዘመ

    ሰልፈኛ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, በአሜሪካ የሚከፈተውን የኢቦላ ህክምና ማዕከልን በመቃወም በተካሄደ ሰልፍ ሁለት ሰዎች ተገድለዋል

    የኬንያው ፕሬዝዳንት ዊሊያም ሩቶ ተቃውሞ የገጠመውን የኢቦላ ተጠርጣሪዎችን ለመለየት የሚያስችል ማዕከል ለማቋቋም ከአሜሪካ ጋር የተደረሰውን ስምምነት ቢደግፉም የአገራቸው ፍርድ ቤት ግን በማዕከሉ ላይ የጣለውን ዕገዳ አራዘመ።

    ላይኪፒያ በተባለችው የኬንያ ማዕከላዊ ግዛት ውስጥ የሚከፈተውን የህክምና ማዕከል በመቃወም ከተካሄደው ሰልፍ ጋር በተያያዘ ሁለት ሰዎች መገደላቸው ተዘግቧል።

    ፕሬዝዳንቱ ከአሜሪካ ጋር የሚቋቋመው የህክምና ማዕከል ኬንያውያንን ጭምር የሚጠቅም የጋራ ስምምነታቸው አካል መሆኑን እና ኬንያ ተላላፊ በሽታዎችን ለመከላከል እንዲሁም ህሙማንን ለማከም የሚያስችላት መሆኑን በመጥቀስ ተከራክረዋል።

    ፕሬዝዳንቱ ይህንን በተናገሩበት ጊዜ የኬንያ ከፍተኛው ፍርድ ቤት ከአሜሪካ እና ከሌላ ከማንኛውም የውጭ መንግሥት ጋር በሚደረግ ስምምነት የሚመሠረት እና ሥራ ላይ የሚውል የኢቦላ ህሙማን መለያ ተቋምን የሚያግደውን ጊዜያዊ ውሳኔውን አራዝሟል።

    ፍርድ ቤቱ ዛሬ ባስተላለፈው ውሳኔ የኬንያ መንግሥት በሰባት ቀናት ውስጥ ከአሜሪካ መንግሥት ጋር የተደረሰውን አወዛጋቢ ስምምነት ይፋ እንዲያደርግ አዝዟል።

    በተጨማሪም መንግሥት እና ሌሎች አካላት “ጉዳዩ በፍርድ ቤት እልባት እስኪያገኝ ድረስ የኢቦላ ለይቶ ማቆያ ማዕከል ከመክፈት፣ ሥራ ከማስጀመር፣ ፈቃድ ከመስጠት እና ከማጽደቅ እንዲታቀቡ” ውሳኔውን አጽንቷል።

    የለይቶ ማቆያ ማዕከሉ ይቋቋምበታል በተባለው በማዕከላዊ ኬንያ ናኙኪ ከተማዋ ውስጥ ውጥረት የተፈጠረ ሲሆን፣ በመቶዎች የሚቆጠሩ ነዋሪዎች የህክምና ማዕከሉ ሊያስከትል የሚችለውን ተጽእኖ በመጥቀስ አደባባይ ወጥተው ተቃውሟቸውን ገልጸዋል።

    በተቃዋሚዎች እና በፖሊስ መካከል በተፈጠረው ግጭት ሁለት ሰዎች በጥይት ተመትተው መሞታቸው ተዘግቧል።

  10. ተመድ እስራኤል የሊባኖስን አምባ መቆጣጠሯን በተመለከተ አስቸኳይ ውይይት አካሄደ

    የፀጥታው ምክር ቤት

    የፎቶው ባለመብት, EPA-EFE/REX/Shutterstock

    የተባበሩት መንግሥታት የፀጥታው ምክር ቤት እስራኤል የሊባኖስን ጥንታዊ አምባ - ቢውፎርትን በቁጥጥር ሥር ማዋሏን በተመለከተ ትናንት አስቸኳይ ውይይት አካሄደ።

    በተመድ የሩሲያ አምባሳደር ቫስሊ ነቤንዝ “እስራኤል እና ሊባኖስ በአሜሪካ አሸማጋይነት የደረሱት የተኩስ አቁም ስምምነት እስራኤል ሊባኖስ ላይ ጥቃት እንድትፈጽም ከለላ ሰጥቷል” ብለዋል። ሊባኖስ የጋዛ ሰርጥ እጣ ፈንታ እንደሚጠብቃትም አክለዋል።

    በተመድ የፈረንሳይ ልዑክ ጀሮም ቦንፎን ውይይቱ እንዲካሄድ አገራቸው ጥሪ ማቅረቧን ጠቅሰው “እስራኤል ራሷን የመለካከል መብት ቢኖራትም ሊባኖስ ላይ የምታደርሰው ጥቃት ምክንያታዊ አይደለም” ብለው ንግግር አድርገዋል።

    በሺዎች የሚቆጠሩ ንጹኃን እንደተጎዱ እና እንደተፈናቀሉ የፈረንሳዩ ተወካይ ተናግረዋል።

    የአሜሪካ ተወካይ ማይክል ጄ ዋልዝ በበኩላቸው፤ድርድርን ጨምሮ ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶች መቀጠላቸውን ገልጸዋል።

    “ሕጋዊው የሊባኖስ መንግሥት በቴህራን ከሚደገፈው አሸባሪ አገሪቱን ነጻ ለማውጣት ተነሳሽነት አሳይቷል” ብለዋል።

    የሊባኖስ ተዋካይ አሕመድ አራፋ ደግሞ መንግሥታቸው ነገሮችን ለመቆጣጠር ቢሞክርም “እስራኤል እንደ ሁልጊዜው ቀጣናዊውን ሁኔታ እየተጠቀመችበት ነው” ብለዋል።

    እስራኤል ሐኪሞችን፣ ሆስፒታሎችን፣ ጋዜጠኞችን፣ ትምህርት ቤቶችን እና የፀጥታ ተቋማትን ዒላማ በማድረግ “ስልታዊ የውድመት ዘመቻ” መክፈቷንም ጠቅሰዋል።

    በተመድ የእስራኤል ልዑክ ዳኒ ዳኖን “አንድ ቀን ተነስተን ሊባኖስ ለመግባት አልወሰንም። አማራጭ አጥተን ነው” ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል።

    ኢራን ሄዝቦላህን በእጅ አዙር መጠቀም መቀጠሏን ጠቅሰው፤ የተኩስ አቁም ስምምነት ላይ ቢደረስም “ሄዝቦላህ ሚሳዔል እና ድሮን መተኮስ” እንዳላቆመ ተናግረዋል።

  11. በቀጣይ ሳምንት ከኢራን ጋር ስምምነት ላይ ሊደረስ እንደሚችል ትራምፕ ተናገሩ

    ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ከኢራን ጋር የተኩስ አቁም ለማራዘም እና የሆርሙዝ ወሽመጥን ለመክፈት በቀጣይ ሳምንት ስምምነት ላይ እንደሚደረስ የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ለኤቢሲ በሰጡት ቃለ ምልልስ ተናገሩ።

    “አሁን ላይ ነገሮች በጣም ጥሩ ናቸው። ውስን ችግር ነበር፤ ነገር ግን እንዳያችሁት በፍጥነት ፈትቼዋለሁ” ሲሉ በስልክ በሰጡት ቃለ ምልልስ ገልጸዋል።

    ትራምፕ ችግር ብለው የጠቀሱት እስራኤል በሊባኖስ ላይ የምታደርሰው ጥቃት ኢራንን ማስቆጣቱን ነው።

    ሄዝቦላህ በእስራኤል ላይ ጥቃት ማድረስ እንዲያቆም ከአሜሪካ የቀረበለትን ሐሳብ መቀበሉን ሊባኖስ አስታውቃለች። እስራኤልም በሊባኖስ መዲና ቤሩት ጥቃት ላለመፈጸም መስማማቷም ተገልጿል።

    ትራምፕ ከጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ እና ከሄዝቦላህ ተወካዮች ጋር መወያየታቸውን ጠቅሰው “ተኩስ ለማቆም ተስማምተዋል” ብለዋል።

    ትራምፕ “ሄዝቦላህን አትተኩሱ ብያቸዋለሁ። ቢቢ [ኔታንያሁ] እንዳይተኩስም ነግሬዋለሁ። ሁለቱም ተኩስ አቁመዋል” ሲሉም አክለዋል።

    በቀጣይ ሳምንት የሆርሙዝ ወሽመጥ ይከፈታል ብለው እንደሚያምኑም ፕሬዝዳንቱ ተናግረዋል።

  12. ሩሲያ በዩክሬን ከተሞች በፈጸመችው ጥቃት ቢያንስ 16 ሰዎች ተገደሉ

    ሞስኮ የፈጸመችው ጥቃት በነዳጅ ማደያ እሳት አቀጣጥሏል።

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ሩሲያ በዩክሬን ዋና ዋና ከተሞች ባደረሰችው ጥቃት ቢያንስ 16 ሰዎች እንደተገደሉ እና ብዙዎች እንደቆሰሉ ተገለጸ።

    በዲፕሮ ከተማ 11 ሰዎች ሲገደሉ 25 ሰዎች ተጎድተዋል። ዛሬ ንጋት ላይ በደረሱ ጥቃቶች በመዲናዋ ኪቭ አምስት ሰዎች መገደላቸው እና 51 መቁሰላቸውም ተዘግቧል፤ 35 ያህሉ ደግሞ ሆስፒታል ገብተዋል።

    የኪቭ ከንቲባ ቪታሊ ክሊሽኮ እንዳሉት ሁለት ግዙፍ የመኖሪያ ሕንጻዎች የተመቱ ሲሆን፤ ሰዎች በፍርስራሽ ሥር ተቀብረው ሊሆን እንደሚችል ይገመታል።

    ዩክሬን ባለፈው ወር የድሮን ድብደባ በመፈጸሟ በምላሹ “ስልታዊ ጥቃት” ለማድረስ ሞስኮ ስትዝት ቆይታለች።

    ሩሲያ በቁጥጥሯ ሥር ባዋለችው የዩክሬን ሉሀንስክ ግዛት በደረሰው የድሮን ጥቃት 21 ሰዎች ተገድለዋል።

    የኪቭ ከንቲባ ነዋሪዎች ከቤታቸው እንዳይወጡ ማስጠንቀቂያ ሰጥተዋል። “ጠላታችን በባለስቲክ ሚሳዔል ጥቃት እየፈጸመ ነው” ሲሉም ተናግረዋል።

    በአብዛኞቹ የዩክሬን ከተሞች የአየር ጥቃት ማስጠንቀቂያ ደወሎች እየተሰሙ ነው። በማዕከላዊ ኪቭ ጭስ መታየቱም ተገልጿል።

    በሌላ በኩል በሩሲያ ኢልስኪ የነዳጅ ማቀነባበሪያ የደረሰ ጥቃት እሳት ማስነሳቱ ተገልጿል።

    ኪቭ ውስጥ የበርካታ ድሮኖች እና ፍንዳታ ድምጽ እየተሰማ ይገኛል። ሞስኮ የፈጸመችው ጥቃት በነዳጅ ማደያ እሳት አቀጣጥሏል።

    ጥቃት የደረሰበት ሕንጻ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

  13. ሄዝቦላህ በእስራኤል ላይ ጥቃት ማድረሱን ለማቆም መስማማቱን ሊባኖስ ገለጸች

    ቤሩት

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ሄዝቦላህ በእስራኤል ላይ ጥቃት ማድረስ እንዲያቆም ከአሜሪካ የቀረበለትን ሐሳብ መቀበሉን ሊባኖስ አስታወቀች።

    እስራኤልም በሊባኖስ መዲና ቤሩት ጥቃት ላለመፈጸም መስማማቷም ተገልጿል።

    አሜሪካ የሚገኘው የሊባኖስ ኤምባሲ “አሜሪካ ሁለቱም ወገኖች ጥቃት እንዳያደርሱ ያቀረበችውን ምክረ ሐሳብ ሄዝቦላህ ተቀብሏል” ብሏል።

    የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁም ስምምነት ላይ መደረሱን አረጋግጠዋል።

    ሆኖም “ሄዝቦላህ ከተሞቻችን እና ዜጎቻችን ላይ ጥቃት ከፈጸመ ግን ቤሩትን እንደበድባለን” ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከኔታንያሁ እና ከሄዝቦላህ ተወካዮች ጋር መወያየታቸውን ጠቅሰው “ተኩስ ለማቆም ተስማምተዋል” ብለዋል።

    እስራኤል በሊባኖስ የምታደርሰው ጥቃት የኢራን እና አሜሪካን የተኩስ አቁም ስጋት ውስጥ እንደሚጥል ቴህራን መግለጿ ይታወሳል።

    የሊባኖስ ኤምባሲ ባወጣው መግለጫ “ሄዝቦላህ እስራኤል ላይ ጥቃት ካልፈጸመ እስራኤልም በቤሩት ጥቃት እንደማታደርስ ተስማምተናል” ብሏል።

    የተኩስ አቁሙ በሒደት “ሌሎች የሊባኖስ አካባቢዎችን እንደሚሸፍን” ተገልጿል።

    ኔታንያሁ በበኩላቸው “የእስራኤል መከላከያ ኃይል በታቀደው መሠረት በደቡብ ሊባኖስ ዘመቻውን ይቀጥላል” ብለዋል።

    ሁለቱ ወገኖች ተኩስ ለማቆም መስማማታቸውን ትራምፕ ከገለጹ በኋላ የተወሰኑ ግጭቶች መነሳታቸው ተዘግቧል።

  14. ፕሬዝዳንት ትራምፕ የአሜሪካ እና የኢራን ስምምነትን ለማረም ፍላጎት እንዳላቸው ተነገረ

    ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከሦት ወራት በፊት የተጀመረውን የአሜሪካ እና ኢራን ጦርነት ለመቋጨት የሚያስችለውን ስምምነት ለማስተካከል ፍላጎት እንዳላቸው የዋሽንግተን መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ።

    ለውጦቹ በሆርሙዝ ወሽመጥ እና የተብላላ የዩራኒየም አወጋገድ ጋር የተያያዙ እንደሆኑ በአሜሪካ የቢቢሲ አጋር የሆነው ሲቢኤስ ኒውስ ዘግቧል።

    ዋይት ሐውስ አስተያየት እንዲሰጥ ቢጠየቅም ምላሽ አልሰጠም።

    የኢራን ዋና ተደራዳሪ መሐመድ ባገር ጋሊባፍ እሑድ ዕለት የኢራን መብት ሙሉ ለሙሉ እስካልተጠበቀ ድረስ ቴህራን ምንም ዓይነት ስምምነት አትፈጽምም ብለዋል።

    የተኩስ አቁም ስምምነቱን ለማራዘም በሚያስችለው ማዕቀፍ ላይ ፕሬዝዳንት ትራምፕ እና ከፍተኛ ባለሥልጣናት ጋር አርብ ዕለት ለንግግር ቢቀመጡም፤ ስብሰባው ቀጣይ እርምጃዎች ላይ ግልፅነት ሳይኖረው ተጠናቋል። ሙሉውን እዚህ ያንብቡ ፕሬዝዳንት ትራምፕ የአሜሪካ እና የኢራን ስምምነትን ለማረም ፍላጎት እንዳላቸው ተነገረ